ፈልግ

ቅዱስነታቸው የክርስቶፎር ኮሎምቦ ካቶሊካዊ ማኅበር አባላትን በተቀበሉበት ወቅት፣ ቅዱስነታቸው የክርስቶፎር ኮሎምቦ ካቶሊካዊ ማኅበር አባላትን በተቀበሉበት ወቅት፣ 

ር. ሊ. ጳ. ፍራንችስኮስ የቸርነት አገልግሎት የቤተክርስቲያን ጥሪ መሆኑን አስታወቁ።

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ ከተቋቋመ መቶ ዓመት የሆነውን እና በመካከለኛው ምስራቅ አገሮች የቸርነት አገልግሎቶችን በማበርከት ላይ የሚገኘውን የክርስቶፎር ኮሎምቦ ካቶሊካዊ ማኅበር አባላትን፣ የካቲት 2/2012 ዓ. ም. በቫቲካን ውስጥ በሚገኘው በቅዱስ ቀለሜንጦስ የመሰብሰቢያ አዳራሽ ተቀብለው ማነጋገራቸው ታውቋል። ማኅበራቸው የተመሠረተበትን መቶኛ ዓመት በቫቲካን በሚገኘው በቅዱስ ጴጥሮስ ባዚሊካ ማክበርን ለመረጡት የማኅበሩ አባላት ቅዱስነታቸው ባሰሙት ንግግር፣ በጦርነት፣ በድህነት እና በስደት ውስጥ ለሚገኝ የመካከለኛው ምስራቅ አገሮች ህዝቦች ከረጅም ዓመታት ወዲህ በማቅረብ ላይ ለሚገኙት የቸርነት እና የፍቅር ድጋፍ ቅዱስነታቸው ምስጋናቸውን አቅርበውላቸዋል። 

የዚህ ዝግጅት አቅራቢ ዮሐንስ መኰንን - ቫቲካን

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ የማሕበሩ አባላትን ተቀብለው ባነጋገሯቸው ጊዜ ሰላምታቸውን አቅርበው ቡራኬአቸውን ከሰጧቸው በኋላ ማሕበሩ ከአንደኛው የዓለም ጦርነት አንስቶ በርካታ የቸርነት ስራዎችን ሲያከናውን መቆየቱን አስታውሰው፣ በዚያ የጨለማ ዘመን፣ የቀድሞ ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ቤነዲክቶስ 15ኛ ጥያቄ መሠረት ማሕበሩ ለአካባቢው ሕዝቦች ዕለታዊ ምግብን እና ሰብዓዊ ዕርዳታዎች ሲያቀርብ መቆየቱን ቅዱስነታቸው አስታውሰዋል። ማሕበሩ ከዚህም በተጨማሪ ለአካባቢው አገሮች ወጣቶች የመዝናኛ ማዕከላትን፣ የትምህርት ተቋማትን እና የመኖሪያ ቤቶች አገልግሎት በመስጠት ትልቅ እገዛ ማድረጋቸውን እና ከዚህ ጎን ለጎን በትምህርተ ክርስቶስ ማዳረስ አገልግሎት በመሳተፋቸው ምስጋናችውን አቅርበውላቸዋል።

ለመካከለኛው ምሥራቅ አገሮች የቀረበ አገልግሎት፣

ማኅበሩ በማበርከት ላይ ከሚገኝበት አገልግሎቶች መካከል ከፍተኛ ዋጋ የሚሰጠውን የጠቀሱት ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ፣ በጦርነት ምክንያት ከመኖሪያቸው ለሚፈናቀሉት የሚያደርገውን ድጋፍ እና ስደት እና መከራ ለሚደርስባቸው በሙሉ የሚያደርገውን ድጋፍ አስታውሰው፣ ማኅበሩ ይህን በማበርከቱ የእግዚአብሔር ፍቅር መገለጫ ሆኖ በመገኘቱ ምስጋናቸውን አቅርበዋል።

ቅዱስነታቸው ለማኅበሩ አባላት ባሰሙት ንግግር፣ ማኅበሩ በመካከለኛው የምሥራቅ አገሮች ውስጥ ለሰው ልጅ ቅድስና የሚሰጡትን ታማኝ ምስክርነት አስታውሰዋል፣ ቅዱስነታቸው በማከልም ማኅበሩ በዚህ ታማኝ ምስክርነት በመታገዝ፣ በአመጽ፣ በጦርነት እና በድህነት ውስጥ ለሚሰቃይ የአካባቢው ሕዝቦች ቁሳዊ እና መንፈሳዊ አገልግሎቶችን ሲያበረክት መቆየቱን ገልጸው፣ በስቃይ ለሚገኙት ወንድሞቻቸው እና እህቶቻቸው ባደረጉት የቸርነት ተግባር፣ የእግዚአብሔርን ዘለዓለማዊ ፍቅር በተግባር በማሳየታቸው ምስጋናቸውን አቅርበውላቸዋል።

ግድ የለሽነትን ማስወገድ፣

ከሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ ተተኪ ከሆኑት ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ጎን በመቆም፣ እጅግ ለተቸገሩት፣ ለደኸዩት እና ከማኅበረሰብ ለተገለሉት፣ በተለይም ወጣቶችን መደገፍ ለቤተክርስቲያን የተሰጣት የቸርነት አገልግሎት አደራ መሆኑን በመረዳት፣ የማኅበሩ መስራች የሆኑትን የክቡር ሚካኤል ማጊቪኒ ዓላማ ማሳካት እና ዓለምን ከግድ የለሽነት ባሕል ማላቀቅ መሆኑን ቅዱስነታቸው አስረድተዋል።

በዓለማችን ውስጥ ልዩነት እና የሃብት ክፍፍል አለመመጣጠን ይታያል ያሉት ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ፣ ማሕበሩ በችግር ለወደቁት በሚያበረክተው የቸርነት አገልግሎት በዓለማችን ጎልቶ የሚታየውን የግድ የለሽነት ባሕል በማስወገድ በጋራ ሁሉን አቀፍ እና የበለጠ ፍትሃዊ ማኅበረ ሰብን ለመገንባት ያግዛል ብለዋል።

ይህን ዘገባ በድምጽ ለማዳመጥ ከዚህ ቀጥሎ የሚገኘውን “ተጫወት” የሚለውን ምልክት ይጫኑ!
12 February 2020, 15:24