ፈልግ

ር. ሊ. ጳ. ፍራንችስኮስ የጋናውን ፕሬዝዳንት አቶ አኩፎ-አዶን በቫቲካን ሲቀበሉ ር. ሊ. ጳ. ፍራንችስኮስ የጋናውን ፕሬዝዳንት አቶ አኩፎ-አዶን በቫቲካን ሲቀበሉ  (Vatican Media)

ር. ሊ. ጳ. ፍራንችስኮስ የጋናውን ፕሬዝዳንት አቶ አኩፎ-አዶን በቫቲካን ተቀብለው አነጋገሩ

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ ከጋናው ፕሬዝዳንት አቶ ናና አዶ አኩፎ-አዶ ጋር ቅዳሜ ሐምሌ 15/2015 ዓ. ም. በቫቲካን ተገናኝተው ተነጋግረዋል። ፕሬዝዳንቱ ከቅዱስነታቸው ጋር ከተገናኙ በኋላ ከቅድስት መንበር ዋና ጸሐፊ ከሆኑት ብጹዕ ካርዲናል ፔዬትሮ ፓሮሊን ጋርም ተገናኝተው በትምህርት እና በጤና አጠባበቅ መስኮች፣ ስለ ዓለም አቀፍ ሰላም እና የጸጥታ ጉዳዮች እንዲሁም በምዕራብ አፍሪካ በሚደረግ የጋራ ጥረት ላይ ተነጋግረዋል።

የዚህ ዝግጅት አቅራቢ ዮሐንስ መኰንን - ቫቲካን

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ ከጋና ሪፐብሊክ ፕሬዝዳንት አቶ ናና አዶ አኩፎ አዶ ጋር ቅዳሜ ሐምሌ 15/2015 ዓ. ም. ቫቲካን ውስጥ በጳውሎስ ስድስተኛ አዳራሽ ውስጥ መገናኘታቸውን የቅድስት መንበር መግለጫ ክፍል አስታውቋል። ፕሬዝዳንት ናና አዶ አኩፎ አዶ ከርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ ጋር ከተገናኙ በኋላ ከቅድስት መንበር ዋና ጸሐፊ ብጹዕ ካርዲናል ፒዬትሮ ፓሮሊን እና በቅድስት መንበር የመንግሥታት እና ዓለም አቀፍ ድርጅቶች ግንኙነት ጽሕፈት ቤት ሃላፊ ከሆኑት ሊቀ ጳጳስ አብነ ፖል ሪቻርድ ጋላገርን ጋር ተገናኝተው መነጋገራቸውን መግለጫ ክፍሉ አስታውቋል። ንግግራቸውም በቅድስት መንበር እና በጋና መንግሥት መካከል ባለው መልካም ግንኙነት ላይ ያተኮረ እንደነበር ተገልጿል።

ውይይታቸው በዋናነት በጋና ካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን እና በመንግሥት መካከል ያለውን ትብብር ለማሳደግ ያተኮረ ሲሆን፥ በተለይም በትምህርት እና በጤና አጠባበቅ መስክ ላይ ከመነጋገራቸው በተጨማሪ በጋና ፖለቲካዊ እና ማኅበራዊ እና ኤኮኖሚያዊ ሁኔታዎች ላይም መወያየታቸው ተነግሯል። ከሰላም ጋር በተያያዙ ጉዳዮችም ችግሮችን በዓለም አቀፍ ደረጃ መፍታት እና በምዕራብ አፍሪካ ሀገራት የፀጥታ ሁኔታን ለማሻሻል ትኩረት መስጠት እንደሚገባ እና ሌሎች ወቅታዊ ዓለም አቀፍ ጉዳዮችም ተዳሰዋል።

22 July 2023, 15:50