ፈልግ

ከዛሬ 40 ዓመት በፊት እ.አ.አ በ1980 ዓ.ም በኤል ሳልቫዶር የተገደሉ ሚስዮናዊያን ከዛሬ 40 ዓመት በፊት እ.አ.አ በ1980 ዓ.ም በኤል ሳልቫዶር የተገደሉ ሚስዮናዊያን  

ር.ሊ.ጳ ፍራንቸስኮስ ከዛሬ 40 ዓመት በፊት በኤል ሳልቫዶር ለተገደሉ ሰማዕታት ጸለዩ።

ቀድም ሲል በኤል ሳልቫዶር በነበረው የእርስ በእርስ ጦርነት የተጎዱ ሰዎችን በተለያየ መልኩ ሲያገለግሉ የነበሩ የካቶሊክ ቤተክርስቲያን ሴት ሚሲዮናዊ የቅዱስ ወንጌል ልዑካን የዛሬ አርባ አመት ገደማ በታጣቂዎች አሰቃቂ በሆነ መልኩ መገደላቸው የሚታወስ ሲሆን ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ የዛሬ አራባ አመት ገደማ በኤል ሳልቫዶር ለተገደሉ ሰማዕታት ጸሎት ማድረጋቸው ተገልጿል።

አቅራቢ መብራቱ ኃ/ጊዮርጊስ ቫቲካን

በኤል ሳልቫዶር የእርስ በእርስ ጦርነት ከተጀመረ ከአስር ወራት በኋላ እ.ኤ.አ. በታህሳስ 2/1980 ዓ.ም ነበር በወቅቱ ይህንን የእርስ በእርስ ጦርነት በከፍተኛ ሁኔታ ሲቃወሙ የነበሩት በወቅቱ የሳልቫዶር ሊቀ ጳጳስ የነበሩት እና አሁን በቅርቡ የቅድስና ማዕረግ የተሰጣቸው ቅዱስ ኦስካር ሮሜሮ ከተገደሉ ከስምንት ወራት በኋላ ነበር አራት አሜሪካውያን የካቶሊክ ቤተክርስቲያን ሴት ሚሲዮናዊ የቅዱስ ወንጌል ልዑካን በጭካኔ የተገደሉት።

በወቅቱ በተከሰተው የእርስ በእርስ ጦርነት ምክንያት ለኤል ሳልቫዶር እና ለጎረቤት አገራት የሰብዓዊ ዕርዳታ በማቅረብ ላይ የነበሩ አራት ሴት ሚሲዮናዊ የቅዱስ ወንጌል ልዑካን ለቀኝ ክንፍ መንግሥት ሥጋት ተደርገው ይታዩ የነበረ ሲሆን የፖለቲካ ተቃውሞን በማሰማት በአገዛዙ ተከሰው ነበር።

ይህንን ዝግጅት ከእዚህ በታች ያለውን ተጫወት የሚለውን ምልክት በመጫን ማዳመጥ ትችላላችሁ!

የአርባ አመት እድሜ የነበራቸው ሲስተር ኢታ ፎርድ እና ሲስተር ማውራ ክላርክ እነዚህ ሁለት ሴት ሚሲዮናዊ የቅዱስ ወንጌል ልዑካን ከኒዮርክ ከተማ ወደ ኤል ሳልቫዶር ሂደው ያገለግሉ የነበሩ መነኩሳት እንደ ነበሩ የተገለጸ ሲሆን የአርባ ዘጠኝ አመት እድሜ የነበራቸው ሲስተር ዶሬቲ የኦርሶሊን ማሕበር አባል የነበሩ መነኩሴ  ከኬቪላንድ ወደ ኤል ሳልቫዶር በመጓዝ ሕዝቦችን ሲያገለግሉ እንደ ነበረ ተገልጿል፣ በመጨረሻም የጋብቻ ስነ-ስተዓት ለመፈጸም በመዘጋጀት ላይ የነበረችው የ 27 አመት እድሜ የነበራት ምዕመን ሚስዮናዊ ዣን ዶኖቫን እንዲሁም ከኬቪላንድ የመጣች ወጣት ምዕመን የቅዱስ ወንጌል ልዑክ እንደ ምትገኝበት ተግልጿል። እነዚህ አራት ሴት የቅዱስ ወንጌል ልዑክ የነበሩ ሚስዮናዊያን በአምስት የኤል ሳልቫዶሪያ ብሔራዊ ጥበቃ ዘብ አባላት ከተደፈሩ በኋላ ነበር በአሰቃቂ ሁኔታ የተገደሉት።

የሊቀ ጳጳሱ ጸሎት

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ በሕዳር 23/2013 ዓ.ም በቫቲካን የጠቅላላ የትምህርተ ክርስቶስ አስተምህሮ ካደረጉ በኋላ የእነዚህ ቀድም ሲል የገለጽናቸው አራት ሰማዕታት በግፍ የተገደሉበት 40ኛው አመት መታሰቢያን አስመልክተው ለታዳሚዎች እነዚህን አራት ሰማዕታት በተመለከተ ሲናገሩ የሚከተለውን ብለዋል . . .

