ፈልግ

ር.ሊ.ጳ ፍራንቸስኮስ በቫቲካን በጳውሎስ 6ኛ የስብሰባ አዳራሽ ር.ሊ.ጳ ፍራንቸስኮስ በቫቲካን በጳውሎስ 6ኛ የስብሰባ አዳራሽ 

ር.ሊ.ጳ ፍራንቸስኮስ “በተከፈተው የድክመታችን በር የእግዚኣብሔር የማዳን ኃይል ይገባል!”

ር.ሊ.ጳ ፍራንቸስኮስ “በተከፈተው የድክመታችን በር የእግዚኣብሔር የማዳን ኃይል ይገባል!”

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ ዘወትር ረዕቡ እለት በቫቲካን በሚገኘው የጳውሎስ 6ኛ የስብሰባ አዳራሽ ወይም ደግሞ እዳስፈላጊነቱ እና እንደ አየሩ ሁኔታ በቅዱስ ጴጥሮስ አደባባይ ለሚሰበሰቡ ምዕመናን እና የሀገር ጎብኝዎች በተለያዩ አርእስቶች ላይ ተመርኩዘው የጠቅላላ የትምህርተ ክርስቶስ አስተምህሮ እንደ ሚያደርጉ ይታወቃል።

ቅዱስነታቸው ከዚህ ቀደም ከወራት በፊት በምስጢረ መሮን ዙሪያ ላይ በተከታታይ ያደርጉት የነበረውን የጠቅላላ የትምህርተ ክርስቶስ አስተምህሮ አጠናቀው ከሳምንታት በፊት በእግዚኣብሔር ትዕዛዛት ዙሪያ ቀጣይነት ያለው አስተምህሮ ማድረግ መጀመራቸውን ቀድም ባሉት ጊዜያት ባስተላለፍናቸው ዝግጅቶቻችን መግለጻችን ይታወሳል።

በዚህም መሰረት በሰኔ 6/2010 ዓ.ም ቀትር ላይ በቫቲካን በሚገኘው በቅዱስ ጴጥሮስ አደባባይ ለተሰበሰቡ ምዕመናን ባደርጉት የክፍል አንድ የጠቅላላ የትምህርተ ክርስቶስ አስተምህሮ እንደ ገለጹት “እግዚኣብሔር ገዢያችን ሳይሆን አባታችን ነው” ማለታቸውን መግለጻችን የሚታወስ ሲሆን በሰኔ 13/2010 ዓ.ም ደግሞ አሁንም በቫቲካን በሚገኘው በቅዱስ ጴጥሮስ አደባባይ ለተሰበሰቡ ምዕመናን ባደረጉት የክፍል ሁለት የጠቅላላ አስተምህሮ “የእግዚኣብሔርን ቃል ኪዳን በሕይወታችን ለመተግበር በሚያስችሉን” ዐሥርቱ ትዕዛዛት ዙሪያ ላይ ያተኮረ አስተምህሮ ማደርጋቸውንም መገለጻችን ይታወሳል።

በሰኔ 20/2010 ዓ.ም ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ ባደረጉት የክፍል ሦስት የጠቅላላ የትምህርተ ክርስቶስ አስተምህሮ “ሕግ ከእግዚእብሔር ፍቅር በላይ ሆኖ ሲታይ ትርጉም ያጣል፣ እመንት ሊጀምር የሚገባው ከነጻናት ስሜት ነው እንጂ ከግዴታ ሊሆን አይገባውም” ማለታቸውን መግለጻችን የሚታወስ ሲሆን ከዚያም በመቀጠል በሰኔ 27/2010 ዓ.ም ባደረጉት የክፍል አራት የጠቅላላ የትምህርተ ክርስቶስ አስተምህሮ ከአስርቱ ትዕዛዛት የመጀመሪያው በሆነውን “ከእኔ በቀር ሌላ አምላክ አትምልክ” በሚለው የመጀመሪያው ትዕዛዝ ዙሪያ ላይ ትኩረቱን ያደረገ የጠቅላላ አስተምህሮ ማድረጋቸውን መገለጻችን ይታወሳል።

