ፈልግ

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ  29/09/2010 ዓ.ም በቫቲካን በሚገኘው በቅድስት ማርታ የጸሎት ቤት ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ 29/09/2010 ዓ.ም በቫቲካን በሚገኘው በቅድስት ማርታ የጸሎት ቤት   (© Servizio Fotografico L'Osservatore Romano)

ር.ሊ.ጳ. ፍራንቸስኮስ ክርስቲያኖች “ወደ ዓለም እቅዶች አትመለሱ ነጻነታችሁን ይገፋሉና”

“ወደ ዓለም እቅዶች አትመለሱ ነጻነታችሁን ይገፋሉና”

 

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮ በግንቦት 21/2010 ዓ.ም በቅድስት ማርታ የጸልሎት ቤት ባሳረጉት መስዋዕተ ቅዳሴ ላይ ባሰሙት ስብከት እንደ ገለጹት “ወደ ዓለም እቅዶች አትመለሱ ነጻነታችሁን ይገፋሉና” ማለታቸው የተገለጸ ሲሆን ወደ ቅድስና ሕይወት የምናደርገውን ጉዞ አጠናክረን መቀጠል ይገባል እንጂ ወደ ዓለማዊ እቅዶች መመለስ የለብንም ማለታቸውን ለመረዳት ተችሉዋል።

የዚህ ዜና አቀናባሪ መብራቱ ኃይሌጊዮርጊስ ቫቲካ

ከፍተኛ ፈተና በሚገጥማችሁ ሰዓት ዓለማዊ ወደ ሆኑ እቅዱች ውስጥ በፍጹም መግባት አይኖርባችሁም በማለት ስብከታቸውን የቀጠሉት ቅዱስነታቸው ዓለማዊ በሆኑ እቅዶች ውስጥ መግባት ወይም መዘፈቅ ነጻነታችሁን ይገፋል፣ በእዚህም ምክንያት ማነኛውም ዓይነት ፈተና በሚገጥመን ሰዓት ወደ ቅድስና ሕይወት የሚወስደውን መንገድ በብርታት መጓዝ ያስፈልጋል ብለዋል።

ቅዱስ መሆን ማለት ቅዱሳን ያላቸውን ዓይነት ፊት ሊኖረን ይገባል ማለት አይደለም

በእለቱ የአውሮፓዊያኑን የቀን አቆጣጠር በሚከተሉ የክርስቲያን ማሕበረሰቦች ዘንድ በላቲን ስርዓተ አምልኮ አቆጣጠር ደንብ መሰረት በቀዳሚነት 1 ጴጥሮስ 1፡10-16 ተወስዶ በተነበበው የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል ላይ ተመርኩዘው ቅዱስነታቸው በስብከታቸው የሚከተለውን ብለዋል. . .

“የቅድስና ጥሪ፣ የተለመደ ጥሪ ነው፣ እንደ አንድ ክርስቲያን ሆኖ የመኖር ጥሪ ነው፣ ይህም ማለት እንደ አንድ ክርስቲያን ሆኖ መኖር ማለት እንደ ቅዱስ ሆኖ መኖር ማለት ነው። ብዙን ጊዜ እኛ ስለቅድስና ስናስብ ልክ እንደ አንድ ለየት ያለ ነገር አድርገን በመቁጠር ርእይ የሚታይበት ወይም በጣም ልዩ የሆነ ጸሎት የሚደረግበት ነገር አድርገን እንቆጥራለን። ወይም ደግሞ ቅዱስ መሆን ማለት በጣም ልዩ የሆነ ቅዱሳኖች ያላቸው ዓይነት ፊት ያለው ሰው አድርገን ልናስብ እንችል ይሆናል . . .በፍጹም እንዲህ አይደለም። ቅዱስ መሆን ማለት ከእዚህ የተለየ ነገር ነው። ጌታ ስለቅድስና በተናገረው መንገድ ላይ መጓዝ ማለት ነው። ታዲያ በቅድስና መንገድ መጓዝ ማለት ምን ማለት ነው? ቅዱስ ጴጥሮስ ይህንን በተመለከተ እንዲህ ይላል፡ “ስለዚህ ልባችሁን አዘጋጁ፤ ራሳችሁንም ግዙ፤ ተስፋችሁን ኢየሱስ ክርስቶስ ሲገለጥ ለእናንተ በሚሰጠው ጸጋ ላይ ሙሉ በሙሉ አድርጉ”።”

