ፈልግ

የኢየሱስ ክርስቶስ ስቅለት፤ የኢየሱስ ክርስቶስ ስቅለት፤ 

የቤተክርስቲያን አስተምህሮ መጎልበት ለለውጥ ያለውን ታማኝነት የሚገልጽ ነው ተባለ።

በርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ላይ የሚቀርቡ ትችቶች በሁለተኛው የቫቲካን ጉባኤ ላይ ያለውን ቅሬታ የሚገልጹ፣ የቀድሞ ርዕሳነ ሊቃነ ጳጳሳት ቅዱስ ዮሐንስ ጳውሎስ ዳግማዊ እና የርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ቤነዲክቶስ 16ኛ ሐዋርያዊ አስተምህሮችን የዘነጉ መሆናቸው ታውቋል። ትችቶቹ በጉባኤው ሰነድ በተቀመጡ አንቀጾች ሳይሆን፣ ከሁለተኛው የቫቲካን ጉባኤ ዓላማ እየራቁ መሄዳቸውን የሚያመለክቱ ናቸው ተብሏል። ከዚህም በተጨማሪ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያንን በመምራት ላይ በሚገኙት ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ ላይ የሚቀርቡ ትችት አዘል መልዕክቶች፣ ከእርሳቸው አስቀድሞ የነበሩ ርዕሳነ ሊቃነ ጳጳሳት ቅዱስ ዮሐንስ ጳውሎስ ዳግማዊ እና ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ቤነዲክቶስ 16ኛ ያመጡትን የቤተክርስቲያን እድገት ያላገናዘቡ ናቸው ተብሏል።     

የቫቲካን ዜና፤

የጋራ ውይይት ዓላማ፣

የቀድሞ ር. ሊ. ጳጳሳት ቅዱስ ዮሐንስ ጳውሎስ ዳግማዊ፣ ኢየሱስ ክርስቶስ ደቀ መዛሙርቱ አንድ እንዲሆኑ በማለት ያቀረበውን ጸሎት በመከተል ክርስቲያኖች ወደ አንድነት እንዲደርሱ በመመኘት ይፋ ያደረጉት “አንድ ስለ መሆን” የተሰኘ ሐዋርያዊ ቃለ ምዕዳን 25ኛ ዓመት ተከብሮ ማለፉ ይታወሳል። ከሃያ አምስት ዓመት በፊት ይፋ የሆነው የርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ቅዱስ ዮሐንስ ጳውሎስ ዳግማዊ ሐዋርያዊ ቃለ ምዕዳን፣ የዘመናችን አብያተ ክርስቲያናት የደረሱበትን ደርጃ ለማወቅ እና ጥረታቸውን በአዲስ መልክ አጠናክረው እንዲቀጥሉ የሚያግዝ ትንቢታዊ ቃለ ምዕዳን መሆኑ ሲታወቅ፣ ቅዱስ ዮሐንስ ጳውሎስ ዳግማዊ ይህን ሐዋርያዊ ቃለ ምዕዳን ይፋ ባደረጉበት ጊዜ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን ከተቀሩት የሐይማኖት ተቋማት ጋር ገንቢ ውይይቶችን እንድታደርግ የሚያበረታታ ሆኖ መገኘቱ ታውቋል። “አንድ ስለ መሆን” የተሰኘ ሐዋርያዊ ቃለ ምዕዳን 25ኛ ዓመት በአንዳንድ ሰዎች ዘንድ በቂ ትኩረት ያልተሰጠው ትክክለኛ ዓላማውን ካለማወቅ እና አሁን የምንገኝበትን ዘመን የማይመጥኑ ባሕላዊ መንገዶችን በመከተል፣ ለውይይት ራስን ዝግ ከማድረግ፣ የቅዱስ ዮሐንስ ጳውሎስ ዳግማዊ ሐዋርያዊ አስተምህሮችን ከመዘንጋት እና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ አባቱ ዘንድ ያቀረበውን የአንድነት ጸሎት ተግባራዊ ለማድረግ ፈቃደኛ ካለመሆን የተነሳ መሆኑ ታውቋል።

