ፈልግ

ር.ሊ.ጳ ፍራንቸስኮስ “ታሪክን ለመቅረጽ የሚያስችል እውነተኛው መንገድ ርህራሄ ነው”

ር.ሊ.ጳ ፍራንቸስኮስ ከኅዳር 09-16/2012 ዓ.ም ድረስ በታይላንድ እና በጃፓን በቅደም ተከተል የሚያደርጉትን 32ኛውን ሐዋርያዊ ጉብኝት በኅዳር 09/2012 ዓ.ም አመሻሹ ላይ መጀመራቸውን መዘገባችን የሚታወስ ሲሆን በእዚህም መሰረት ቅዱስነታቸው ከኅዳር 09-12/2012 ዓ.ም በታይላንድ ቆያታ ካደረጉ በኋላ በመቀጠል “ሕይወትን ከጉዳት እና ከሞት አደጋ እንታደግ” በሚል መሪ ቃል ከኅዳር 12-16/2012 ዓ.ም ድረሰ የ32ኛው ሐዋርያዊ ጉብኝታቸው ሁለተኛ መዳረሻ አገር ወደ ሆነችው ጃፓን ማቅናታቸው መግለጻችን ይታወሳል። ቅዱስነታቸው በእነዚህ በጃፓን በሚኖራቸው የአራት ቀን ቆያት የጃፓን ዋና ከተማ የሆነችውን ቶክዮን ጨምሮ፣ በሁለተኛ የዓለም ጦርነት ወቅት በኒውክለር የጦር መሣርያ ድብደባ ምክንያት ከፍተኛ ውድመት የደረሰባቸውን እና እጅግ በጣም ብዙ የሆኑ የሰው ልጆች ሕይወት የተቀጠፈበት አደጋ ተከስቶ የነበረባቸውን ኔጋሳኪ እና ሂሮስሺማን በቀደም ተከተል መጎብኘታቸው መግለጻችን የሚታወስ ሲሆን ከእዚያም በመቀጠል ቅዱስነታቸው በኅዳር 14/2019 ዓ.ም የክርስቶስ ንጉሥ በዓል በተከበረበት ወቅት በሂሮሽማ መስዋዕተ ቅዳሴ ማሳረጋቸው ተገልጹዋል።

የእዚህ ዝግጅት አቅራቢ መብራቱ ኃ/ጊዮርጊስ-ቫቲካን

ቅዱስነታቸው በወቅቱ ባሳረጉት መስዋዕተ ቅዳሴ ላይ ባሰሙት ስብከት እንደ ገለጹት “ታሪክን ለመቅረጽ የሚያስችል እውነተኛው መንገድ ርህራሄ ነው” ማለታቸው የተገለጸ ሲሆን ቅዱስነታቸው በወቅቱ ከሉቃስ ወንጌል 23፡35-43 ላይ ተወስዶ በተነበበውና “ኢየሱስ ሆይ፤ በመንግሥትህ አስበኝ” ብሎ በተናገረውና ከኢየሱስ ጎን ተስቅሎ በነበረው ወንጀለኛ ታሪክ ላይ መሰረቱን ያደርገ ስብከት እንደ ነበረ ለመረዳት የተቻለ ሲሆን የእዚህ ወንጀለኛ የነበረው ሰው ባሕሪይ እና እምነቱን የገለጸበት ሁኔታ አስፈሪ እና አሰቃቂ፣ ኢፍትሃዊ የሆነው የመስቀል ላይ ሕይወት ለሰው ልጆች ሁሉ የተስፋ መልእክት እንዲሆን አድርጓል ብለዋል።