ወደ ብርሃን መጓዝ

ስለእዚህ “ወደ ቅድስና መጓዝ” ተስፋችን ወደ ሆነው ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ ግልጽት እና ጸጋ መጓዝ” ማለት እንደ ሆነ በመጥቀስ ስብከታቸውን የቀጠሉት ቅዱስነታቸው ይህም በብርሃን መንገድ ላይ እንደ መጓዝ ይቆጠራል ብርሃን ባለበት መነገድ ላይ በምንጓዝበት ወቅት ሁሉ ብርሃኑ መንገዳችንን ቁልጭ አድርጎ ስለሚያሳይ አንሰናከልም ብለዋል።

ቀድሞ ወደ ነበሩን ዓለማዊ እቅዶች ተመልሰን መግባት የለብንም

በቅድስና መንገድ ላይ ለመጓዝ ነጻ እና የነጻነት ስሜት የሚሰማን ሰዎች ልንሆን እንደ ሚገባን በመጥቀስ ስብከታቸውን የቀጠሉት ቅዱስነታቸው ነገር ግን በሕይወታችን ጠፍረው ይዘውን ባሪያ የሚያደርጉን ብዙ ነገሮች እንዳሉ ጠቅሰው ይህም ልክ ሐዋሪያው ጴጥሮስ  “ቀድሞ ባለማወቅ ትኖሩበት የነበረውን ክፉ ምኞት አትከተሉ” እንደ ሚለን ሁሉ እኛም ከቀድሞ ምኞቶቻችን ተላቀን ወደ ፊት መጓዝ ይኖርብናል ብለዋል። ይህንን በተመለከተ ደግሞ ቅዱስነታቸው የሚከተለውን ብለዋል. . .

“ይህንን ትርጉም በተመለከተ ትክክለኛው ምክር ይህ ነው-ዓለማዊ በሆኑ እቅዶች ውስጥ አትግቡ፣ ስለዓለም ለማሰብ ዓለማዊ በሆኑ እቅዶች ውስጥ አትግቡ ፣ ዓለም በስጦታነት ለሚያቀርብላችሁ ሐሳብ እና ውሳኔ አትቀበሉ ምክንያቱም ይህ ጉዳይ ነጻነታችሁን ይገፈዋልና። በቅድስና መንገድ ላይ ለመጓዝ ነጻ መሆን ያስፈልጋል፡ ብርሃንን እያዩ ወደ ፊት ለመሄድ የሚያስችል ነጻነት ያስፈልጋል፣ በነጻነት ወደ ፊት መሄድ ያስፈልጋል። ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ከመገናኘታችን በፊት ወደ ነበርንበት ወደ ቀድሞ ዓለማዊ ሕይወታችን በምንመለስበት ወቅት ወይም ደግሞ ዓለማዊ ወደ ሆኑ እቅዶች ውስጥ ተመልሰን በምንገባበት ወቅት ነጻነታችንን ሙሉ በሙሉ እናጣለን።”

በቅድሚያ ነጻ የሆንን ሰዎች ካልሆንን በስተቀር ቅዱስ መሆን በፍጹም አንችልም

በቅድሚያ ነጻ የሆንን ሰዎች ካልሆንን ቅዱስ መሆን በፍጹም አንችልም በማለት ስብከታቸውን የቀጠሉት ቅዱስነታቸው በኦሪት ዘፍጥረት መጽሐፍ ውስጥ ተጠቅሶ እንደ ምናገኘው በወቅቱ የነበሩ የእስራኤል ሕዝቦች በበረሃ ጉዞዋቸው ወደ ደኽንነት የሚወስዳቸውን የጉዞ መስመር አሻግረው መመልከት አቁመው በተቃራኒው ወደ ኃላቸው መመልከት ፈልገው እንደ ነበረ የገለጹት ቅዱስነታቸው በወቅቱ በበረሃ ይጓዙ የነበሩ የእስራኤል ልጆች በእግዚኣብሔር ላይ ያጉረመርሙ ነበር፣ በቀድሞ ጊዜ በግብፅ በባርነት ቀነበር ሥር በነበሩበት ወቅት የነበረውን ዓይነት ሕይወት፣ ለምሳሌም ሽንኩርት እና ሥጋ በመመኘት ያለፈው ጊዜያቸውን ያስቡ እንደ ነበረ ያስታወሱት ቅዱስነታቸው “ፈተናዎች እና ችግሮች በሚያጋጥሙዋቸው ወቅቶች ሁሉ ሕዝቡ ወደ ኃላ ተመለሱ በእዚህም ድርጊታቸው ነጻነታቸውን አጡ፣ እውነት ነው በግብፅ በሚኖሩበት ወቅት ጥሩ የሆነ ምግብ ይመገቡ ነበር፣ ነገር ግን ምግቡ ጥሩ ይሁን እንጂ የሚመገቡት በባርነት ቀንበር ሥር ሆነው ነበር ብለዋል።

በፈተና እና በመከራ ጊዜያት ወደ ኃላ አትመልከቱ

“በፈተና እና በመከራ ጊዜያት ወደ ኃላ አትመልከቱ” በማለት ስብከታቸውን የቀጠሉት ቅዱስነታቸው ይህንን በተመለከተ ደግሞ የሚከተለውን ብለዋል. . .