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ ከዚህ ቀደም በተከታታይ በዕስርቱ ቃላት/ትዕዛዛት ላይ ተመርኩዘው ያደርጉትን የጠቅላላ የትምህርተ ክርስቶስ አስተምህሮ ይህንን ያህል ካስታወስናችሁ በዛሬው እለት ማለትም በነሐሴ 02/2010 ዓ.ም ያደርጉት ክፍል አምስት የጠቅላላ የትምህርተ ክርስቶስ አስተምህሮ መሰርቱን አድርጎ የነበረው “ጣዖትን አታምልክ” በሚለው ሁለተኛው ትዕዛዝ ላይ ትኩረቱን በማድረግ “በተከፈተው የድክመታችን በር የእግዚኣብሔር የማዳን ኃይል ይገባል!” ማለታቸውን ለመረዳት ተችሉዋል።

በእለቱ የተነበቡ ምንባባት

ከዚያም እግዚአብሔር (ያህዌ) ሙሴን፣ “ከግብፅ ያወጣኻቸው ሕዝብህ ስተዋልና ውረድ አለው፤ ካዘዝኋቸው ፈቀቅ ለማለት ፈጣኖች ሆኑ፤ ለራሳቸውም በጥጃ ምስል የተቀረጸ ጣዖትን ሠሩ፤ ለእርሱም ሰገዱለት፤ ሠዉለትም፤ እንዲሁም፣ ‘እስራኤል ሆይ፤ ከግብፅ ምድር ያወጡህ አማልክትህ እነዚህ ናቸው’ ” አሉ (ዘጸ. 32፡7-8)።

የዚህ ዝግጅት አቅራቢ መብራቱ ኃይሌጊዮርጊስ-ቫቲካን

ክቡራን እና ክቡራት የዝግጅቶቻችን ተከታታዮች ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ በዛሬው እለት ማለትም በነሐሴ 02/2010 ዓ.ም በቫቲካን በሚገኘው በጳውሎስ 6ኛ የስብሰባ አዳራሽ ለተገኙ ምዕመናን ያደረጉትን የጠቅላላ የትምህርተ ክርስቶስ አስተምህሮ ሙሉ ይዘቱን እንደ ሚከተለው ተርጉመነዋል አብራችሁን በመሆን እንድትከታተሉን ከወዲሁ እንጋብዛለን።

የተወደዳችሁ ወንድሞቼ እና እህቶቼ እንደምን አረፈዳችሁ!

በአስርቱ ትዕዛዝት ዙሪያ የጀመርነውን አስተንትኖ ዛሬም በመቀጠል አሁን ደግሞ ጣዖት ማምለክ በሚለው ጭብጥ ዙሪያ ላይ ይህንኑ ጣዖት ማምለክ በተመለከተ ቀደም ሲል ከኦሪት ዘጸሃት (32፡1-8) ተወስዶ በተነበበው ምንባብ ላይ የተጠቀሰውን  የወርቅ ጥጃ ዛሬ በጥልቀት እንመለከታለን። የዚህ ትዕይንት ክፍል የእውነታውን ትክክለኛ ዐውደ ቁልጭ አድርጎ ያሳየናል-ወይም ያመለክተናል፣ ይህም ማለት ሕዝቡ ሙሴን በበረሃማ ቦታ ሆኖ እየጠበቁት ነበር፣ ሙሴ ደግሞ እግዚኣብሔር የሚሰጠውን መመሪያ ለመቀበል ወደ ተራራ ወጥቶ ነበር።

