ር.ሊ.ጳ ፍራንቸስኮስ መንፈስ ቅዱስ ርቀቶችን በማገናኘት ረገድ ልዩ ችሎታ አለው ማለታቸው ተገልጸ።
ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ ዘወትር እሁድ እለት በቫቲካን በሚገኘው የቅዱስ ጴጥሮስ አደባባይ ለሚሰበሰቡ መዕመናን በእለቱ በሚነበበው ቅዱስ ወንጌል ላይ ተንተርሰው የቅዱስ ወንጌል አስተንትኖ እንደሚያደርጉ ይታወቃል። በዚህ መሰረት ቅዱስነታቸው በግንቦት 28/2014 ዓ.ም ያደረጉት አስተንትኖ በወቅቱ የጎርጎሮሳዊያኑን የቀን አቆጣጠር በሚከተሉ የካቶሊክ ቤተክርስቲያን ምዕመናን ዘንድ የተከበረውን የጴንጤቆስጤ በዓል ላይ መሰረቱን ያደረገ አስተንትኖ እንደ ነበረ የተገለጸ ሲሆን መንፈስ ቅዱስ ርቀቶችን በማገናኘት ረገድ ልዩ ችሎታ አለው ማለታቸው ተገልጿል።
የዚህ ዝግጅት አቅራቢ መብራቱ ኃ/ጊዮርጊስ ቫቲካን
ክቡራን እና ክቡራት የዝግጅቶቻችን ተከታታዮች ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ በወቅቱ ያደረጉትን የቅዱስ ወንጌል አስተንትኖ ሙሉ ይዘቱን እንደ ሚከተለው አሰናድተነዋል፣ ተከታተሉን።
የተወደዳችሁ ወንድሞቼ እና እህቶቼ እንደምን አረፈዳችሁ፣ መልካም እለተ ሰንበት ይሁንላችሁ!
ዛሬ ደግሞ እንኳን ለበዓለ ሃምሳ አደረሳችሁ፤ ምክንያቱም ዛሬ የጴንጤቆስጤ በዓልን እያከበርን እንገኛለንና ነው። በሐዋርያት ላይ መንፈስ ቅዱስ የፈሰሰበትን እለት እናከብራለን። ይህም ከፋሲካ ከሃምሳ ቀናት በኋላ የሚከበር በዓል ነው። ኢየሱስ ብዙ ጊዜ ቃል ገብቶላቸው ነበር። በዛሬው የስርዓተ አምልኮ ሥርዓት ውስጥ የተነበበው ቅዱስ ወንጌል ኢየሱስ ለደቀ መዛሙርቱ ሲነግራቸው ከእነዚህ ተስፋዎች መካከል አንዱን ይተርካል፡- “ሁሉን ያስተምራችኋል የነገርኋችሁንም ሁሉ ያሳስባችኋል” (ዮሐንስ 14፡26) በማለት ይገልጻል። መንፈስ ቅዱስ የሚያደርገው ይህንን ነው፡ ክርስቶስ የተናገረውን ያስተምረናል ያሳስበናል። የኢየሱስን ወንጌል ወደ ልባችን እንዲገባ ያደረገው በዚህ መንገድ ስለሆነ ለማስተማር እና ለማስታወስ በእነዚህ ሁለት ድርጊቶች ላይ እናሰላስል።
በመጀመሪያ መንፈስ ቅዱስ ያስተምራል። በዚህ መንገድ፣ በእምነት የልምምድ ጉዞ ላይ የሚያቀርበውን የመራቅ መንፈስ መሰናክል እንድናሸንፍ ይረዳናል። በእምነት ልምድ የርቀት መሰናክልን እንድናሸንፍ ያስተምረናል። በእርግጥም በወንጌል እና በዕለት ተዕለት ሕይወት መካከል ትልቅ ርቀት እንዳለ ጥርጣሬ ሊፈጠር ይችላል-ኢየሱስ ከሁለት ሺህ ዓመታት በፊት የኖረ፣ እነሱ ሌሎች ጊዜያት እና ሌሎች ሁኔታዎች ናቸው፣ እናም ስለዚህ ወንጌሉ ጊዜ ያለፈበት ይመስላል፣ አሁን ያለንበት ወቅት፣ ከጥያቄዎቹ እና ከችግሮቹ ጋር ለመናገር የማይቻል ይመስላል። ጥያቄው ወደ እኛ ይመጣል፡ ወንጌል በኢንተርኔት ዘመን፣ በግሎባላይዜሽን ዘመን ምን ይላል? ቃሉ ምን ተጽዕኖ ሊያሳድር ይችላል?
