ፈልግ

የሩምቤክ ሊቀ ጳጳስ ብጹእ አቡነ ክርስቲያን ካርላሳሬ- የፋይል ፎቶ የሩምቤክ ሊቀ ጳጳስ ብጹእ አቡነ ክርስቲያን ካርላሳሬ- የፋይል ፎቶ  

የደቡብ ሱዳኑ ብጹእ አቡነ ካርላሳሬ የትንሳኤ በዓል የነጻነት እና አዲስ ህይወት ይሁንልን አሉ

የሩምቤክ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የሆኑት ብጹእ አቡነ ክርስቲያን ካርላሳሬ ለደቡብ ሱዳን ምእመናን የትንሳኤ መልእክት ያስተላለፉ ሲሆን፥ ክርስቲያኖች በወዳጅነት እርስ በርስ ለመደጋገፍ እና ለመዋደድ እንዲያስችላቸው ወደ ትንሳኤው ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንዲመለከቱ አበረታተዋል።

  አቅራቢ ዘላለም ኃይሉ ፥ አዲስ አበባ

ከፍርሃታችን ነፃ ስንወጣ፥ የኛ መኖር ሌሎችን ነፃ ያወጣል።

የነጻነት እና የህይወት ትንሳኤ ለመለማመድ በዐብይ ፆም የተጓዝንበት ጉዞ ይህ ነው፥ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ጉዞ ከእኛ ጋር ነበር።

የመስቀሉን መንገድ ወደ ህይወት መንገድ እንዴት እንደሚለውጠው ያውቃል፥ ይሄም እርስ በርሳችን የምንገናኝበት፣ አብረን የምንጓዝበት እና እንደ ማህበረሰብ ፈተናውን የምንወጣበት መንገድ ነው። መስቀሉን በሌሎች ላይ አንጭንም፥ ግን አብረን እንሸከማለን፥ ኢየሱስ መስቀሉን ከእኛ በፊት ተሸክሞ ነበር፣ ዛሬ ደግሞ ከእኛ ጋር ተሸክሞታል። ጨለማንና ሞትን አሸንፏል፥ እርሱ የዓለም ብርሃን ነው።

ብርሃንን ለምን እንፈራለን? የዚህ ብርሃን መገለጫ ለመሆን መፍራት ያለብን ለምንድን ነው? ሁላችንም የተወለድነው በእያንዳንዳችን ውስጥ ያለውን የእግዚአብሔርን ውበት ለማሳየት ነው። እናም የእግዚአብሔር ብርሃን በውስጣችን እንዲበራ ስንፈቅድ፣ ሳናውቀው ሌሎችም እንደዛው እንዲያደርጉ እድል እንሰጣለን። ይህ ነው ተስፋችን፥ ሞት ብቻ በሚመስል ቦታ ህይወትን የሚለውጥ እና በመልካም መንገድ እንዲፈስ የሚያደርግ እምነት።

ባለፈው ክፍለ ዘመን የኖሩ አንድ ታዋቂ ሐኪም ከእንፋሎት የበለጠ፣ ከኤሌትሪክ ኃይል፣ ከአቶሚክ ሃይል የበለጠ የሚንቀሳቀስ ኃይል እንዳለ ይናገሩ ነበር፥ ይሄም ፍላጎት ይባላል። ሌላም ምሳሌያዊ አነጋገር አለ፥ 'ፍላጎት ካለ መንገድ አለ' ይላል። እና እኔም አንድ ነገር እጨምርበታለሁ፥ ‘በጎ የሆነ ፍላጎት’።

ፍላጎታችን ሊያሳስተን ይችላል፥ ነገር ግን ለበጎ ነገር የታሰበ ፍላጎት ወደ ሩቅ ቦታ፣ ወደፊት ሊወስደን ይችላል። እናም ወዳጅነት በጉዞ ወቅት አስደሳች ነገር ነው።

ባለፈው ጥር፣ 84 ወጣቶች ከበርካታ ማህበረሰቦች ጋር በመሆን ከሩምቤክ ወደ ቶንጅ የሰላም ጉዞ እንድናደርግ በጠንካራ ፍላጎታቸው አነሳስተውናል። በተጨማሪም በስብከተ ወንጌል ሥራ እና በትንሣኤው ጌታ ስም የምናደርገው ማንኛውም ሥራ የመላው ሀገረ ስብከት ልምድ ነው።

ገና የምንጓዘው ረጅም መንገድ አለ፥ ግን መቼም ቢሆን ብቻችንን አይደለንም፥ ሁሌም በብርሃኑ ስር ነን።
'መልካም የትንሳኤ በዓል ይሁንልን' በማለት መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።
 

29 March 2024, 11:34