ይቅርታን የማድረግ ዓላማ፣

የክርስቲያኖችን አንድነት ለማሳደግ የሚረዳ ሌላው መንገድ፣ የቀድሞ ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ቅዱስ ዮሐንስ ጳውሎስ ዳግማዊ ከሃያ ዓመት በፊት ይፋ ያድረጉት የ2000 የምሕረት ዓመት መታሰቢያ መሆኑ ይታወሳል። የቀድሞ ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ቅዱስ ዮሐንስ ጳውሎስ ዳግማዊ ያወጁት የምሕረት ዓመት ኢዮቤልዩ፣ ቤተክርስቲያን ባለፉት ዘመናት ለፈጸመቻቸው ኃጢአቶች ከእግዚአብሔር ምሕረትን ለመለመን መልካም መንገድ ያመቻቸ መሆኑ ይታወሳል። የእግዚአብሔር ልጆች ሲባል ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳትንም የሚጨምር ያስታወቁት ቅዱስ ዮሐንስ ጳውሎስ ዳግማዊ፣ ምህረትን በምንለምንበት ጊዜ አንዳንድ ያልተጠበቁ ጉዳቶች ሊያጋጥሙ እንደሚችል ተናግረው ቢሆንም ሁል ጊዜ የእውነት መንገድ መከተል እንደሚያስፈልግ እና  ቤተክርስቲያንም እውነትን መፍራት እንደሌለባት ማሳሰባቸው ይታወሳል። በወቅቱ የቅድስት መንበር የእምነት ጉዳይ የሚከታተል ጳጳሳዊ ጽሕፈት ቤት አስተባባሪ የነበሩት እና በኋላም ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሆነው የተመረጡት ዮሴፍ ራትሲንገር፣ ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ቤተክርስቲያን የፈጸመቻቸው በደሎች መኖራቸውን በማመን ምሕረት መጠየቃቸው ከዚህ በፊት ተደርጎ የማይታወቅ አዲስ ተግባር ነው በማለት መናገራቸው ይታወሳል።

በማደግ ላይ ያለ የመብት ጥያቄ እና አመጽ፣

የክርስትና ታሪክ እንዲዘነጋ የሚያደርጉ፣ የክርስቲያኖች የአንድነት ጥረቶች እና ውይቶች በተገቢው መንገድ እንዳካሄዱ የሚያደርጉ፣ የተሳሳቱ ታሪኮች በመጥቀስ በቤተክርስቲያን ውስጥ የጥላቻ ተግባራት የሚፈጽሙ አልጠፉም። የታሪክ አጥኚዎችም እውነትን ለማግኘት በሚደረጉ ጥረቶች መካከል ታሪክን እና እውነትን የሚያዛቡ ተግባራት መፈጸማቸውን ያምናሉ። ቢሆን እነዚህ እንቅፋቶች ቤተክርስቲያን የሕሊና ምርመራን በማድረግ ወደ ትክክለኛው መንገድ ለመመለስ የምታደርገውን ጥረት ሊያደናቅፍ እንደማይችል የቀድሞ ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ቅዱስ ዮሐንስ ጳውሎስ አስገንዝበዋል። ባለፉት የቤተክርስቲያን ታሪኮች ተጠቅሰው ከምናገኛቸው የአመጽ ተግባራት መካከል አንዳንዶቹ እውነት እንዳይሰወር ተብሎ የተፈጸሙ ቢሆንም አንዳንድ አመጾች ጠላትነት እንዲያድግ ያደረጉ በመሆናቸው በ2000 ዓ. ም. ኢዮቤልዩ በቤተክርስቲያን ውስጥ ለተከሰቱት ልዩነቶች እና ለተፈጸሙት የአመጽ ተግባራት ምሕረት የተጠየቀበት ዓመት እንደነበር ይታወሳል። ቀጥሎ ባሉት ዓመታት፣ እንደ ጎርጎሮሳዊያኑ የቀን አቆጣጠር 2004 ዓ. ም. በመንፈስ ቅዱስ የምትመራ ቤተክርስቲያን፣ ለሕሊና በመገዛት፣ በቅዱስ ወንጌል በመመራት፣ ገጽታዋን ከሚያበላሹ የአመጽ እና የጥላቻ መንገዶች ለመራቅ ጠንካራ ፍላጎት ያደረባት መሆኑን ቅዱስ ዮሐንስ ጳውሎስ ዳግማዊ በይፋ መግለጻቸው ይታወሳል።

