ፈልግ

የአውስትራሊያ ብጹአን ጳጳሳት የአውስትራሊያ ብጹአን ጳጳሳት 

የአውስትራሊያ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን ጳጳሳት ጉባኤ ብሔራዊ የሥነ ምግባር ደንቦችን አወጣ

የአውስትራሊያ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን ጳጳሳት ጉባኤ “በጋራ ተልእኮአችን ውስጥ አንድነትን እናጎልብት” የሚል ደህንነትን የሚያረጋግጥ እና የቤተክርስቲያን መሪዎችን ጥቃት የማይታገስ ብሄራዊ የስነምግባር ህግ ይፋ አደረገ።

  አቅራቢ ዘላለም ኃይሉ ፥ አዲስ አበባ

በአውስትራሊያ ዙሪያ በሚገኙ የካቶሊክ አህጉረ ስብከቶች ውስጥ ለሚያገለግሉ ሰዎች በአውስትራሊያ የካቶሊክ ጳጳሳት ጉባኤ ብሔራዊ የሥነ ምግባር ደንብ ወጥቷል።

አዲሱ ሰነድ

መጋቢት 30 ቀን 2016 ዓ.ም. ታትሞ የወጣው ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ብጹአን ጳጳሳቱ “የአውስትራሊያ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን ጳጳሳት ጉባኤ ለህፃናት እና ለተጋላጭ ሰዎች ደህንነት የሚያደርገውን ቀጣይነት ያለው ቁርጠኝነት ለማጎልበት” መፍትሄ ነው ያሉትን ባለ 32 ገጽ ሰነድ አቅርበዋል።

ሰነዱ “በጋራ ተልእኳችን ውስጥ” በሚል ርዕስ ቀርቦ ህዳር 2015 ዓ.ም. በተካሄደው የጳጳሳቱ ምልአተ ጉባኤ ላይ የፀደቀ ሲሆን፥ ቀደም ሲል የነበሩትን ለአብነትም ‘በቄሳውስት እና ገዳማዊያን አገልግሎት ውስጥ ያለው አንድነት’ የሚል እና ‘በቤተክርስቲያን ለቤተክርስቲያን አገልግሎት ውስጥ ለሚሰሩ ምዕመናን አንድነት’ ተብለው ሲተገበሩ የነበሩ ሕጎችን እንደሚተካ ተነግሯል።

የንጉሳዊ ኮሚሽኑ ሕጻናት ላይ ለሚደርሱ ወሲባዊ ጥቃቶች ተቋማዊ ምላሾች እንደሚያስፈልጉ በጠየቀው መሠረት ይህ አዲሱ ሰነድ እንደወጣና የቀድሞዎቹን ወደ አንድ እና ወጥ የሆነ አቀራረብ እንደሚያመጣቸው ተገልጿል።

ይህ ሰነድ የብሔራዊ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን የህፃናት ጥበቃ መስፈርቶችን የሚያሟላ ሲሆን፥ ዓላማውም “የቀሳውስትን እና የሃዋሪያዊ ሥራ መሪዎችን በማቋቋም እና በማነሳሳት በሁሉም የሕይወታቸው መንገድ ግልፅ የሆነ አቋማቸውን እንዲያንጸባርቁ” ለመርዳት ነው ተብሏል።

ለካህናት ምስረታ አስፈላጊ ነው

የአውስትራሊያ ብጹአን ጳጳሳት በጋዜጣዊ መግለጫቸው ላይ “በሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ጥያቄ ወይም የመጨረሻ ክትትል ስር የሃዋሪያዊ ሥራ የሚያከናውን ማንኛውም ሰው የብሔራዊ የሥነ ምግባር ደንቡን ማክበር አለበት” ሲሉ ጽፈዋል። በተጨማሪም እንደየሁኔታው ለተወሰኑ ህጋዊ ውሎች፣ ስምምነቶች ወይም ሌሎች ግዴታዎች ተገዢ ሊሆኑ እንደሚችሉም ተገልጿል።

የጳጳሱ ቃላት

የጳጳሳት የባለሙያ መስፈርቶች እና ጥበቃ ኮሚሽን ሊቀ መንበር የሆኑት ብጹእ አቡነ ግሬግ ቤኔት ቤተ ክርስቲያኒቱ ለሚደርሱ ጥቃቶች ምንም ዓይነት ትዕግስት እንደሌላት በመግለጽ፥ “በጋራ ተልእኳችን ውስጥ ያለን ታማኝነት፥ ለህፃናት እና ለተጋላጭ ሰዎች ደህንነት ያለንን ቁርጠኝነት ለማደስ ወሳኝ ግብአት ነው” በማለት በአፅንዖት ተናግረዋል።

ጳጳሱ አክለውም “መርሆቹ ከሁሉም በቤተክርስቲያኑ አገልግሎት ላይ የተሰማሩ ሰዎች የሚጠበቁ ባህሪያትን ለመምራት፣ ለማነፅ፣ ለማጠናከር እና ለማረጋገጥ የተዘጋጁ ናቸው” ብለዋል።

ጋዜጣዊ መግለጫው በህጉ ውስጥ የተካተቱትን እንደ አካላዊ እና ስሜታዊ ድንበሮች፣ ለቅሬታዎች ምላሽ መስጠት፣ አዎንታዊ ግንኙነቶችን፣ የማህበራዊ ሚዲያዎች አጠቃቀም፣ በስራ ቦታ ላይ የሚፈጸሙ ጥቃቶች እና የፋይናንስ ስነምግባርን የመሳሰሉ አንዳንድ ጉዳዮችን በማንሳት ተጠናቋል።
 

09 April 2024, 14:01