በረሃ ምንድን ነው? ውሃ፣ ምግብና መጠለያ የማይገኝበት እርግጠኞች የማንሆንበት እና ስጋት የሰፈነበት ሥፍራ ነው። በረሃ በእርግጠኛ ሁኔታ የማይኖርበት እና ምንም ዓይነት ዋስትና የሌለበት የሰዎች ሕይወት ምስል ነው። ይህ እርግጠኛ ያለመሆን ስሜት ኢየሱስ በቅዱስ ወንጌል ውስጥ “ምን እንበላለን?፣ ምን እንጠጣለን?፣ ምን እንለብሳለን?” (ማቴ 6፡13) በማለት የተናገራቸውን ጭንቆቶችን በሰዎች ሕይወት ውስጥ ይፈጥራል።

እናም በዚያ በረሃ ውስጥ “ሙሴ ከተራራው ላይ ሳይ ወርድ ብዙ መቆየቱን ባዩ ጊዜ” (ዘጸ. 321) ሕዝቡ የጣዖት አምልኮ እንዲጀመር የሚያደርግ አንድ ሁኔታ ይፈጠራል። ሕዝቡ አንድ በዋቢነት የሚያየው ሰው ይፈልጋል፣ እርግጠኛ የሆነ መሪ ይፈልጋል፣ ይህም በመጉደሉ የተነሳ ጉዳዩ መሸከም ከሚችሉት በላይ ይሆንባቸዋል። በዚህም ምክንያት ሕዝቡ አንድ በዓይን የሚታይ ተጨባጭ የሆነ፣ በዋቢነት ሊጠቅሱት የሚችሉት እና የሚመራቸው አምላክ እንዲኖራቸው ፈለጉ። በዚህም ምክንያት የተነሳ ሕዝቡ  “ናና በፊታችን የሚሄዱ አማልክትን ሥራል” (ኦዘ 32፡1) በማለት አሮንን ይጠይቁታል። የሰው ልጅ ተፈጥሮኣዊ ባሕሪ እግዚኣብሔር ራሱን ካልገለጸ ከጊዜያዊ ችግሮች ለመሸሽ ከእግዚኣብሔር ጋር ሊሰተካከል የሚችል “እሱ ራሱ በራሱ አቅም ወደ አበጀው” ሃይማኖት ይሸሻል። “አንድ ሰው በጣዖት ፊት ለፊት ቆሞ የጥርጣሬ ስሜቱን የሚያስወግድለት ጥሪ ሊሰማ በፍጹም አይችልም፣ ምክንያቱም ጣዖቶች “አፍ አላቸው ግን አይናገሩምና” (መዝ. 115፡5)። ስለዚህ ጣዖት “እኛ የራሳችንን የእጅ ሥራ ውጤቶች የሆኑ ነገሮችን ለማምለክ’ ያስችለን ዘንድ እኛ ራሳችንን በእውነታው መአከል ውስጥ ለማስገባት የምንጠቀምበት ቅድመ ሆኔታ ነው።

አሮን የሕዝቡን ጥያቄ በፍጹም መቃወም ስላልቻለ የጥጃ ምስል በወርቅ ሠራላቸው። ጥጃ በጥንት ጊዜ በነበሩ ምስራቃዊያን ዘንድ ሁለት ትርጉም ነበረው፣ በአንድ በኩል የልምላሜ እና የበረከት ምልክት ተደርጎ ይቆጠር የነበረ ሲሆን በሌላ በኩል ደግሞ የኃይል እና የጉልበት ተምሳሌት ተደርጎ ይቆጠር ነበር። በተለይም ደግሞ ወርቅ የሐብት ምልክት ተደርጎ ይቆጠር ነበር። ስኬት፣ ስልጣን ጉልበት። ከጥንት ጊዜ ጀምሮ የነበሩ አሁንም የሚቀጥሉ ፈተናዎች ናቸው። በወርቅ የተሠራው ጥጃ ይህ ነው፣ ነጻ የመሆን ፍልጎቶቻችንን የሚያሟሉ የሚመስሉ ቅዥቶች፣  ነገር ግን ባርነት ውስጥ የሚከቱን ነገሮች ናቸው።

