ፈልግ

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቺስኮስ አዲስ የተሾሙትን የኩዌት፣ የኒውዚላንድ፣ የማላዊ፣ የጊኒ፣ የስዊድን እና የቻድ አምባሳደሮችን ተቀብለው ሲያነጋግሩ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቺስኮስ አዲስ የተሾሙትን የኩዌት፣ የኒውዚላንድ፣ የማላዊ፣ የጊኒ፣ የስዊድን እና የቻድ አምባሳደሮችን ተቀብለው ሲያነጋግሩ  (VATICAN MEDIA Divisione Foto)

ር.ሊ.ጳጳሱ አዲስ ለተሾሙት አምባሳደሮች 'ኮፕ28' ወደፊት የሚያራምድ ታሪካዊ እርምጃ ይሆናል አሉ

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቺስኮስ በቅድስት መንበር አዲስ ዕውቅና የተሰጣቸውን ስድስት አምባሳደሮችን ባነጋገሩበት ወቅት ዱባይ እየተካሄደ በሚገኘው የኮፕ28 ጉባኤ ላይ የሚገኙ የዓለም መሪዎች የአየር ንብረት ለውጥን ለመግታት በተጨባጭ በሚወሰዱ እርምጃዎች ላይ ሊስማሙ እንደሚችሉ ያላቸውን ተስፋ ደግመው ገልፀዋል።

  አቅራቢ ዘላለም ኃይሉ ፥ አዲስ አበባ

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቺስኮስ ከተለያዩ ሃገራት በቅድስት መንበር በአምባሳደርነት ተሹመው የመጡትን ስድስት አዲስ አምባሳደሮች ያቀረቡትን የሹመት ደብዳቤ ተቀብለዋል። እነዚህም አምባሳደሮች ተሹመው የመጡት ከኩዌት፣ ኒውዚላንድ፣ ማላዊ፣ ጊኒ፣ ስዊድን እና ቻድ እንደሆነም ተገልጿል።

ሁለገብ ዲፕሎማሲ ለችግሮች ዓለም አቀፋዊ መፍትሄዎች ናቸው

ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ሐሙስ ዕለት ወደ ቫቲካን ተሹመው የመጡትን ዲፕሎማቶች ሲቀበሉ እንደተናገሩት፥ የሶስተኛው የዓለም ጦርነት ስጋት በማለት ደጋግመው በገለጹበት ወቅት ለዓለም ሰላም ያላቸውን ጠንካራ ፍላጎት በመግለፅ፥ በአየር ንብረት ለውጥ ምክንያት የጋራ ቤታችን የወደፊት ዕጣ ፈንታ ስጋት ላይ መውደቁን ከገለፁ በኋላ፥ በዚህ አውድ ውስጥ የዲፕሎማሲውን ወሳኝ አስፈላጊነት አፅንዖት ሰጥተው ተናግረዋል።

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳቱ በማከልም “የግጭቶቹን ዓለም አቀፋዊ ስፋት ግምት ውስጥ በማስገባት ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ በዲፕሎማሲው ሰላማዊ መንገድ ብዙ ጊዜ ለግጭቶቹ መንስኤ የሆኑትን ከባድ ኢፍትሃዊነትን ለመፍታት ዓለም አቀፍ መፍትሄዎችን ለመፈለግ ተገዳድሮታል” ብለዋል።

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቺስኮስ በቅርቡ ‘ላውዳቶ ዲየም’ ወይም ‘እግዚያብሄርን አወድሱት’ በሚለው ሃዋሪያዊ ደብዳቤያቸው ያቀረቡትን ሐዋርያዊ ማሳሰቢያ በማስታወስ፥ “ለሚከሰቱ ችግሮች ውጤታማ ምላሾችን ለመስጠት” እና “በአሁኑ ወቅት የአካባቢ፣ የሕዝብ ጤና፣ የባህልና የማኅበራዊ ለውጦችን ለመፍታት ዓለም አቀፍ ዘዴዎችን ለመንደፍ የባለብዙ ወገን ዲፕሎማሲን እንደገና ማዋቀር አስፈላጊ መሆኑን በድጋሚ አረጋግጠዋል።

“ዲፕሎማሲውን በትዕግሥት ማከናወን ግጭቶችን ለመከላከልና ለመፍታት ጥረት ማድረግ ብቻ ሳይሆን የዓለም ሕዝቦችን ሰላም በጋራ የመኖርና ሰብዓዊ ዕድገትን ለማጠናከር፣ ሰብዓዊ ክብርን በማሳደግ፣ የእያንዳንዱ ወንዶችን፣ ሴቶችን እና ህጻናትን የማይገሰስ መብቶችን በማስጠበቅ፣ የተቀናጀ ኢኮኖሚያዊ እና ሰብአዊ ልማት ሞዴሎችን ማስተዋወቅ ተገቢ ነው” ብለዋል ብጹእነታቸው።

የአየር ንብረት ለውጥ ተፅእኖ በጣም ተጋላጭ በሆኑ ሰዎች ላይ

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቺስኮስ በአየር ንብረት ለውጥ እና በተፈጥሮአዊ በሆኑ አካባቢዎች ላይ በደረሰው ውድመት ላይ ያተኮሩ ሲሆን ይህም ቅድስት መንበር በጣም ተጋላጭ በሆኑ ሰዎች ላይ የሚያሳድረው ተጽእኖ ምን ያክል እንደሚያሳስባት አመላክተዋል።

ከዚህ ጋር በተያያዘ በተባበሩት መንግስታት የአየር ንብረት ለውጥ ኮንፈረንስ ‘ኮፕ28’ ላይ ባደረጉት ንግግር በዱባይ የተሰበሰቡት የዓለም መሪዎች “ለመጪው ትውልድ የበለጠ እና ሙሉ ለሙሉ ፈጣሪያችን እንድንከባከብና ጥበቃ እንድናረግላት አደራ የሰጠን ፍሬያማ ገነት የምትመስል ዓለም ለማስረከብ ተጨባጭ እርምጃዎችን በመውሰድ እንደሚተባበሩ ያላቸውን ተስፋ በድጋሚ ተናግሯል።

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳስ ፍራንቺስኮስ በመጨረሻም “የኮፕ28 ውሳኔዎች ለእነዚህ ግልጽ እና ወቅታዊ ሁለንተናዊ የጋራ ጥቅም ስጋቶች በጥበብ እና አርቆ አሳቢነት ምላሽ ለመስጠት የሚወሰዱ ታሪካዊ እርምጃዎችን እንደሚወክሉ እመኛለሁ” ካሉ በኋላ፥ “የሁላችንም የወደፊት እጣ ፈንታ አሁን በምንመርጠው እና በምንወስዳቸው እርምጃዎች ላይ የተመሰረተ ነው” ሲሉ አረጋግጠዋል።
 

08 December 2023, 14:24