ፈልግ

ር.ሊ.ጳ ፍራንችስኮስ እግዚአብሔር አቅፎ ከኃጢአታችን ነፃ ያወጣናል ማለታቸው ተገለጸ!

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ ዘወትር እሁድ በቫቲካን በሚገኘው በቅዱስ ጴጥሮስ አደባባይ ለሚሰበሰቡ ምዕመናን በእለቱ በሚነበበው የቅዱስ ወንጌል ክፍል ላይ ተንተርሰው የቅዱስ ወንጌል አስተንትኖ እንደሚያደርጉ ይታወቃል። በእዚህ መሰረት ቅዱስነታቸው በመጋቢት 01/2016 ዓ.ም የጎርጎሮሳዊያኑን የቀን አቆጣጠር በሚከተሉ የካቶሊክ ቤተክርስቲያን ምዕመናን ዘንድ በተከበረው 4ኛ የዐብይ ጾም ሳምንት ላይ ባደረጉት የቅዱስ ወንጌል አስተንትኖ እግዚአብሔር አቅፎ ከኃጢአታችን ነፃ ያወጣናል ማለታቸው ተገልጿል።

የእዚህ ዝግጅት አቅራቢ መብራቱ ኃ/ጊዮርጊስ ቫቲካን

ክቡራን እና ክቡራት የዝግጅቶቻችን ተከታታዮች ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ በወቅቱ ያደረጉትን የቅዱስ ወንጌል አስተንትኖ ሙሉ ይዘቱን እንደሚከተለው አሰናድተነዋል፣ ተከታተሉን።

የተወደዳችሁ ወንድሞቼ እና እህቶቼ እንደምን አረፈዳችሁ!

በዚህ የዐብይ ጾም አራተኛ እሑድ (የጎርጎሮሳዊያኑን የቀን አቆጣጠር በሚከተሉ የካቶሊክ ቤተክርስቲያን ምዕመናን ዘንድ ማለት ነው) ላይ የተነበበው ቅዱስ ወንጌል የኒቆዲሞስን ምሳሌ ያቀርብልናል (ዮሐ. 3፡14-21)፣ ፈሪሳዊ፣ “የአይሁድ አለቃ” (ዮሐ 3፡1) የሆነ ሰው ነበር። ኢየሱስ ያደረጋቸውን ምልክቶች አይቶ ከእግዚአብሔር የተላከ መምህር መሆኑን እርሱ አወቆ ሌሎች ሰዎች እንዳያዩት በማሰብ በሌሊት ሊገናኘው ሄደ። ጌታ ተቀበለው፣ ከእርሱ ጋር ተነጋገረ እና አለምን ሊያድን እንጂ ሊፈርድ እንዳልመጣ ገለጠለት (ዮሐንስ 3፡17)። እስቲ በዚህ ላይ ቆም ብለን እናስብ፡ ኢየሱስ የመጣው ለማዳን እንጂ ለመኮነን አይደለም። ይህ ቆንጆ የሆነ ነገር ነው!

ብዙ ጊዜ በወንጌል ውስጥ ክርስቶስ የሚያገኛቸውን ሰዎች ሐሳብ ሲገልጽ፣ አንዳንድ ጊዜ እንደ ፈሪሳውያን ያሉ የሐሰት አመለካከቶቻቸውን ሲገልጥ እናያለን (ማቴ. 23፡27-32)፣ ወይም በሕይወታቸው መዛባት ላይ እንዲያስቡ፣ እንደ ሳምራዊቷ ሴት (ዮሐ. 4፡5-42) ያሉ ሰዎችን ሲገናኝ ሐሳባቸውን አንዲያጠሩ ያደርጋል። በፊቱ ምንም ምስጢር የለም፡ በልቡ ያነባቸዋል። ይህ ችሎታው ሊረብሽ ይችላል ምክንያቱም በመጥፎ ጥቅም ላይ ከዋለ ሰዎችን ይጎዳል፣ ምሕረት ለሌለው ፍርድ ያጋልጣል። በእርግጥም ማንም ሰው ፍጹም አይደለም፡ ሁላችንም ኃጢአተኞች ነን፣ ሁላችንም እንሳሳታለን፣ እና ጌታ ድክመታችንን እውቀቱን ተጠቅሞ እኛን ለመኮነን ቢጠቀም፣ ማንም ሊድን አይችልም ነበር።

ነገር ግን እንደዚህ አይደለም። በእርግጥም ሕይወታችንን ለመቀበል፣ ከኃጢአት ነፃ ለማውጣትና እኛን ለማዳን እንጂ፣ ጣቱን ወደ እኛ ለመቀሰር አይሻም። ኢየሱስ እኛን ለፍርድ ለማቅረብ ወይም እኛ ላይ ለመፍረድ ፍላጎት የለውም፣ ማናችንም እንዳንጠፋ ይፈልጋል። ጌታ በእያንዳንዳችን ላይ ያለው እይታ እኛን የሚያደነቁረን እና አስቸጋሪ ሁኔታዎች ውስጥ የሚከቱት ዓይነ ስውር ብርሃን ሳይሆን ረጋ ያለ የወዳጅ መብራት ብልጭታ ሲሆን ይህም በራሳችን ውስጥ ያለውን መልካም ነገር እንድናይ እና ክፉውን ዝንባሌዎቻችንን እንድንገነዘብ ይረዳናል፣ ስለዚህ በጸጋው ረዳትነት ተመልሰን እንድንፈወስ እድል ይሰጠናል።

ኢየሱስ ዓለምን ሊያድን እንጂ ሊፈርድ አልመጣም። ብዙውን ጊዜ ሌሎችን የምንኮን እኛን እናስቡ፣ ብዙ ጊዜ፣ መጥፎ መናገር፣ በሌሎች ላይ ሐሜት ለመፈለግ መሄድ እንወዳለን። ጌታ እኛን ሁላችንም ይህን መሐሪ እይታ እንዲሰጠን፣ እርሱ እኛን እንደሚመለከተን እኛም ሌሎችን እንድንመለከት እንጠይቀው።

እርስ በርሳችን መልካም ነገር እንድንመኝ ማርያም በአማልጅነቷ ትርዳን።

11 March 2024, 10:10