የጋሊሌዮ ጉዳይ በተመለከተ፣

የካቶሊክ እምነት ተከታይ የነበረው ጣሊያናዊ ተመራማሪ ጋሊሌዮ ጋሊሌዪን ያስታወሱት ቅዱስ ዮሐንስ ጳውሎስ ዳግማዊ፣ ከቤተክርስቲያን አባላት እና ከአንዳንድ ግለሰቦች በኩል የሚነሱ ሃሳቦችን ለውይይት ማቅረብ አስፈላጊ መሆኑን አስታውቀው፣ በየዘመኑ የሚነሱ ሃሳቦች የዘመኑን አስተሳሰስብ እና ግንዛቤን የተከተሉ በመሆናቸው፣ ምንም እንኳን የሰው ልጅ የማሰብ እና የማገናዘብ ችሎታው በጊዜው ባለው የባሕል እድገት ደረጃ መወሰኑን አስረድተው፣ ተመራማሪው ጋሊሌዮ ጋሊሌዪ፣ ትክክለኛ እውቀት ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ የሚመጣ፣ በአንድ ወቅት በተገኘ እውነት ብቻ ተውስኖ የሚቀር እንዳልሆነ መናገሩን አስታውሰዋል።

የነፃነት ጽንሰ-ሀሳብ እድገት፣

አዲስ ኪዳን መጽሐፍ ለውጥ እንዲደረግ ከማሳሰቡ በላይ ነጻነትም እንዲኖር የሚጠይቅ ሲሆን እነዚህ የነጻነት ጥያቄዎች ቀስ በቀስ የሚመጡ መሆናቸው ታውቋል። የቀድሞ ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ቦኒፋቾ 8ኛ እንደ ጎርጎሮሳዊያኑ የቀን አቆጣጠር 1302 ዓ. ም. “በአንድ መሪ የበላይነት አምናለሁ” በማለት ይፋ ባደረጉት የማስታወሻ ጽሑፋቸው፣ መንፈሳዊ ስልጣን በተቀሩት የስልጣን ዓይነቶች ላይ የበላይነት እንዳለው መናገራቸው ይታወሳል። ይህም ቢሆን የዘመናቸውን የአስተሳሰብ ደርጃ የሚገልጽ እንጂ እውነትነት ያለው ሆኖ አልተገኘም።  ከ700 ዓምታት በኋላ ቅዱስ ዮሐንስ ጳውሎስ ዳግማዊ በአውሮፓ ፓርላማ ፊት ቀርበው ባደረጉት ንግግራቸው፥ የመካከለኛው ዘመን ክርስትና በእምነት እና በማኅበራዊ ሕይወት መካከል ያለውን ግንኙነት ለይቶ የሚያውቅ አልነበረም በማለት መናገራቸው ይታወሳል። ለዚህም ዋና ማስረጃ የሚሆነው አንዳንድ እምነቶች እውነት በትክክል አልተገልጸም በማለት ራሳቸውን ከተቀረው ማህበራዊ አንድነት እየለዩ መምጣታቸው ነው በማለት አስረድተዋል። በእምነት ተከታዮች መካከል የሚታዩ ልዩነቶችን በማስወገድ ወደ አንድነት እና ወንድማማችነት መንገድ የሚመሩ ሐዋርያዊ አስተምህሮች ከቀድሞ ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ቅዱስ ጳውሎስ ዳግማዊ በኋላ በተሰየሙ ርዕሣነ ሊቃነ ጳጳሳት በኩል ሲገለጹ መቆየታቸው ይታወሳል።

ልዩነቶችን ከመቼ ጀምሮ ማቆም ያስፈልጋል?

