ር. ሊ. ጳ ፍራንችስኮስ፣ ከሐዋርያዊ ጉብኝታቸው ተመልሰው ለእመቤታችን ማርያም ምስጋና አቀረቡ
የዚህ ዝግጅት አቅራቢ ዮሐንስ መኰንን - ቫቲካን
ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ፣ ወደ ሮም ከደረሱ በኋላ በከተማው በሚገኝ የእመቤታችን ማርያም ታላቁ ባዚሊካ ደርሰው፣ በሁለቱ አገራት ላደረጉት ሐዋርያዊ ጉብኝት ድጋፍ እና ጠባቂ ለሆነቻቸው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ምስጋና አቅርበው ወደ ቫቲካን በሰላም መመለሳቸውን የቅድስት መንበር ጋዜጣዊ መግለጫ ክፍሉ አክሎ አስታውቋል።
ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ በግሪክ ሐዋርያዊ ጉብኝት ሲያደርጉ ያሁኑ ለሁለተኛ ጊዜ ሲሆን የመጀመሪያውን እ. አ. አ በ2016 ዓ. ም. ማድረጋቸው የሚታወስ ነው። በግሪክ ባደረጉት የመጀመሪያ ሐዋርያዊ ጉብኝታቸው ወቅት በሌስቦ ደሴት የሚገኙ በሺህ ዎች የሚቆጠሩ ስደተኞችን እና ጥገኝነት ጠያቂዎችንም መጎበኙታቸው ይታወሳል። በዚሁ ሐዋርያዊ ጉብኝታቸው ወቅትም በመጣለያ ጣቢያ የሚገኙ በርካታ ስደተኞች ፍርሃትን፣ ልዩነትን እና ለሞት የሚዳርግ ቸልተኝነት እንዲያስወግዱ አሳስበው ብርታትን ተመኝተውላቸዋል።
በግሪክ ዋና ከተማ አቴንስ በሚገኝ ቅዱስ ዲዮኒሲዮስ ካቶሊክ ትምህርት ቤት ውስጥ በመገኘት የወደፊት ሕይወታቸው አስጊ እና አስፈሪ ለሆነባቸው ወጣቶች ብርታትን ተመኝተውላቸዋል። በኦርሶላይን ማኅበር እህቶች በሚመራ ካቶሊክ ትምህርት ቤት በተዘጋጀው ሥነ-ሥርዓት ላይ የተገኘ አንድ ወጣት ለቅዱስነታቸው ባቀረበው መልዕክት፣ የር. ሊ. ጳ ፍራንችስኮስ በግሪክ ያደረጉት ሐዋርያዊ ጉብኝት በእግዚአብሔር ለማያምኑትም እጅግ ጠቃሚ እንደነበር ለቫቲካን የዜና አገልግሎት ገልጿል። ር. ሊ. ጳ ፍራንችስኮስ በዓለማችን ውስጥ ለሚገኝ እያንዳንዱ ማኅበረሰብ እንደሚያሳቡ እና እንደሚጨነቁ የገለጸው ወጣት ፊሊፖ ፋሩሲስ፣ ቅዱስነታቸው ግሪክን ጎብኝተው መልዕክታቸውን ማስተላለፋቸው፣ ማህበራዊ ችግሮችን ለመገንዘብ ፍላጎት ላደረበት ወጣት ትልቅ ዕድል መሆኑን አስረድቷል።