ር. ሊ. ጳ. ፍራንችስኮስ ከፖላንድ ከመጡ ወጣት ናጋዲያን ጋር በቫቲካን መገናኘታቸው ተነገረ
የዚህ ዝግጅት አቅራቢ ዮሐንስ መኰንን - ቫቲካን
ከበርካታ ቤተሰቦች ጋር ወደ ሮም የመጡ ወደ 150 የሚጠጉ የፖላንድ ነጋዲያን ሰኞ ሐምሌ 10/2015 ዓ. ም. ጠዋት ላይ ከርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ ጋር ተገናኝተዋል። ነጋዲያኑ ወደ ሮም የደረሱት ሐምሌ 8/2015 ዓ. ም. ሲሆን ዓላማቸውም የብርሃን እና የሕይወት ማኅበረሰብ ወይም በስፋት “የህያው ቤተ ክርስቲያን ምንጭ” በመባል የሚታወቀው የፖላንድ ትልቁ የቤተ ክርስቲያን እንቅስቃሴ ያዘጋጀውን ሱባኤ ለመካፈል እንደሆነ ታውቋል። ሱባኤውን የሚመሩት ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ በቅርቡ ለካርዲናልነት ማዕረግ ያጯቸው እና በፖላንድ የውዥ ከተማ ሊቀ ጳጳሳ ብጹዕ አቡነ ግሬጎርስ ሪስ እንደሆኑ ታውቋል።
ወጣቶቹ እና ቤተሰቦች ከዚህ በፊት ዓመቱን በሙሉ በየቁምስናዎቻቸው ክርስቲያናዊ ስልጠናዎችን የተከታተሉ እንደሆኑ ተነግሯል። ምዕመናኑ ከፖላንድ ተነስተው ወደ ሮም ያደረጉት ንግደት የተደራጀ የሱባኤ ጊዜን የሚወስድ እንደሚሆን ሲነግር ይህም አብዛኛውን ጊዜ ከተለያዩ የፖላንድ ሀገረ ስብከቶች የሚመጡ ምዕመናንን የሚያሳትፍ እንደሆነ ታውቋል። በፖላንድ የብርሃን እና የሕይወት ማኅበረሰብን የመሠረቱት በኮሚኒስት አገዛዝ እንደ ጎርጎሮሳውያኑ በ1987 ዓ. ም. በደኅንነት ኃይሎች የተገደሉት አባ ፍራንቺሴክ ብላቺኒስኪ እንደነበሩ ይታወሳል።
የጸሎት እና የክርስትና ሕይወት መንገድ ፍለጋ
የፖላንድ ምዕመናን ወደ ሮም የሚያደርጉት ንግደት እና ከርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ጋር የሚያደርጉት ውይይት ወጣቶቹ እና ቤተሰቦች ባላቸው ሦስት የሱባኤ ደረጃዎች መካከል አስፈላጊዎች እንደሆኑ ታውቋል። የሱባኤው ተሳታፊዎች በምዕመናን የክርስትና ሕይወት ውስጥ መንገድን በሚፈልጉበት ወቅት የቤተ ክርስቲያን ምስጢርን በልዩነት መካከል እንዲለማመዱ ተጋብዘዋል።
የሱባኤው ተካፋዮች ሥነ-ሥርዓቱን በመካፈል የተለያዩ የጸሎት ዓይነቶችን፣ ወጎችን እና ወንድማማችነትን የሚማሩ ሲሆን በተጨማሪም ሮም ውስጥ የሚገኙ የተለያዩ ቅዱስ ሥፍራዎችን በመጎብኘት የክርስትና ታሪክ ዕውቀታቸውን እንደሚያሳድጉ ታውቋል።