“የእግዚአብሔር ቤተክርስቲያን” የሚለው ሐዋርያዊ መልዕክት፣ በሁለተኛው የቫቲካን ጉባኤ ላይ ቅሬታቸውን ለሚገልጹ አጥባቂ የቤተክርስቲያን እንቅስቃሴዎች፣ “ሁለተኛው የቫቲካን ጉባኤ አዲስ ቤተክርስቲያን ለማቋቋም ያቀደ ጉባኤ ነው” በማለት እንደ ጎርጎሮሳዊያኑ የቀን አቆጣጠር 1962 ዓ. ም. እና ከዛም አስቀድሞ በ1870 ዓ. ም. ድምጻቸውን ማሰማታቸው የሚታወስ ነው። እነዚህን የመሳሰሉ ለቤተክርስቲያን እድገት እንቅፉትን ሆነው የቆዩ እንቅስቃሴዎች በየጊዜው መታየታቸው አልቀረም። የቀድሞ ር. ሊ. ጳ. ፒዮስ 9ኛ በሐዋርያዊ አስተዳደር ዘመናቸው ማለትም እንደ ጎርጎሮሳዊያኑ የቀን አቆጣጠር 1854 ዓ. ም. አካባቢ፣ ቤተክርስቲያን ቅድስናቸውን ይፋ ካደረጉላቸው እንኳ ሳይቀር ተቃውሞ ይደርስባቸው እንደ ነበር ገልጸው፣ ተቀባይነት በሌላቸው ጥንታዊ ባሕሎች መመራት በአስራ ሁለተኛው ክፍለ ዘመን ላይ የማይጠቅም መሆኑን መናገራቸው ይታወሳል።

ኢየሱስ ያዘጋጀው መንገድ፣

ኢየሱስ ክርስቶስ “የሙሴን ሕግና የነቢያትን ትምህርት ለመሻር የመጣሁ አይምሰላችሁ፤ እኔ ፍጹም እንዲሆኑ ላደርጋቸው ምርጣሁ እንጂ ልሽራቸው አልመጣሁም” (ማቴ. 5፡17) በኋላ “ስለዚህ ከእነዚህ ትዕዛዞች አነስተኛ የሆነችውን አንዷን እንኳ የሚያፈርስ እና ሌሎችም ሰዎች እንዲህ እንዲየደርጉ የሚያስተምር ሰው በመንግሥተ ሰማይ አነስተኛ ይሆናል” (ማቴ. 5.19) ብሎ ማስተማሩን እናገኛለን። በሌላ ወገን ከሁለት ሺህ ዓመት በፊት በሕዝቡ ዘንድ ዘንድ ይከበሩ የነበሩ የሙሴ ሕጎች በሐዋርያት በኩል ተቃውሞ እንደገጠማቸው፣ ከእነዚህም መካከል ግርዛት እና የሰንበት አከባበር የሚጠቀሱ ናቸው። ለወንጌል ምስክርነት ያለን ተነሳሽነት እና ፍቅር ሁል ጊዜ በእምነታችን ውስጥ ዋጋን ሊያስከፍል የሚችል ቢሆንም ዘለዓለማዊው እግዚአብሔር ለቃሉ ምስክርነት ያቆመን መሆኑን በመገንዘብ፣ የተሟላ ሕግ የሚገኝበትን ሰማያዊውን ጥበብ በመሻት፣ ቀራጮች እና ፈሪሳዊያን በሚፈጽሙት የጭቆና ተግባር ላይ የበላይነትን በሚቀዳጅ ፍትሃዊ መንገድ በመጓዝ፣ የመንግሥተ ሰማይን ምስጢር ጠንቅቆ የሚያውቅ የሕግ መዝገብ ላይ የጋራ ውይይቶችን በማድረግ የክርስቲያኖች አንድነት እና ወንድማማችነት ለማሳደግ የሚያግዙ አዲሱን እና አሮጌውን ሕጎች ማወቅ እንደሚያስፈልግ ሃሳብ ቀርቧል።             

23 June 2020, 17:52