“በሕይወት ውስጥ ፈተናዎች በሚገጥሙን ጊዜያት ሁሉ እኛ ወደ ኃላ የመመልከት ምኞት ያድርብናል፣ ዓለማዊ የሆኑ እቅዶችን መመኘት ይቀናናል፣ የደኽንነት ሕይወት ከመጀመራችን በፊት የነበረንን ዓይነት እቅድ መመልከት እንፈልጋለን፣ ይህም ነጻነታችንን ያሳጣናል። ነጻ ካልሆንን ደግሞ ቅዱስ ለመሆን አንችልም። ከፊት ለፊታችን ያለውን ብርሃን እየተመለከትን ለመጓዝ ከሚያስችሉን ቅድመ ሁኔታዎች ውስጥ አንዱ እና ዋነኛው ነጻ መሆን ነው። ዓለማዊ በሆኑ የዓለም እቅዶች ውስጥ በፍጹም እንዳትገቡ፣ ወደ ፊት ተጓዙ፣ ቃል ኪዳን የተገባልንን እና ተስፋችን የሆነውን ብርሃን ብቻ እየተመለከትን ወደ ፊት እንጓዝ፣ ይህ ቃል ኪዳን የእስራኤል ሕዝቦች በበረሃ በሚጓዙበት ወቅት የተገባላቸው ዓይነት ቃል ኪዳን ነው፣ ወደ ፊት አሻግረው እየተመለከቱ በሚጓዙበት ወቅት ሁሉ በጥሩ ሁኔታ ይጓዙ ነበር፣ ነገር ግን በግብፅ እያሉ ይሰጣቸው የነበረ ዓይነት ጥሩ ምግብ ባለመብላታቸው የተነሳ የቀድሞ ሕይወታቸውን በሚናፍቁበት ወቅት ሁሉ ይሳሳታሉ በእዚያ በነበሩበት ወቅት ነጻነት እንዳልነበራቸው ይዘነጋሉ።”

ወደ ቅድስና መጓዝ

ዓለማዊ እቅዶች ብዙ ነገር ቃል ይገቡልናል ነገር ግን ምንም ነገር አይሰጡንም

“ጌታ በእየለቱ ሁላችንንም ወደ ቅድስና ይጠራናል” በማለት ስብከታቸውን የቀጠሉት ቅዱስነታቸው ትክክለኛ በሆነው የቅድስና መንገድ ላይ መጓዛ አለመጓዛችንን ለማወቅ የሚረዱን ሁለት መመዘኛዎች እንዳሉ ጠቁመው በመጀመሪያ ደረጃ የጌታ ብርሃን እንደምናገኝ ተስፋ በማድረግ ወደ እዚያው አቅጣጫ አሻቅበን የምንመለከት ከሆን፣ በመቀጠልም መከራዎች ወይም ፈተናዎች በሚገጥሙን ጊዜያት ሁሉ ወደ ፊት መመልከታችንን በምንቀጥልበት ወቅት እንደ ሆነ ጠቅሰው “ብዙ ነገር ቃል የሚገቡልን ነገር ግን ምንም ነገር በማይሰጡን” ዓለማዊ አስተሳሰቦች ውስጥ አንዘፈቅም ነጻነታችንንም አናጣም ብለዋል። “እኔ ቅዱስ እንደ ሆንኩኝ እናንተም ቅዱሳን ሁኑ የሚለው ቃል የእግዚኣብሔር ትዕዛዝ እንደ ሆነ በመገለጽ ስብከታቸውን የቀጠሉት ቅዱስነታቸው እግዚኣብሔር በነጻነት በቅድስና መንገድ ላይ መራመድ ማለት ምን ማለት እንደ ሆነ፣ እንዲሁም ኢየሱስን ከመገናኘታችን በፊት በዓለማዊ እቅዶች ውስጥ ተዘፍቀን የኖርንባቸውን ጊዜያት መገንዘብ እንችል ዘንድ እንዲረዳን ጸጋውን ይሰጠን ዘንድ ልንማጸነው ይገባል ካሉ በኃላ ስብከታቸውን አጠናቀዋል።

 

29 May 2018, 10:06
ሁሉንም ያንብቡ >