ፈልግ

የአፍሪካ እና የማዳጋስካር ጳጳሳት ጉባሄዎች ሕብረት ፕሬዚደንት የሆኑት ብፁዕ ካርዲናል ፍሪዶሊን አምቦንጎ የአፍሪካ እና የማዳጋስካር ጳጳሳት ጉባሄዎች ሕብረት ፕሬዚደንት የሆኑት ብፁዕ ካርዲናል ፍሪዶሊን አምቦንጎ 

የአፍሪካ ቤተክርስቲያን የተመሳሳይ ጾታ ጥንዶችን ሳትባርክ 'ከጳጳሱ ጋር ያላትን ሕብረት ትጠብቃላች”!

በእንግሊዘኛው ምጻረ ቃል “SECAM” (Symposium of the Episcopal Conferences of Africa and Madagascar፣ ‘የአፍሪካ እና የማዳጋስካር ጳጳሳት ጉባሄዎች ሕብረት) ፕሬዚደንት የሆኑት ብፁዕ ካርዲናል ፍሪዶሊን አምቦንጎ፣ የአፍሪካ አብያተ ክርስቲያናት “Fiducia supplicans” (የእምነት ተማጽኖ) በሚል አርዕስት በቅርቡ ይፋ በሆነው ሰነድ ላይ ማሰላሰላቸውን እንደሚቀጥሉ ገልጸው፣ “ከርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ ጋር ያላቸውን የማያወላውል ግንኙነት” በማረጋገጥ እና የእያንዳንዱን ጳጳስ በራሳቸው ሀገረ ስብከት ውስጥ ያለውን ነፃነት በማጉላት ላይ ይገኛሉ።

የእዚህ ዝግጅት አቅራቢ መብራቱ ኃ/ጊዮርጊስ ቫቲካን

“በአፍሪካ ውስጥ የሚገኙ የጳጳሳት ጉባሄዎች ከርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ ጋር ያላቸውን ግንኙነት አጥብቀው እያረጋገጡ በመላው አፍሪካ የሚገኙ የጳጳሳት ጉባሄዎች “Fiducia supplicans” (የእምነት ተማጽኖ) መግለጫ ላይ የቀረበው ከሥርዓተ-አምልኮ ውጪ የሆኑ ቡራኬዎች ራሳቸውን ለአጭበርባሪዎች ሳያጋልጡ በአፍሪካ ሊከናወኑ እንደማይችሉ ያምናሉ” ሲሉ ገልጸዋል።

የኪንሻሳ ሊቀ ጳጳስ እና የ SECAM (የአፍሪካ እና ማዳጋስካር ጳጳሳት ጉባሄዎች) ፕሬዚደንት ብፁዕ ካርዲናል ፍሪዶሊን አምቦንጎ ቤሱንጉ የእምነት ጉዳዮችን የሚመለከተው የቅድስት መንበር ጽ/ቤት መግለጫ ላይ የቀረበውን “ተጨማሪ ሥነ-ሥርዓታዊ” ቡራኬዎችን በተመለከተ የአፍሪካ ጳጳሳት ያላቸውን አቋም የሚገልጽ ደብዳቤ አሳትመዋል።

እ.አ.አ በታኅሳስ 18/2023 ዓ.ም ላይ የታተመው “Fiducia supplicans” (የእምነት ተማጽኖ) በካቶሊክ ሥነ ምግባር መሠረት ተመሳሳይ ጾታ ያላቸውን ጥንዶች ጨምሮ “ያልተለመዱ” ሁኔታዎች ውስጥ ጥንዶችን የመባረክ ዕድል ይከፍታል ፣ ምንም እንኳን ቡራኬው ከማንኛውም የአምልኮ ሥርዓት ውጭ መሆን አለበት እና በጭራሽ የሠርግ ሥነ-ሥረዓትን መምሰል የለበትም ቢልም።