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮ በወቅቱ ያደረጉ ስብከት ቀደም ሲል እንደ ገለጽነው ከኢየሱስ ጎን ተሰቅሎ የነበረው ወንጀለኛ የነበረው ሰው ላይ ትኩረቱን ያደረገ እንደ ነበረ የተገለጸ ሲሆን “ኢየሱስ ሆይ ፣ በንጉሣዊ ስልጣንህ ተመልሰህ ስትመጣ አስበኝ” በማለት ከኢየሱስ ጋር ተስቅሎ የነበረው ሰው መናገሩን አስታውሰው ኢየሱስ ለእዚህ ወንጀለኛ ተብሎ ለተፈረጀው ሰው “እውነት እልሃለሁ ፣ ዛሬ ከእኔ ጋር በገነት ትሆናለህ” በማለት ማረጋገጫ እንደሰጠው ቅዱስነታቸው ጨምረው ገልጸዋል። ያ አጋጣሚ የኢየሱስን ሕይወት አጠቃላይ ትርጉም እና እውነታ የሚያሳይ አጋጣሚ እንደ ነበረ የገለጹት ቅዱስነታቸው ኢየሱስ ሁልጊዜ እና በሁሉም ስፍራ ለልጆቹ የድህንነት ስጦታ እንደ ሚያቀርብላቸው ጨምረው ገልጸዋል።

ፍቅር ጥላቻን ፣ ራስ ወዳድነትን ያሸንፋል

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ ስብከታቸውን በቀጠሉበት ወቅት ጨምረው እንደ ገለጹት “ፍቅር ጥላቻን እና ራስ ወዳድነትን ያሸንፋል” ማለታቸው የተገለጸ ሲሆን “ ‘ራስህን አድን!’ የሚለው ቃል ነቀፋ የሌለበት፣ ነገር ግን ስቃይን እንዲቀበል የተፈረደበት አምላክ የመጨረሻ ቃል አይደለም” በማለት ስብከታቸውን የቀጠሉት ቅዱስነታቸው “ከዚያ ይልቅ ፣ ልባቸው እንዲነካ ፣ ታሪክን ለመቅረፅ እውነተኛ መንገድ ርህራሄን ከሚመርጡ ሰዎች መልስ ያገኛሉ” ብለዋል።

ቅዱስ ጳውሎስ ሚኪ እና በመቶዎች የሚቆጠሩ ከእርሱ ጋር የነበሩ ሰማዕታት ቅዱስ ወንጌል በጃፓን በጽናት ተሞልተው በመመስክር ሂደት ውስጥ በነበሩበት ወቅት በአሰቃቂ ሁኔታ ተገለው ሰማዕት መሆናቸውን ያስታወሱስት ቅዱስነታቸው ለእኛ ሲል የተሰቀለው ክርስቶስ የእርሱ ፍቅር ሁሉንም የጥላቻ ፣ የራስ ወዳድነት መንፈስ እና ፌዝ የሚያሸንፍ መሆኑን በድፍረት እንድንናገር ይረዳናል ብለዋል። ቅዱስነታቸው ስብከታቸውን በቀጠሉበት ወቅት እንደ ገለጹት መልካም ተግባሮችን እና ውሳኔዎችን የሚያደናቅፉ እነዚያን የፊት ገጽታዎችን አፍራሽ አመለካከቶች ወይም ምቾት መጓደል ሁሉ ማሸነፍ ይችላል” ብለዋል።

ሚስዮናዊ ደቀመዛሙርት፣ ምስክሮቹ እና የመጪውን ግዜ የምስራች ቃል አብሳሪዎች እንደመሆናችን መጠን በምንም ዓይነት መልኩ በክፉዎች ፊት መሳለቂያ መሆን አንችልም” በማለት ስብከታቸውን የቀጠሉት ቅዱስነታቸው ይልቁንም እኛ ራሳችንን ባገኘንበት ቦታ ሁሉ የክርስቶስ መንግሥት እርሾ እንድንሆን መጠራታችንን ማስታወስ ይገባናል፣ በቤተሰብ ውስጥ ፣ በሥራ ቦታ ወይንም በአጠቃላይ በሕብረተሰቡ ውስጥ፣ መንፈስ ቅዱስ በሕዝቦች መካከል ተስፋን መተንፈሱን የሚቀጥልበት ትንሽዬ የሆነ የተከፈተ በር መሆን ይኖርብናል” ብለዋል።