መንፈስ ቅዱስ ርቀቶችን በማገናኘት ረገድ ልዩ ባለሙያተኛ ነው ልንል እንችላለን፣ ርቀቶችን እንዴት እንደሚያስተካክል ያውቃል። እነሱን እንዴት ማሸነፍ እንደምንችል ያስተምረናል። የኢየሱስን ትምህርት ከእያንዳንዱ ጊዜ እና ከማንኛውም ሰው ጋር የሚያገናኘው እሱ ነው። ከእርሱ ጋር የክርስቶስ ቃላት ትዝታ አይደሉም፣ የክርስቶስ ቃል፣ በመንፈስ ቅዱስ፣ ዛሬ ሕያው ሆነ! መንፈሱ ለእኛ ሕያዋን ያደርጋቸዋል፡ በቅዱሳት መጻሕፍት በኩል እርሱ ይናገረናል እና በአሁኑ ጊዜ ይመራናል። መንፈስ ቅዱስ የዘመናት ማለፍን አይፈራም፤ ይልቁንም ምእመናንን በጊዜያቸው ለሚከሰቱ ችግሮች እና ክስተቶች ትኩረት እንዲሰጡ ያደርጋል። በእውነት መንፈስ ቅዱስ ሲያስተምር በተግባር ይገለጻል፡ እምነትን ለዘላለም ወጣት ሆኖ እንዲቀጥል ያስችለዋል። እምነትን የሙዚየም ቁራጭ ለማድረግ እንራወጣለ፣ ይህ ደግሞ አደጋ ነው! እሱ በሌላ በኩል፣ ወቅታዊ፣ ሁልጊዜ ወቅታዊ፣ እምነትን ወቅታዊ ያደርገዋል፣ ይህ የእርሱ ሥራ ነው። መንፈስ ቅዱስ ራሱን ካለፉት ዘመናት ወይም ፋሽኖች ጋር አያቆራኝም፣ ነገር ግን የተነሣውን እና ሕያው የሆነውን የኢየሱስን አስፈላጊነት ዛሬ ላይ ያመጣል።
መንፈስ ይህን የሚያደርገው እንዴት ነው? እንድናስታውስ በማድረግ ነው የሚተገብረው። ሁለተኛው ግስ ይኸውና፣ ማስታወስ የሚለው ነው። ማሳሰብ ማለት ምን ማለት ነው? ማሳሰብ ማለት ወደ ልብ መመለስ ማለት ነው፣ መንፈስ ቅዱስ ወንጌሉን ወደ ልባችን ይመልሳል። ለሐዋርያት እንዳደረገው ሆነ፣ ኢየሱስን ብዙ ጊዜ ያዳምጡ ነበር፣ ነገር ግን ብዙም አልተረዱም። በእኛ ላይ ተመሳሳይ ነገር ይደርስብናል። ከበዓለ ሃምሳ ጀምሮ ግን ከመንፈስ ቅዱስ ጋር ያስታውሳሉ እና ይረዱታል። ቃላቶቹን በተለይም ለእነሱ እንደተሰራላቸው ይቀበላሉ፣ እናም ከውጫዊ እውቀት፣ የማስታወስ ግንዛቤ፣ ወደ አፍቃሪ ግንኙነት፣ ከጌታ ጋር ወደ ሚተማመን፣ አስደሳች ግንኙነት ይሸጋገራሉ። ይህን የሚያደርገው መንፈስ ቅዱስ ነው፣ “ከመስማት” ወደ ግል የኢየሱስ እውቀት የሚሸጋገር፣ ወደ ልብ የሚገባው በዚሁ መልኩ ነው። ስለዚህ መንፈስ ሕይወታችንን ይለውጣል፣ የኢየሱስን ሃሳቦች ሀሳባችን እንዲሆኑ ያደርጋል። ይህንንም የሚያደርገው ቃሉን በማስታወስ፣ የኢየሱስን ቃላት ዛሬ ወደ ልባችን በማምጣት ነው።
ወንድሞች እና እህቶች፣ መንፈስ ቅዱስ ኢየሱስን ካላስታወሰን በቀር እምነት የሚረሳ ይሆናል። በጣም ብዙ ጊዜ እምነት ትውስታ ሆኖ ይቀራል። ይልቁንም ትዝታ ሕያው ነው እና ሕያው ትውስታ በመንፈስ ነው የሚመጣው። እናም እኛ - እራሳችንን ለመጠየቅ እንሞክር - እኛ የምንረሳ ክርስቲያኖች ነን ወይ? የኢየሱስን ፍቅር ለመርሳት እና ወደ ጥርጣሬ እና ፍርሃት ለመግባት የሚያስፈልገው ውድቀት፣ ትግል፣ ቀውስ ብቻ ነው? እኛ የምንረሳ ክርስቲያኖች ብንሆን ወዮልን! መድኃኒቱ መንፈስ ቅዱስን መማጸን ነው። ይህንን ደጋግመን እናድርግ፣ በተለይም አስፈላጊ በሆኑ ጊዜያት፣ ከአስቸጋሪ ውሳኔዎች በፊት እና በአስቸጋሪ ሁኔታዎች ውስጥ። ወንጌልን በእጃችን ይዘን መንፈስ ቅዱስን እንጥራ። “መንፈስ ቅዱስ ሆይ፣ ና፣ ኢየሱስን አስታውሰኝ፣ ልቤን አብራልኝ” ልንል እንችላለን። ይህ የሚያምር ጸሎት ነው: "መንፈስ ቅዱስ ሆይ፣ ና፣ ኢየሱስን አስታውሰኝ፣ ልቤን አብራልኝ።" አብረን እንበለው? " መንፈስ ቅዱስ ሆይ ና ኢየሱስን አስታውሰኝ ልቤን አብራልኝ " ከዚያም ወንጌሉን ከፍተን አንድ ትንሽ ክፍል በቀስታ እናንብብ። መንፈስም ለሕይወታችን እንዲናገር ያደርገዋል።
ድንግል ማርያም በመንፈስ ቅዱስ ተሞልታ ወደ እርሱ እንደ ጸለይች ሁሉ እኛም እንድንጸልይ የእግዚአብሔርን ቃል እንድንቀበል መሻታችንን በአማላጅነቷ ታነሳሳልን።