የዚህ ዝግጅት አቅራቢ ዮሐንስ መኰንን - ቫቲካን
በሦስት ዶክተሮች ትብብር የተካሄደው የቀዶ ጥገና ሕክምና በስኬት መፈጸሙን ለቫቲካን ጋዜጣዊ መግለጫ ክፍል ዳይሬክተር ለአቶ ማቴዎ ብሩኒ ቅዱስነታቸው ገልጸዋል። ሌሎችም የሆስፒታሉ ዶክተሮች ለቅዱስነታቸው የተደረገላቸውን የሕክምና እርዳታ በቅርብ የተከታተሉት መሆኑ ታውቋል። ር. ሊ. ጳ ፍራንችስኮስ እሑድ ሰኔ 27/2013 ዓ. ም ከሰዓት በኋላ ሮም ወደሚገኝ የካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን ሆስፒታል የሄዱት ከዚህ በፊት በተያዘላቸው ቀጥሮ መሠረት መሆኑን ጋዜጣዊ መግለጫ ክፍሉ ዳይሬክተር አስረድተዋል።
አክለውም ቅዱስነታቸው ሦስት ሰዓት የወሰደ የቀዶ ጥገና ሕክምና ከተደረገላቸው በኋላ አሁን በመልካም ሁኔታ ላይ እንደሚገኙ ገልጸው፣ ክትትል እየተደረገላቸው ለሚቀጥሉት ሰባት ቀናት ያህል በሆስፒታሉ የሚያርፉ መሆኑን አቶ ማቴዎ ብሩኒ አስታውቀዋል።