ፈልግ

2019.06.29 Papa Francesco celebra la Santa Messa Pietro e Paolo

በቅዱስ ጴጥሮስ ባሲሊካ ውስጥ በሚገኘው መንበረ ታቦት ላይ ያለው ድባብ ሊታደስ መሆኑ ተገለጸ!

እ.አ.አ ከ2025 የኢዮቤልዩ አመት በፊት፣ የኮሎምበስ ፈረሰኞች ማሕበር በቅዱስ ጴጥሮስ ባዚሊካ ውስጥ የሚገኘውን ዋና የመስዋዕተ ቅዳሴ መሠዊያ መንበረ ታቦት ላይ ያለው ድባብ የሚደረግለትን የአስር ወራት እድሳት በገንዘብ እንደሚደግፉ ተገለጸ።

የእዚህ ዝግጅት አቅራቢ መብራቱ ኃ/ጊዮርጊስ ቫቲካን

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ በጂያን ሎሬንዞ በርኒኒ ባሮክ ድንቅ ሥራ ከተጀመረ ከ400 ዓመታት ገደማ በኋላ በመንበረ ታቦቱ ላይ የሚገኘው ድባብ የቅዱስ ጴጥሮስ ቤተ ክርስቲያን የመጀመሪያ “ስልታዊ እና የተሟላ” እድሳት ፈቅደዋል።

“አስቸጋሪው እና አስፈላጊው” እድሳት “ትልቅ ተምሳሌታዊ እሴት አለው” በማለት የባዚሊካ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ ካርዲናል ማውሮ ጋምቤቲ ሥራውን በማስተዋወቅ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ እንዳሉት በመንበረ ታቦቱ ላይ የሚገኘው ድባብ በትልቁ መንበረ ታቦት ሥር የሚገኘውን “የሐዋርያው ጴጥሮስን የመካነ መቃብር ቦታ በሚያስደንቅ ሁኔታ ያሳያል” ብለዋል።

ለአንድነት እና በጎ አድራጎት ተግባር ቁርጠኝነት

“በቅጽበት የሚታወቅ እና የሚደነቅ” በመንበረ ታቦቱ ላይ የሚገኘው ድባብ እድሳት የሚከናወነው እ.አ.አ በ1882 በብፁዕ አቡነ ሚካኤል ማክጊቪኒ የተመሰረተው ዓለም አቀፋዊ የካቶሊክ ወንድማማችነት ሥርዓት በሆነው የኮሎምበስ ፈረሰኞች ማሕበር ድጋፍ የሚደረግ እድሳት ነው።

በተጨማሪም በጋዜጣዊ መግለጫው ላይ፣ የኮሎንቦስ ፈረሰኞች ማሕበር ጠቅላይ ዋና ጸኃፊ የሆኑት ፓትሪክ ኬሊ እንደተናገሩት “ቅዱስ የሆነ ጥበብ ነጠላ ታላቅ ቅርስ” መልሶ ማቋቋም ከፈረሰኞቹ “ለቤተክርስቲያን እና በተለይም ከቅዱስ ጴጥሮስ ተተኪዎች ጋር ያለው የአገልግሎት ታሪክ እና ሕብረት” ጋር ይዛመዳል ሲሉ ተናግረዋል።

“ለዚህ እድሳት ያለን ቁርጠኝነት ለዋነኛ የበጎ አድራጎት እና የአንድነት መርሆቻችን ያለንን ዘላቂ ቃል ያንፀባርቃል” ብለዋል፣ “በእርግጥ ጥቂት የጥበብ ስራዎች ይህንን አንድነት በግልፅ እና በፍጥነት ይገልጻሉ ሲሉ አክለው ተናግረዋል።

ወደ ኢዮቤልዩ ወደፊት በመመልከት ላይ

ብፁዕ ካርዲናል ጋምቤቲ በበኩላቸው፣ እድሳቱ “በጥንቃቄ እና ለቅርሱ ባለው አሳቢነት” የተነሳሳ መሆኑን እና የኢዮቤልዩ ዓመት መክፈቻ ላይ በታህሳስ 2024 ይጠናቀቃል ተብሎ ይጠበቃል ሲሉ ተናግረዋል።

ካርዲናሉ እንዳብራሩት የመንበረ ታቦቱ ድባብ መልሶ ማቋቋም በተለይ በሰነዶች፣ በሎጂስቲክስ፣ በማህደር ጥናት፣ በሳይንሳዊ ምርምሮች፣ በመወጣጫ መዋቅሮች አደረጃጀት፣ የግንባታ ቦታው አደረጃጀት ከእንቅስቃሴው ጋር በተያያዙ ጉዳዮች ምክንያት በተለይ ውስብስብ እና ግልጽ በሆነ መልኩ ተለይቶ ይታወቃል። እና የባዚሊካ የአምልኮ ሕይወት፣ እና በእርግጥ፣ ጥበቃ ላይ ያተኮሩ የተለያዩ ጣልቃገብነቶች አስፈላጊነት ላይ ትኩረት ተሰጥቶ እንደሚሰራ አክለው ገልጸዋል።

በተለይም በሕማማት ሳምንት እና በፋሲካ በዓል ወቅት የተለያዩ የቫቲካን ጽ/ቤቶች በመተባበር “በአከባበሩ ላይ ለሚደረገው መደበኛ ሥነ-ሥርዓት እጅግ ተስማሚ የሆኑ መፍትሄዎችን በማፈላለግ በተሃድሶው ወቅት የጳጳሳዊ ሥርዓተ አምልኮዎች መካሄዳቸውን እንደሚቀጥሉም አክለው ገልጸዋል።

የመልሶ ማቋቋም እቅድ

የመንበረ ታቦቱ ድባብ እድሳት በጊዜያዊ ስራ እና እቅድ በመጀመር እና በቅድመ እና በቦታው ላይ ምርመራ እና ሰነዶችን በማዘጋጀት በሶስት ደረጃዎች ይከናወናል።

በሦስተኛው ደረጃ የማገገሚያ ሥራ የብረት (ነሐስ እና ብረት) ንጣፎችን፣ የድንጋይ ንጣፎችን እና በመንበረ ታቦቱ ላይ ያለው የድባብ የእንጨት መዋቅሮችን ወደነበረበት መመለስ ላይ ያተኩራል።

ፕሮጀክቱ 700,000 ዩሮ (በግምት 768,000 ዶላር) ይፈጃል ተብሎ የሚጠበቅ ሲሆን ሙሉ በሙሉ በኮሎምበስ የፈረሰኞች ማሕበር የገንዘብ ድጋፍ እየተደረገለት ነው ያሉት ካርዲናል ጋምቤቲ “ለቤተክርስቲያኗ እና ለጳጳሱ በሚደረግ የአገልግሎት መንፈስ” የሚከናወን ተግባር ነው ብለዋል።

12 January 2024, 16:27