ፈልግ

በወታደራዊ ስልጠና ላይ የሚገኙ የዩክሬን ወታደሮች በወታደራዊ ስልጠና ላይ የሚገኙ የዩክሬን ወታደሮች  (ANSA)

ር. ሊ. ጳ. ፍራንችስኮስ፥ በጦርነት አስከፊ አደጋ በርካታ ወጣቶች እንደሚሞቱ ገለጹ

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ ረቡዕ መጋቢት 4/2016 ዓ. ም. ባቀረቡት ሳምንታዊ የጠቅላላ ትምህርተ ክርስቶስ አስተምህሮአቸው ማጠቃለያ ላይ ለታዳሚዎች ባሰሙት ንግግር፥ በአስጨናቂው የጦርነት አደጋ ለሚሰቃዩ ወገኖቻችን ጸሎት እንዲደረግላቸው ጠይቀው፥ በጦር ግንባር የነበረ አንድ ወታደር ከመሞቱ በፊት የላከላቸውን የመቁጠሪያ እና የቅዱስ ወንጌል ስጦታን ተቀብለዋል።

የዚህ ዝግጅት አቅራቢ ዮሐንስ መኰንን - ቫቲካን

የጦርነት አደጋን ለማሸነፍ ሲሉ በርካታ ወጣቶች እንደሚሞቱ፥ ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ ረቡዕ መጋቢት 4/2016 ዓ. ም. በቫቲካን ባቀረቡት ሳምንታዊ የጠቅላላ ትምህርተ ክርስቶስ አስተምህሮ ማጠቃለያ ላይ ገልጸው፥ በዚሁ ዕለቱም ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሆነው የተመረጡበትን አሥራ አንደኛውን ዓመታቸውን አክብረዋል።

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ ለጣልያንኛ ተናጋሪ ምዕመናን ሰላምታቸውን ባቀረቡበት ወቅት በጦርነት ለቆሰሉ ሰዎች እንዲጸልዩ ጥሪያቸውን በድጋሚ አቅርበዋል።

በጸሎት መጽናት

ምዕመናን በሙሉ በዚህ የዓብይ ጾም ወቅት በጦርነት ምክንያት አስከፊ አደጋ ለሚደርስባቸው ሰዎች በጸሎት መጽናት እንደሚገባ አጽንኦት በመስጠት ክርስቲያናዊ የትብብር ተግባራትን እንዲፈጽሙ አደራ ብለዋል።

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ ከመጋቢት 4/2016 ዓ. ም. ጀምሮ ላለፉት አሥራ ሁለት ወራት በዩክሬን የሚካሄደው ጦርነት እንዲቆም ከ 150 ጊዜ በላይ ጥሪ ማቅረባቸው፣ ከ 60 ጊዜ በላይ በመካከለኛው ምሥራቅ የተኩስ አቁም ስምምነት እንዲደረግ ጥሪ ማቅረባቸው ይታወሳል 

በጦርነት የተገደለ የአንድ ወጣት ወታደር መቁጠሪያ

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ ረቡዕ መጋቢት 4/2016 ዓ. ም. በቅዱስ ጴጥሮስ አደባባይ ለተሰበሰቡት ምዕመናን ባደረጉበት ንግግር፥ “በጦር ግንባር ከሞተ አንድ ወጣት ወታደር ተዘጋጅቶ የነበረውን የመቁጥሪያ እና የቅዱስ ወንጌል መጽሐፍ ስጦታ ማግኘታቸውን ገልጸዋል።

ሟቹ ወታደር መቁጠሪያን እና ቅዱስ ወንጌልን ይዞ ይጸልይ እንደ ነበር በማስታወስ፥ ዛሬ በርካታ ወጣቶች በጦር ሜዳ እንደሚሞቱ በማሰብ ምዕመናኑ በጸሎታቸው እንዲያስታውሷቸው ጠይቀዋል።

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ ለምዕመናኑ ያደረጉትን ንግግር ሲደመድሙ፥ ዘወትር ሽንፈትን የሚያከናንብ የጦርነት ዓመል የሚሸነፍበት ጸጋ እንዲሰጠን ወደ እግዚአብሔር እንጸልይ ብለዋል።

 

13 March 2024, 13:19