ፈልግ

እኛ ጌታን ይቅርታ መጠየቅ ብንታክትም እንኳን፣ ጌታ ለእኛ ይቅርታ ማድረግ ግን በፍጹም ታክቶ አያውቅም

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራቸስኮስ ዘወትር ረቡዕ እለት በቫቲካን በሚገኘው በቅዱስ ጴጥሮስ አደባባይ ወይም በቫቲካን በሚገኘው የጳውሎስ ስድስተኛ የስብሰባ አዳራሻ ለሚሰበሰቡ ምዕመናን፣ መንፈሳዊ ነጋዲያን እና የአገር ጎብኝዎች በተለያዩ አርእስቶች ላይ ተመርኩዘው የጠቅላላ የትምሕርተ ክርስቶስ አስተምህሮ እንደ ሚያደርጉ ይታወቃል። በዚህ መሰረት ቅዱስነታቸው በጥር 27/2012 ዓ.ም በቫቲካን በሚገኘው የጳውሎስ ስድስተኛ የስብሰባ አዳራሽ ያደርጉት የጠቅላላ የትምህርተ ክርስቶስ አስተምህሮ ከእዚህ ቀድም ባለፈው ሳምንት በማቴዎስ ወንጌል ምዕራፍ 5 ውስጥ በተጠቀሰው ኢየሱስ በተራራው ላይ በሰበከው ስብከት ላይ መሰረቱን ያደረገ አስተምህሮ እንደ ነበረ የተገለጸ ሲሆን ““እናንት ሸክም የከበዳችሁና የደከማችሁ ሁሉ ወደ እኔ ኑ፤ እኔም ዕረፍት እሰጣችኋለሁ። ቀንበሬን ተሸከሙ፤ ከእኔም ተማሩ፤ እኔ በልቤ የዋህና ትሑት ነኝና፤ ለነፍሳችሁም ዕረፍት ታገኛላችሁ፤ ቀንበሬ ልዝብ ሸክሜም ቀላል ነውና” (ማቴ 11፡28-30) በሚለው በእለቱ በተነበበው የቅዱስ ወንጌል ክፍል ላይ ተንተርሰው ባደረጉት አስተምሮ ቅዱስነታቸው እንደ ገለጹት “እኛ ጌታን ይቅርታ መጠየቅ ብንታክትም እንኳን፣ ጌታ ለእኛ ይቅርታ ማድረግ ግን በፍጹም ታክቶ አያውቅም!” ብለዋል።

የእዚህ ዝግጅት አቅራቢ መብራቱ ኃ/ጊዮርጊስ-ቫቲካን

ክቡራን እና ክቡራት የዝግጅቶቻችን ተከታታዮች ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ በጥር 27/2012 ዓ.ም ያደረጉትን የጠቅላላ የትምሕርተ ክርስቶስ አስተምህሮ ሙሉ ይዘቱን እንደ ሚከተለው አሰናድተነዋል ተከታተሉን።

የተወደዳችሁ ወንድሞቼ እና እህቶቼ እንደምን አረፈዳችሁ!

በማቴዎስ ወንጌል ውስጥ ከተጠቀሱት ስምንት ብጹዕን እንድንሆን ከሚያደርጉን ተግባራት መካከል የመጀመሪያውን ዛሬ እንመለከታለን። ኢየሱስ የደስታን መንገድ እንዴት እንደ ምንጀምር ግራ የተጋባ በሚመስል መልኩ በመግለጽ መልእክቱን ይጀምራል “በመንፈስ ድሆች የሆኑ ብፁዓን ናቸው፣ መንግሥተ ሰማያት የእነሱ ናትና” (5፣3) ይለናል። አስገራሚ የሆነ መንገድ እና ብጽዕና የሚገኝበት ለየት ያለ ምንገድ ነው።

ራሳችንን መጠየቅ አለብን! እዚህ ጋር “ድሃ” ሲባል ምን ማለት ነው? ቅዱስ ማቴዎስ ይህንን ቃል ብቻ ከተጠቀመ ትርጉሙ በቀላሉ ኢኮኖሚያዊ ይሆናል ማለት ነው ፣ ማለትም እሱ አነስተኛ ወይም ምንም ዓይነት ድጋፍ የሌላቸውን እና የሌሎችን እርዳታ የሚፈልጉ ሰዎችን ያመለክታል ማለት ነው።

ነገር ግን የማቴዎስ ወንጌል ከሉቃስ ወንጌል በተለየ መልኩ “በመንፈስ ድሃ የሆኑ” በማለት ይገልጻል፣ ይህ ምን ማለት ነው? መጽሐፍ ቅዱስ እንደ ሚገልጸው እግዚአብሔር ለአዳም እፍ ብሎ የሰጠውን የሕይወት እስትንፋስ ያመለክታል፣ ይህ ደግሞ እኛ የሰው ስብዕና ማለትም የሕይወታችን ዋና ክፍል የሆነው ለእኛ በጣም የቅርብ ልኬታችን ነው። እንግዲያውስ “በመንፈስ ድሆች” የተባሉት እና ድህነት የሚሰማቸው፣ እርዳታ ፈላጊ የሆኑ ሰዎች፣ በልባቸው ጥልቀት ውስጥ የሚኖሩ ሰዎች ናቸው። “መንግሥተ ሰማያት የእነርሱ ናትና” ኢየሱስ እነርሱ የተባረኩ መሆናቸውን ተናግሯል።