“መንግሥተ ሰማያት የእኛ የጋራ ግብ ነው” በማለት ስብከታቸውን የቀጠሉት ቅዱስነታቸው ስለ ነገ ብቻ ሳይሆን ስለ ዛሬም ጭምር ስንል በእኛ ውስጥ የሚታየው የግዴለሽነት መንፈስ ብዙውን ጊዜ የታመሙትንና የአካል ጉዳተኞችን ፣ አዛውንቶችን እና የተረሱትን ሰዎች፣ ስደተኞችን እና ስደተኛ ሰራተኞች ከሚሰቃዩበት ሁኔታ ነጻ ይሆኑ ዘንድ የበኩላችንን ተግባር ማከናወን እንደ ሚገባ የገለጹት ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳቱ ኢየሱስ ራሱ በእነዚህ ሰዎች ፊት ላይ ራሱን እየገለጸ ይገኛል ብለዋል።

ድምፃችንን በብርታት ከፍ እናድርግ

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ ስብከታቸውን በቀጠሉበት ወቅት እንደ ገለጹት በመቀል ላይ እጅግ በጣም ብዙ የሆኑ ድምቾች ዝም ሲሉ፣ ሌሎች ደግሞ ሲያሾፉ፣ ከኢየሱስ ጎን ተሰቅሎ የነበረው ወንጀለኛ ተብሎ ተፈርጆ የነበረው ሰው ግን ድምጹን ማሰማት መቻሉ ለጥቃት ሰለባ የሆኑ ንጹሐን ሰዎችን ድምጽ እንደ ሚወክል የገለጹ ሲሆን በመቀጠል “እርሱም በብርታት የተሞላ የእምነት ምስክርነት ሥራ ነበር፣ እያንዳንዳችን አንድ እድል አለን፣ ዝም ማለት ወይም ትንቢት መናገር ከእዘዚህ አንዱን መምረጥ ይኖርብናል” ብለዋል።

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ በነጋሳኪ ከተማ ላይ ደርሶ የነበረውን አደጋ ላይ ትኩረት በማደረግ በከተማዋ “ላይ የደርሰው አደጋ እና ውድመት አሰቃቂ ነው፣ ለመፈወስ አሰቻጋሪ የሆነ ቁስል ነው፣ ባለፈው ጊዜ እና አሁን ባሉት ጦርነቶች የተከሰቱ የሚገኙ እጅግ ብዙ እና ንጹሃን በሆኑ ሰዎች ላይ እየደርሰ የሚገኘውን በደል ለመረዳት አስቸጋሪ መሆኑን ገልጸው በአሁኑ ወቅት በዓለም ዙሪያ የሚታዩ ግጭቶች መከራዎች፣ ጦርነቶች ለሦስተኛው የዓለም ጦርነት ነጋሪት እየጎሰሙ እንደ ሚገኙ ያሳያል ብለዋል።

ከኢየሱስ ጎን ተሰቅሎ እንደ ነበረው ሰው እኛም “ድምፃችንን ከፍ እናድርግ እና አሁን በእዚህ አሰቃቂ በሆነ ጦርነት እና ግጭቶች ምክንያት እየተሰቃዩ ለሚግኙ ሰዎች ድምጻችንን በማሰማት በጋራ በጽሎት መንፈስ መጮኽ ይገባናል” ካሉ በኋላ ቅዱስነታቸው ለእለቱ ያዘጋጁትን ስብከት አጠናቀዋል።

 

Photogallery

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ በጅፓን ሂሮሽማ መስዋዕተ ቅዳሴ ማሳረጉበት ወቅት
24 November 2019, 16:57