ብጹዕ ካርዲናል ፓሮሊን፣ በቅድሚያ የሰውን ሕይወት መታደግ እንደሚያስፈልግ አሳሰቡ
የዚህ ዝግጅት አቅራቢ ዮሐንስ መኰንን - ቫቲካን
ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ፣ እሑድ የካቲት 26/2015 ዓ. ም. በቅዱስ ጴጥሮስ አደባባይ ከተሰበሰቡት ምዕመናን ጋር የመልአከ እግዚአብሔር ጸሎት ባቀረቡበት ወቅት፥ “ሰዎች የተሻለ ሕይወት ለመኖር ተስፋ በማድረግ የሚያደርጉት ጉዞ ወደ ሞት መለወጥ የለበትም” በማለት፣ ለስደተኞች የሚገባውን አቀባበል በማስመልከት በሮም ከተማ በተዘጋጀ ስብሰባ መክፈቻ ላይ መልዕክት አስተላልፈዋል።
የቅዱስነታቸውን መልዕክት ለስብሰባው ተካፋዮች መንባብ ያቀረቡት የቅድስር መንበር ዋና ጸሐፊ ብጽዕ ካርዲናል ፒዬትሮ ፓሮሊን ሲሆኑ፣ ቅዱስነታቸው በዚህ መልዕክታቸው፣ “የመልካም አቀባበል መንፈስን ለማጎልበት የሚያግዝ አዲስ ቁርጠኝነት እንዲኖር መመኘታቸውን፣ ብጹዕ ካርዲናል ፓሮሊን ገልጸዋል። በሕዝቦች መካከል ሰላምን እና ወንድማማችነትን ማጎልበት እንደሚገባ ቅዱስነታቸው አሳስበው፣ በተጨማሪም የብዙ ስደተኛ ወንድሞች እና እህቶች መኖር ለሰው ልጅ ዕድገት፣ በባሕሎች እና በሃይማኖቶች መካከል ለሚኖር ግንኙነት እና የጋራ ውይይት ዕድል ማመቻቸትን እንደሚያበረታታ ገልጸዋል።
ከቤተ ክርስቲያን የሚሰጠውን መመሪያ ግምት ውስጥ ማስገባት
በስደተኞች የተስፋ ጉዞ ላይ የሚደርስ ተጨማሪ እልቂትን ማስወገድ በጣም አስፈላጊ ነው ያሉት ብጹዕ ካርዲናል ፓሮሊን፣ ስደት ደኅንነቱ የተጠበቀ እንዲሆን እና መደበኛ ማድረግ እንደሚያስፈልግ አሳስበው፣ ፍርሃት በተቆጣጠረው ማኅበረሰብ ውስጥ ከሁሉም በላይ አዎንታዊ አመለካከት እንዲኖር ማድረግ ያስፈልጋል ብለዋል። ብጹዕነታቸው አክለውም፣ “ስደተኞች የመጡበትን ሁኔታ እና የሚገኙበትን ሁኔታ ግምት ውስጥ በማስገባት አስፈላጊው አቀባበል ሊደረግላቸው ያስፈልጋል" ብለዋል።
በቅድሚያ የሰው ልጅ ሕይወት ማዳን ያስፈልጋል
ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ፣ እሑድ የካቲት 26/2015 ዓ. ም. ባስተላለፉት መልዕክት፣ ሕገ-ወጥ የሰዎች አዘዋዋሪ ወንጀለኞችን ማስቆም እንደሚገባ ማሳሰባቸውን ያስታወሱት ብጹዕ ካርዲናል ፓሮሊን፣ የሰው ልጆችን በሕገ ወጥ መንገድ ከቦታ ወደ ቦታ በማዘዋወር ትርፋማ የሚሆኑትን ከማውገዝ በተጨማሪ ድርጊቱን ማስቆም እንደሚገባም ጠይቀዋል። ስደተኞችን ባሕር ላይ ከሚደርስ የሞት አደጋ ማዳን ሥራን በተመለከተ የጣሊያን መንግሥት ከነፍስ አድን መንግሥታዊ ካልሆኑ ድርጅቶች ጋር የሚያወጣው አዲስ ደንብ እንዳለ የገለጹት ካርዲናል ፓሮሊን፣ "ከሁሉ በፊት ሰዎችን ከሞት አደጋ ማዳን እና ሕይወት እንዲጠፋ አለመፍቀድ" የሚለው የቅድስት መንበር መርህ ተግባራዊ እንዲሆን አሳስበዋል።
ፍርሃት እንግዳን የመቀበል ታላቅ ጠላት ነው!
ብፁዕ ካርዲናል ፒዬትሮ ፓሮሊን በማጠቃለያ ንግግራቸው፣ የካቲት 19/2015 ዓ. ም. በጣሊያን የባሕር ዳርቻ የደረሰውን አሳዛኝ ክስተት በድጋሚ አስታውሰው፣ “ክስተቱ ለሕሊናችን ማስጠንቀቂያ እንጂ በግድ የለሽነት ወይም በፍርሃት የምናልፈው አይደለም” ብለዋል። "ፍርሃት እንግዳን የመቀበል ታላቅ ጠላት" በማለት ተናግረው፣ ፍርሃቱ ከሕዝብ የሚመነጭ በመሆኑ፣ የመንግሥት እና የተቋማት የፖለቲካ ምርጫ ሁኔታ መስተካከል ይኖርበታል" ብለዋል።