ስንት ጊዜ ነው ይህ ሐሳብ ተቃራኒ በሆነ መልኩ የተነገረን! አንድ ነገር መሆን፣ አንድ ሰው መሆንን ይጠይቃል ... ለራሳችን ስም ስንል መሰራት አለብን ... ብቸኝነት እና ሐዘን የሚመጣው ከእዚህ ነው፣ እኔ “አንድ ሰው” መሆን ካለብኝ ከሌሎች ጋር እወዳደራለሁ፣ ስለራሴ እጨነቃለሁ። ድሃ መሆኔን ካልተቀበልኩኝ የእኔን ብስጭት የሚያስታውሰኝ ነገር ሁሉ እጠላለሁ።

ሁሉም ሰው ምንም ያህል በጣም ብዙ ሥራ ቢሰራ እንኳን እርሱ ሁልጊዜ ሕይወቱ ያልተሟላ እና ለአደጋ የተጋለጠ መሆኑን በራሱ ፊት በሚገባ ያውቃል። ነገር ግን ወስን/ገደባችንን የማንቀበል ከሆነ ምን ያህል አስከፊ የሆነ ነገር ነው! ኩሩ የሆኑ ሰዎች እርዳታ አይጠይቁም፣ ምክንያቱም ራሳቸውን መቻላቸውን ማረጋገጥ አለባቸው። እናም አንድ ስህተት አምኖ መቀበል እና ይቅርታ መጠየቅ ምንኛ አስቸጋሪ ነው! ይልቁንም ጌታ እኛን ይቅር ከማለት በፍጹም ታክቶ አያውቅም፣ አለመታደል ሆኖ ይቅርታን መጠየቀ የምንታክተው እኛ ራሳችን ነን።

ይቅርታን መጠየቅ ለምን ከባድ ሆነ? ምክንያቱም ግብዝነታችንን የሚያሳድግ፣ ገጽታችንን ያዋርዳል ብለን ስለምናምን ነው። አሁንም ቢሆን የአንድን ሰው ድክመቶች ለመደበቅ መሞከር አሰልቺ እና አስጨናቂ ነገር ነው። ኢየሱስ ክርስቶስ ነግሮናል -ድሃ መሆን ለችሮታ እድል ይከፍታል፣ እናም ከዚህ እጥረት የምንወጣበትን መንገድ ያሳየናል። በመንፈስ ድሀ የመሆን መብት ተሰጥቶናል ፣ ምክንያቱም ይህ የእግዚአብሔር መንግሥት መንገድ ነውና።

እንደገና ለመገሰጽ የሚረዳን አንድ መሠረታዊ ነገር አለ - እኛ እራሳችንን በመንፈስ ድሆች አድርገን መቁጠራችንን መለወጥ የለብንም ምክንያቱም እኛ ቀድሞውኑ በመንፈስ ድሃ ነንና! ሁላችንም በመንፈስ ድሆች፣ እርዳታ ፈላጊዎች ነን! ይህ ሰብዓዊ ሁኔታን የሚገልጽ ነገር ነው። የሰዓታት ጸሎቶችን በምናድርግበት ወቅት ጸሎታችንን የምንጀምረው “ጌታ ሆይ በቶሎ ወደ እኔ ና፣ ጌታ ሆይ እኔን ለመርዳት ፍጠን” በማለት እንጀምራለን። እንደዚህ የሚናገረው ማን ነው? እርዳታ ፈላጊ የሆነ ሰው ነው። የፀሎት ኃይል የሚመነጨው ከድህነታችን ነው።

የእግዚአብሔር መንግሥት በመንፈስ ድሆች ለሆኑ ሰዎች ናት። ይህ ዓለም መንግስታቸው የሆነ ሰዎች አሉ፦ ንብረት አላቸው፣ ምቾት አላቸው። ነገር ግን እነሱ ጊዜያዊ የሆኑ መንግሥቶች ናቸው። የሰዎች ኃይል፣ ታላላቅ ገዢዎች እንኳን ሳይቀር ያልፋሉ እናም ይጠፋሉ። ግን ከሁሉም በላይ - ይህ እውነት ነው? ከእራሳቸው በላይ እውነተኛውን መልካም የሆነ ነገር እንዴት መውደድ እንደሚችሉ የሚያውቁ ሰዎች በእውነቱ ይነግሳሉ። ይህ የእግዚአብሔር ኃይል ነው። አንድ እጅግ የሚያምር የስርዓተ አምልኮ ጸሎት እንዲህ ይላል “አቤቱ እግዚአብሔር ሆይ ሁሉን ቻይነትህን ከሁሉም በላይ በምሕረት እና በይቅርታ አሳየን…” ይላል።

ክርስቶስ ኃይሉን ያሳየው በምን ነበር? የምድር ነገሥታት ለማድረግ ችሎታ የሌላቸውን ነገሮች በማድረጉ የተነሳ ነው። ይህ እውነተኛ ኃይል ነው ፡፡

እውነተኛ ነፃነት በዚህ ውስጥ ይገኛል። ይህ የነፃነት አገልግሎት በብጽዕና መንገድ የሚገልጽ የድህነት መንገድ ነው። ምክንያቱም መቀበል ያለብን፣ የእኛን ማንነት እና ይልቁኑ ልንሻው የሚገባን ድህነት ስለሆነ፣ ነፃ ለመሆን እና አፍቃሪ ለመሆን ከዓለም ነገሮች ውስጥ ነፃ መሆን ይገባናል።

ይህንን ዘገባ በድምጽ ለመከታተል ከዚህ በታች ያለውን “ተጫወት” የሚለውን ምልክት ይጫኑ!
05 February 2020, 15:23