ፈልግ

ር. ሊ. ጳ. ፍራንችስኮስ፥ አመስጋኞች እንድንሆን የቅድስት ማርያምን ዕርዳታ በጸሎት ጠየቁ

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ እሑድ መስከረም 27/2016 ዓ. ም. በቅዱስ ጴጥሮስ አደባባይ ለተሰበሰቡት ምዕመናን፣ መንፈሳዊ ነጋዲያን እና የአገር ጎብኝዎች በዕለቱ ቅዱስ ወንጌል ላይ በማስተንተን ስብከታቸውን አቅርበዋል። ቅዱስነታቸው ለምዕመናኑ ካቀረቡት የቅዱስ ወንጌል አስተንትኖ በመቀጠል የመልአከ እግዚአብሔር ጸሎት በኅብረት ካደረሱ በኋላ ንግግር አድርገዋል።

የዚህ ዝግጅት አቅራቢ ዮሐንስ መኰንን - ቫቲካን

እሁድ መስከረም 27/2016 ዓ. ም. ከማቴ. 21:33-43 ተወስዶ በተነበበው የቅዱስ ወንጌል ክፍል ላይ በማስተንተን ስብከታቸውን ያቀረቡት ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ፥ በዚህ የወንጌል ክፍል የተገለጸው የክፉ ገበሬዎች ምሳሌ፥ በወይን አትክልት ገበሬዎች አእምሮ ውስጥ የምስጋና ቢስነት እና የስግብግብነት ሃሳብ ገብቶ የሥራቸው ውጤት ወይም የእርሻው ፍሬ የራሳቸው ብቻ እንደሆነ አድርገው እንዲያስቡ ማድረጉን ገልጸው፥ ገበሬዎቹ አትክልቱን ተንከባክበው መከሩን ከመሬቱ ባለቤት ጋር ከመካፈል ይልቅ ሁሉንም ነገር ለራሳቸው ለማድረግ በመፈለግ የእርሻው ጌታ አገልጋዮችን በማንገላታት በመጨረሻም ልጁን እንደገደሉ አስታውሰዋል።

ምስጋና ቢስነት ወደ ሁከት ይመራል

በምሳሌ ላይ ያስተነተኑት ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ፥ ገበሬዎቹ ከእርሻው ላገኙት የላባቸው ፍሬ እና ለተደረገላቸው አያያዝ አመስጋኖች መሆን ሲገባቸው፥ ይልቁንስ ምስጋና ቢሶች እና ስግብግቦች በመሆን በልባቸው ውስጥ የዓመፅ እና የሁከት ስሜት እየሰፋ ሄዶ ሁኔታውን በተዛባ መልኩ እንዲያዩት እንዳደረጋቸው ተናግረው፥ ከእርሻው እንዲጠቀሙ ዕድል የሰጣቸውን የእርሻውን ጌታ የባለ ዕዳነት ስሜት እንዲሰማው ማድረጋቸውን አስታውሰዋል።

በዚህም የእርሻው ሠራተኞች ከመሆን ይልቅ ነፍሰ ገዳይ ሆነው መገኘታቸውን ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ ተናግረው፥ ቀጥለውም በዚህ ምሳሌ አማካይነት ኢየሱስ ክርስቶስ አንድ ሰው ሌሎች ያደረጉለትን ዕርዳታ በሚዘነጋበት ወቅት እና በከንቱ ሃሳብ ሲታለል ምስጋና ቢስ እንደሚሆን ለማስታወስ መፈለጉን አስረድተዋል። ምስጋና ቢስነት ባገኙት ወደ አለመርካት፣ ወደ አለመግባባት ወደ ቂመኝነት እና በመጨረሻም ሁከትን እንደሚያስነሳ በመግለጽ፥ ምስጋና ቢስነት ዓመፅን እንደሚፈጥር እና ምስጋናን ማቅረብ ግን ሰላምን መልሶ ሊያመጣ እንደሚችል ቅዱስነታቸው አስረድተዋል።

'አመሰግናለሁ' ማለትን መማር

ሕይወታችን እና እምነታችን፣ ሁለመናችን እና የራሳችን የምንለው ነገር በሙሉ ከእግዚአብሔር ጸጋ የተገኙ መሆናቸውን ከተገነዘብን፥ እግዚአብሔርን ለጸጋው ምስጋናን እንድናቀርብ ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ ጋብዘውናል።

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ እሑድ መስከረም 27/2016 ዓ. ም. ያቀረቡትን የቅዱስ ወንጌል  አስተንትኖ በጸሎት ሲያጠቃልሉ፥ በነፍሷ እግዚአብሔርን ያከበረች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም፥ ልባችን ውስጥ በየቀኑ በሚበራው ብርሃን አማካይነት ዘወትር አመስጋኞች እንድንሆን እንድታግዘን በመለመን በቅዱስ ጴጥሮስ አደባባይ ከምዕመናን ጋር በኅብረት ያቀረቡትን የመልአክ እግዚአብሔር ጸሎት አጠናቀዋል።

 

 

09 October 2023, 17:20

የገብርኤል ብሥራት ጥንታዊ መሠርት የያዘና የጌታችን እየሱስ ክርስቶስን ሰው መሆን በማስታወስ በቀን ሦስት ጊዜ ማለትም በንጋት (በአስራሁለት ሰዓት) በቀትር (በስድስት ሰዓት) እንዲሁም በማታ (በአስራሁለት ሰዓት) የሚደገም የጸሎት ዓይነት ሲሆን ጸሎቱ በሚደገምበት ሰዓት ቤተ ክርስቲያንም የመልኣከ እግዚኣብሔርን ደወል በዚሁ ሰዓት ትደውላለች። ይህ ጸሎት መልኣከ እግዚኣብሔር የሚለውን ስያሜ ያገኝው ከጸሎቱ ከመጀመሪያ ስንኝ የእግዚኣብሔር መልኣከ ማርያምን አበሠራት ከሚለው የተወሰደ ሲሆን ጸሎቱ ስለ ጌታችን እየሱስ ክርስቶስ ሰው መሆን ይናገራል። ጸሎቱ በሦስት የተከፈሉ አጫጭር ስንኞች ሲኖሩት በእነኚህ በሦስት አጫጭር ስንኞች መሓል ጸጋን የተሞላሽ የሚለው የማርያም ጸሎት ይደገማል። ይህ ጸሎት በሰንበትና በበዓላት ዕለት ልክ በእኩለ ቀን ላይ በዕለቱ ወንጌል ላይ ትንሽ አስተምሮና ገለፃ ከሰጡ በኋላ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት በቅዱስ ጴጥሮስ ኣደባባይ ላይ ይህንን ጸሎት ይመራሉ። በመቀጠልም በአደባባዩ ላይ የተገኝው ከተለያየ ቦታ ለንግደት የመጣውን ሕዝብ ሰላምታ ይሰጣሉ።በየትኛውም ጊዜ ከበዓለ ፋሲካ እስከ በዓለ ጰራቅሊጦስ በመልኣከ እግዚኣብሔር ጸሎት ፈንታ የጌታችን እየሱስ ክርስቶስን ትንሣኤ የሚዘክረውን “የሰማይ ንግሥት ሆይ ደስ ይበልሽ” የሚለው ጸሎት የሚደገም ሲሆን በመሓል በመሓሉ ጸጋን የተሞላሽ ማርያም ሆይ የሚለው ጸሎት ይታከልበታል።

መልኣኩ ገብርኤል ማሪያምን አበሰራት የሚለው የቀርብ ጊዜ ጸሎት

ሁሉንም ያንብቡ >