ነገር ግን እነዚህ ነገሮች ሁሉ የተፈጠሩት በተለይም ደግሞ በእግዚኣብሔር መታመን ባለመቻላችን፣ ደኅንነታችንን በእርሱ ውስጥ ባለማደራጋችን፣ የልባችንን ፍላጎት ወይም መሻት በጥልቅ የሚፈጽምልን እርሱ መሆኑን ባለማመናችን ነው። በእርሱ መታመናችን ደግሞ ድክመቶቻችንን እንድናሸንፍ፣ ጥርጣሬዎቻችንን እና ጊዜያዊ ፍላጎቶቻችንን በሙሉ እንድናሸንፍ ይረዳናል። እግዚኣብሔርን አስቀድምን ካልያዝን ግን በቀላሉ በጣዖት እጅ ውስጥ እንወድቃለን እርግጠኛ መሆን ተስኖን በመካራ ውስጥ በመግባት ደስታችንን እንነፈጋለን።

ሐብታም ሆኖ ሳለ ለእኛ ብሎ ራሱን ዝቅ ያደርገውን የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ አባት የሆነውን እግዚኣብሔር አጥብቀን ከያዝን ከዚያን በኋላ የእኛ የራሳችን ድክመት ሰብዓዊ ከሆነ እርግማን የመጣ እንዳልሆነ በመገንዘብ ከእኛ ይልቅ ጠንካራ ለሆነ ኃይል ራሳችንን በእውነት እንድንከፍት ያደርገናል። ከዚያም በኋላ በከፈትነው የድክመታችን በር በኩል የእግዚኣብሔር የማዳን ኃይል ይገባል፣ በቂ ያልሆነውን ኃይል በማጎልበት የሰው ልጅ ኃይል ራሱን አባት ለሆነ ለእግዚኣብሔር እንዲከፍት ያደርጋል። የሰው ልጅ እውነተኛ ነጻነት የሚያገኘው እውነተኛ ጌታ እግዚኣብሔር ብቻ መሆኑን ሲቀበል ነው። ይህ ደግሞ አንድ ሰው የእራሱን ድክመቶች እንዲቀበል እና በልባችን ውስጥ የሚገኙ ጣዖቶችን እንዲያስወግድ ያስችለዋል።

እኛ ክርስቲያኖች ደካማ፣ የተናቀ እና ያለውን ነገር ሁሉ የተገፈፈውን በመስቀል ላይ ወደ ተሰቀለው ኢየሱስ እይታችንን እናድርግ። በእርሱ ላይ አነጸባራቂ የሆነ ውሸትን ሳይሆን እውነተኛውን እና ትክክለኛውን የእግዚኣብሔር ፊት እና የፍቅር ታላቅነት ይገለጻል። ነቢዩ ኢሳያስ “በእርሱ ቁስል እኛ ተፈወስን” (ት.ኢሳ. 53፡5) ይለናል። የእኛ ደኅንነት የመጣው ራሱን ድኸ ባደረገው፣ ድክመታችንን በተቀበለው፣ ጊዜያዊ በሆነው ሕይወታችን ውስጥ በጥልቀት ገብቶ በፍቅር እና በኃይል ከሞለው ከእርሱ ነው። እርሱ ወደ እኛ የመጣው የእግዚኣብሔርን አባትነት ለመገለጽ ነው፣ የእኛ ድክመቶች በክርስቶስ አማካይነት ከእርግማንነት ተቀይረው ከአባታችን ጋር የምንገናኝበት ስፍራ እና ከላይ የሚመጣውን አዲስ ኃይለ የምናገኝበት ምንጭ ይሆናል ማለት ነው።

ር.ሊ.ጳ ፍራንቸስኮስ በነሐሴ 02/2010 ዓ.ም ያደረጉት የጠቅላላ የትምህርተ ክርስቶስ አስተምህሮ
08 August 2018, 16:10