ፈልግ

እስራኤል በከፈተችው ጥቃት የተገደሉት ት የበጎ አድርጎት ድርጅት ሠራተኖች እስራኤል በከፈተችው ጥቃት የተገደሉት ት የበጎ አድርጎት ድርጅት ሠራተኖች  

የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ምክር ቤት በጋዛ የሰባት የርዳታ ሰራተኞች መገደልን አወገዘ!

የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ምክር ቤት ዋና ፀሐፊ ከዓለም ሴንትራል ኪችን የእርዳታ ድርጅት በጣም አስፈላጊ የሆኑ ምግቦችን ወደ ጋዛ በመውሰድ ላይ የነበሩትን ሰባት የረድኤት ሠራተኞች መገደላቸውን በጽኑ ያወግዛሉ።

የእዚህ ዜና አቅራቢ መብራቱ ኃ/ጊዮርጊስ ቫቲካን

የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ምክር ቤት (WCC) በቅርቡ እስራኤል ጋዛ ላይ በፈጸመችው የአየር ጥቃት የበጎ አድራጎት ድርጅት የሆነው የዓለም ሴንትራል ኪችን የሚሰሩ ሰባት ሰዎች መገደላቸውን ተከትሎ ዓለም አቀፍ ተቃውሞውን ተቀላቅሏል።

የአውስትራሊያ፣ የብሪታንያ፣ የፖላንድ፣ የፍልስጤም እና የሁለት አሜሪካ-ካናዳ ዜግነት ያላቸው ሰባቱ የረድኤት ሰራተኞች ሰኞ ምሽት በጋዛ ሰርጥ ላሉ ፍልስጥኤማውያን በጣም የሚፈልገውን ምግብ ሲወስዱ የርዳታ ቁሳቁሶችን በጫኑ መኪኖች ላይ በእስራኤል በተተኮሱ የጦር መሣሪያዎች በተመቱበት ወቅት ነበር ሕይወታቸው ያለፈው።

ስለ ክስተቱ ገለልተኛ ምርመራ

በታዋቂው ሼፍ ጆሴ አንድሬስ የተመሰረተው ዎርልድ ሴንትራል ኪችን (WCK) ‘የዓለም መዓከላዊ ኩሺና’ የተሰኘው ዓለም አቀፍ የበጎ አድራጊት ድርጅት ሰራተኞቻቸው የበጎ አድራጎት ድርጅቱን አርማ ባጌጡ ሁለት የታጠቁ መኪኖች እና ሌላ ተሸከርካሪዎች እየተንከራተቱ እንደነበር እና እንቅስቃሴያቸውንም ከእስራኤል ጦር ጋር አስተባብረው እንደነበር ተናግሯል።

ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንጃሚን ኔታንያሁ ማክሰኞ መጋቢት 24/2016 ዓ.ም ግድያው በስህተት የተፈጸመ ነው ሲሉ የእስራኤል ጦር ጉዳዩን በተመለከተ ሙሉ ምርመራ ለማድረግ ቃል ገብተዋል።

አድማው በርካታ የበጎ አድራጎት ድርጅቶች በረሃብ አፋፍ ላይ የሚገኙትን ፍልስጤማውያን የምግብ አቅርቦትን እንዲያቆሙ ያነሳሳ ሲሆን እስራኤል በከበበችበት አካባቢ ያለውን አስከፊ ሰብዓዊ ሁኔታ ለማቃለል ርምጃ እንድትወስድ ዓለም አቀፍ ጫናዎችን አሳድጓል።

የሰብአዊ ርዳታ ሰራተኞች በግጭት ውስጥ በፍፁም ኢላማ መሆን የለባቸውም

የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ምክር ቤት ዋና ጸሃፊ ቄስ ጄሪ ፒላይ ግድያውን አውግዘው ለተጎጂ ቤተሰቦች እና ወዳጆች መጽናናትን ተመኝተዋል።

የሰብአዊ እርዳታ ሰራተኞች በግጭት ውስጥ በፍፁም ኢላማ መሆን የለባቸውም ሲሉ ቄስ ፒላይ ተናግሯል። "እንዲህ ያሉት የንጹሃንን ህይወት የሚቀጥፉ ጥቃቶች በፍፁም ተቀባይነት የሌላቸው እና በማንኛውም ደረጃ ምክንያት አድርጎ ማቅረብ የማይችሉ ናቸው" ሲሉ ተናግሯል። "ሁሉም የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ካውንስል አባል አብያተ ክርስቲያናት በጋዛ ፍትህ፣ ሰላም እና እርቅ እንዲሰፍን ድምፃቸውን እንዲያሰሙ ጥሪ እናቀርባለን ” ሲሉ ተናግረዋል።

ቄስ ፒላይ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የፀጥታው ምክር ቤት እ.አ.አ መጋቢት 25 ቀን በጋዛ ላይ ባወጣው ውሳኔ አፋጣኝ የተኩስ አቁም እና ሁሉም ታጋቾች በአስቸኳይ እንዲፈቱ ያሳሰቡትን መግለጫ ሲያጠቃልሉ “እነዚህ በንፁሀን ዜጎች ላይ የሚደርሰው ትርጉም የለሽ ግድያ መቆም አለበት” ብለዋል።

እ.አ.አ ከጥቅምት 7 ጀምሮ ወደ 200 የሚጠጉ የእርዳታ ሰራተኞች በጋዛ ተገድለዋል።

እንደ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ዘገባ ከሆነ ጦርነቱ ከተቀሰቀሰበት ጊዜ ጀምሮ በጋዛ ወደ 200 የሚጠጉ የእርዳታ ሰራተኞች ሃማስ በእስራኤል ላይ እ.አ.አ በጥቅምት 7 ላይ የሽብር ጥቃት ካደረሰ በኋላ ተገድለዋል። የቅርብ ጊዜ ክስተት በጋዛ ያለውን ተስፋ አስቆራጭ ሁኔታ ለማቃለል ከቆጵሮስ ለእርዳታ የባህር ኮሪደር ለመክፈት የሚደረገውን ጥረት ወደ ኋላ እንደሚያስቀር ያሰጋል።

በፍልስጤም ግዛት ውስጥ እየደረሰ ያለው ሰብአዊ አደጋ አሳሳቢነቱ ተባብሷል በቅርቡ የተቀናጀ የምግብ ዋስትና ደረጃ ምደባ (IPC) በመባል የሚታወቀው ድርጅት አጠቃላይ የጋዛ ህዝብ ከፍተኛ የምግብ እጦት እያጋጠመው እንደሆነ እና በጋዛ ሰሜናዊ ሰርጥ ክፍል ረሃብም ቀድሞውንም ተከስቶ እንደነበር ያሳያል።

 

04 April 2024, 15:34