"በኤል ሳልቫዶር የተገደሉት አራት ሚስዮናውያን የሞቱበት 40 ኛ ዓመት ዛሬ እየታሰበ ይገኛል ... እ.ኤ.አ. ታህሳስ 2/1980 ዓ.ም በአገሪቷ ብሄራዊ የጥበቃ ዘብ አባላት ታፍነው ፣ ተደፈረው ተገድለዋል። በእርስ በእርስ ጦርነት ወቅት ለሕዝቡ አገልግሎት እየሰጡ ነበር። ጦርነቱን ሸሽተው ለተደበቁ ሰዎች በተለይም ለድሃ ቤተሰቦች ምግብና መድኃኒት አቅርቦት ያደርጉ ነበር፣ እነዚህ ሴቶች እምነታቸውን በታላቅ ልግስና መስክረዋል። እነሱ ታማኝ ሚስዮናዊ ደቀ መዛሙርት እንድንሆን ለሁላችንም ምሳሌ አሳይተው አልፈዋል”።

በዚያ የመጀመሪያ ዓመት የእርስ በእርስ ጦርነት ብቻ ከተገደሉት ከ 8,000 በላይ ሰዎች መካከል እነዚህ አራት ሚስዮናዊያን የሚገኙበት ሲሆን በወቅቱ ለ12 አመታት ያህል የዘለቀ ጦርነት ከ 75,000 ሺህ በላይ ሰዎችን ሕይወት መቅጠፉ ይታወሳል።

የ4ቱ ሚስዮናዊያን የግድያ ሁኔታ 

በወቅቱ ከአራቱ ሚስዮናዊያን መካከል ሁለቱ  በማናጓ ኒካራጓ በተካሄደው ኮንፈረንስ ከተሳተፉ በኋላ ወደ መኖሪያቸው ለማቅናት ከአውሮፕላን ማረፊያ ለቀው ከወጡ በኋላ ቀሪዎቹ ሁለት ሚስዮናዊያን ይዘውት በመጡት መኪና ተስፍረው ጉዞ ይጀምራሉ። አምስት የብሔራዊ ጥበቃ አባል ይሆኑ ዘብ ታጣቂዎች እነዚህ አራት ሚስዮናዊያን ይጓዙበት የነበረውን መኪና ያስቆማሉ። በመቀጠል በአንጻራዊ ሁኔታ ገለል ወዳለ ቦታ ተወስደው በወታደሮች ተደበደቡ፣ ተደፈሩ እና ከእዚያም በኋላ ተገደሉ።

ይህ ሲፈጸም የተመለከቱ ምስክሮች ነበሩ - እነዚህ አራት ሴት ሚስዮናዊያን አምስት የብሔራዊ ጥበቃ አባላት በተወሰዱበት አቅራቢያ ይኖሩ የነበሩ አርሶ አደሮች ሁኔታውን አስመልከተው ሲናገሩ እነዚህ አራት ሴት ሚስዮናዊያን ሲጓዙበት የነበረው ነጭ የቫን መኪና ሲነዳ እና ወደ ገለል ያለ ቦታ እንደ ተወሰዱ መመልከታቸውን እና ከእዝያም በኋላ የተኩስ ድምጽ መስማታቸውን በወቅቱ ገልጸው ነበር። ከዚያም አምስቱ የብሔራዊ ጥበቃ ዘብ አባላት አራቱ ሚስዮናዊያን ሲጠቀሙበት የነበሩትን ተመሳሳይ ነጭ መኪና ውስጥ ሆነው ቦታውን ለቀው ሲወጡ ታይተዋል። በሚቀጥለው ቀን እ.አ.አ ታህሳስ 3/1980 ዓ.ም አራት አስከሬን በአንድ ጉድጓድ ውስጥ ተጥለው የተገኙ ሲሆን ገበሬዎቹ በአቅራቢያው በሚገኘው የጅምላ መቃብር እንዲቀብሯቸው እንደ ታዘዙ ተናግረዋል። ጉዳዩን ለደብራቸው ቄስ ያሳወቁ ሲሆን ዜናው በመጨረሻ የሊቀ ጳጳስ አስካር ሮሜሮ ተተኪ የነበሩት ሊቀ ጳጳስ አርቱሮ ሪቬራ ያ ዳማስ እና በኤል ሳልቫዶር የዩናይትድ ስቴትስ አምባሳደር ሮበርት ኋይት እንደ ደረሳቸው ይታወሳል።

እነዚህ አራት ሴት የቅዱስ ወንጌል ልዑክ የነበሩ ሚሲዮናዊያን ሙት አመታቸው በእየአመቱ ታስቦ ይውላ፣ ጸሎትም ይደረጋል። የሰብአዊ መብት ተሟጋቾች እና የተጎጂ ቤተሰቦች ለፍትህ መታገላቸውን አላቆሙም። ይህንን ድርጊት የፈጸሙ አምስት የብሔራዊ ዘብ አባላት በነፍስ ግድያ ወንጀል ተፈርዶባቸዋል፣ በወቅቱ የብሔራዊ ዘብ ወታድሮች የበላይ አለቃ የነበረው ሰዉ ከ16 ዓመት አስልቺ ፍለጋ በኋላ ስደተኛ መስሎ ተሸሽጎ ይኖርባት ከነበረው ከአሜሪካ ፍሎሪዳ ግዛት ወደ ኤል ሳልቫዶር እዲመለስ ተደርጎ ለእዚህ እና ለሌሎች እርሱ በእርሱ ትዕዛዝ ላስፈጸመው ግድያ ፍርድ እንደ ተበየነበት ተገልጿል።

02 December 2020, 13:34