ር. ሊ. ጳ ፍራንችስኮስ፣ በኮንጎ ኪንሻሳ እና ደቡብ ሱዳን ሐዋርያዊ ጉብኝት እንደሚያደርጉ ተነገረ
የዚህ ዝግጅት አቅራቢ ዮሐንስ መኰንን - ቫቲካን
ለዚህ ዓለም አቀፍ ሐዋርያዊ ጉብኝት የወጣው መርሃ ግብር እንዳመለከተው፣ ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ በኮንጎ ዴሞክራሲዊት ሪፓብሊክ እና በደቡብ ሱዳን የሚያደርጉት ዓለም አቀፍ ሐዋርያዊ ጉብኝት ከጥር 23 - 28/2015 ዓ. ም. ድረስ መሆኑን ገልጿል። ር. ሊ. ጳ ፍራንችስኮስ አምና በበጋ ወራት በእነዚህ አገራት ሊያደርጉት የነበረው ሐዋርያዊ ጉብኝት በጤና ምክንያት ለሌላ ጊዜ መተላለፉ ይታወሳል።
ር. ሊ. ጳ ፍራንችስኮስ በኮንጎ ዴሞክራሲዊት ሪፓብሊክ እና በደቡብ ሱዳን ከጥር 23 - 28/2015 ዓ. ም. ድረስ ሐዋርያዊ ጉብኝት እንደሚያደርጉ የቅድስት መንበር መግለጫ ክፍል አስታውቆ፣ ቅዱስነታቸው ከሁለቱ አገራት መሪዎች እና ከብጹዓን ጳጳሳት የተለከላቸውን ግብዣ በደስታ መቀበላቸውን መግለጫ ክፍሉ አክሎ አስታውቋል።
ቅዱስነታቸው በኮንጎ ዴሞክራሲዊት ሪፓብሊክ ከጥር 23-26/2015 ዓ. ም. እና በደቡብ ሱዳን ከጥር 26-28/2015 ዓ. ም. ድረስ የክርስቲያኖችን አንድነት እና ሰላም ለማሳደግ የሚካሄደውን ሐዋርያዊ ንግደት ከርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ ጋር የሚያደርጉት በእንግሊዝ የካንተርበሪው ሊቀ ጳጳስ አቡነ ጀስቲን ዌልቢ እና የስኮትላንድ ቤተ ክርስቲያን ጠቅላላ ጉባኤ መሪ ክቡር ዶ/ር ያን ግሪንሺልድስ መሆናቸውን መግለጫ ክፍሉ አስታውቋል።
የርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ ሐዋርያዊ ጉብኝት ዋና ዋና ነጥቦች፣ በኮንጎ ዴሞክራሲያዊት ሪፐብሊክ ምሥራቃዊ ክፍል በጦርነት የተጎዱ ወገኖችን መገብኘት፣ እንዲሁም በደቡብ ሱዳን የሚገኙ የአገር ውስጥ ተፈናቃዮችን መጎብኝት እና ከልዩ ልዩ አብያተ ክርስቲያናት ጋር የኅብረት ጸሎት ማድረግን የሚያካትት መሆኑ ታውቋል።
የቅድስት መንበር መግለጫ ክፍሉ ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ በኮንጎ ዲሞክራሲያዊት ሪፓብሊክ እና በደቡብ ሱዳን ለክርስቲያኖች አንድነትና ሰላም የሚያደርጉትን ሐዋርያዊ ጉብኝትን ይፋ ባደረገበት ወቅት የቅዱስነታቸውን ሐዋርያዊ ጉብኝት የተመለከተ ጠቅላላ መርሃ ግብር ይፋ ማድረጉ ታውቋል።