ፈልግ

በዩክሬን፣ በበርዲቺቭ ከተማ የሚገኘው የማሪያን ቤተ መቅደስ በዩክሬን፣ በበርዲቺቭ ከተማ የሚገኘው የማሪያን ቤተ መቅደስ 

ብጹእ ካርዲናል ፓሮሊን በሃምሌ ወር ወደ ዩክሬን እንደሚጓዙ ተነገረ

የቫቲካን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር የሆኑት ብጹእ ካርዲናል ፓሮሊን በዩክሬን የላቲን ሥርዓት ተከታይ የሆኑ ካቶሊኮች የሚያደርጉትን ዓመታው መንፈሳዊ ጉዞ መጠናቀቅን በማስመልከት ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳትን ወክለው በስፍራው እንደሚገኙ ተገልጿል።

  አቅራቢ ዘላለም ኃይሉ ፥ አዲስ አበባ

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቺስኮስ የቫቲካን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር የሆኑትን ብፁዕ ካርዲናል ፒዬትሮ ፓሮሊንን ጳጳሳዊ መልዕክተኛ አድርገው የሾሟቸው ሲሆን፥ የላቲን ሥርዓት ተከታይ የሆኑ የዩክሬን ካቶሊኮች በሰሜናዊ ዩክሬን በምትገኘው ታሪካዊዋ በርዲቺቭ ከተማ በሚገኘው የእመቤታችን የቀርሜሎስ ብሄራዊ ቤተ መቅደስ በሚያደርጉት ዓመታዊ መንፈሳዊ ጉዞ ላይ እንደሚገኙ ተነግሯል።

የቅድስት መንበር የዜና ማሰራጫ ጽ/ቤት ያወጣው መግለጫ እንደሚያሳየው፣ ብፁዕ ካርዲናል ፓሮሊን ሃምሌ 21 ቀን 2016 ዓ.ም. በሚካሄደው የዓመታዊ መንፈሳዊ ጉዞ የማጠቃለያ ሥርዓተ ቅዳሴን እንደሚመሩ አስታውቋል።

የቤርዲቺቭ ቤተመቅደስ

በየዓመቱ በግምት 4000 የሚሆኑ መንፈሳዊ ተጓዦች በዛይቶሚር ክልል ውስጥ ወደሚገኘው በዩክሬን የላቲን ሥርዓት ተከታይ የሆነው ትልቁ የካቶሊክ የቤርዲቺቭ ቤተ መቅደስ የአምላክ እናት ተምሳሌት የሆነውን ቤተመቅደስ ለማክበር ወደስፍራው ይጓዛሉ።

የቀርሜሎስ ካህናት የቤተመቅደሱን እና የገዳሙን ስራ እና እንክብካቤን የሚመሩ ሲሆን፥ በ17ኛው ክፍለ ዘመን በተመሰረተው በዚህ ታሪካዊ ቦታ ላይ በሶቪየት የግዛት ዘመን የደረሰውን ጉዳት ለመጠገን ካህናቱ ብዙ ስራዎችን ሰርተዋል።

ከስር ያለውን የቤተክርስቲያኑ የምድር ቤት ክፍል የቀርሜሎስ ካህናት በሩሲያ የአየር ድብደባ ወቅት የአካባቢው ህዝብ ከቦምብ ጥቃት ራሱን እንዲከላከል ከፍተውታል።
 

20 May 2024, 16:57