ሐሙስ ጥር 2/2016 ዓ.ም ዕለት የተለቀቀው የብፁዕ ካርዲናል አምቦንጎ ደብዳቤ በአፍሪካ አህጉር ውስጥ በተለያዩ ብሄራዊ እና አህጉር አቀፋዊው የጳጳሳት ጉባሄዎች የተቀበሉትን አቋም "የተጠናከረ ማጠቃለያ" አቅርቧል።

በደብዳቤው መሠረት “Fiducia supplicans” (የእምነት ተማጽኖ)  “ድንጋጤ” ፈጥረዋል እና “በብዙ ምዕመናን፣ ገዳማዊያን ገዳማዊያት እና ኤጲስ ቆጶሳት አእምሮ ውስጥ የተሳሳቱ አመለካከቶችን እና አለመረጋጋትን ዘርተዋል እናም ጠንካራ ምላሽ ሰጥተዋል።

ካርዲናል አምቦንጎ ደብዳቤው “የብፁዕ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ እና የብፁዕ ካርዲናል ቪክቶር ማኑኤል ፈርናንዴዝ በቅድስት መንበር የእመነት ጉዳዮችን የሚመለከተው ጳጳሳዊ ጽ/ቤት አስተዳዳሪ” ስምምነት ብቻ የተደረገ እንደ ነበረ ገልጸዋል።

የአፍሪካ እና የማዳጋስካር ጳጳሳት ከርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ ጋር ያላቸውን ግንኙነት በድጋሚ እንደሚያረጋግጡ አብራርተዋል። "በተለያዩ መልእክቶቻቸው፣ በአፍሪካ ውስጥ የሚገኙ የእግዚአብሔር ቤተ ክርስቲያን ጳጳሳት ጉባሄዎች ከጴጥሮስ መንበር ምትክ ጋር ያላቸውን የማይናወጥ ቁርኝት ፣ ከእርሳቸው ጋር ያላቸውን ግንኙነት እና ለወንጌል ያላቸውን ታማኝነት በማረጋገጥ” ይጀምራሉ።

ነገር ግን ብፁዕ ካርዲናል አምቦንጎ፣ የተመሳሳይ ጾታ ጥንዶች መባረክ አሳፋሪ የሆኑ ነገሮችን እንደሚያመጣ ያምናሉ፣  ምንም እንኳን ከሥርዓተ አምልኮ ማዕቀፎች ውጭ ቢደረጉም።

"የአፍሪካ እና የማዳጋስካር ጳጳሳት ጉባሄዎች - እያንዳንዱ ጳጳስ በሀገረ ስብከታቸው ነጻ ሆነው - ለተመሳሳይ ጾታ ጥንዶች ቡራኬ መሰጠት እንደ ሌለበት ያምናሉ” ያሉት ብፁዕ ካርዲናል አምቦንጎ፣ ድርጊቱ ግራ መጋባትና ቅሌትን ሊያስከትል ይችላል ብለዋል።

ካርዲናል አምቦንጎ ለካህናቱ፣ ለገዳማዊያን ማህበረሰቦች እና ለሁሉም አማኞች ሲናገሩ “Fiducia supplicans” (የእምነት ተማጽኖ) “ቤተክርስቲያኗ ስለ ክርስቲያናዊ ጋብቻ እና ስለ ጾታዊ ግንኙነት የምትሰጠው ትምህርት አሁንም አልተለወጠም” በማለት በግልጽ አጽንዖት ሰጥተው ተናግረዋል።

"በዚህም ምክንያት እኛ የአፍሪካ ጳጳሳት አፍሪካ የግብረ ሰዶማውያን ማኅበራትን ወይም የተመሳሳይ ጾታ ጥንዶችን መባረክ ተገቢ ነው ብለን አናምንም፣ ምክንያቱም በእኛ ሁኔታ ይህ ግራ መጋባትን ስለሚፈጥር እና ከአፍሪካ ማህበረሰቦች ባህላዊ ስነ-ምግባር ጋር በቀጥታ የሚጋጭ ነው” በማለት መግለጫው አክሎ ገልጿል።   “Fiducia supplicans” (የእምነት ተማጽኖ) ሰነድ ቋንቋ ለተራ ሰዎች የሚገባ ቋንቋ ሳይሆን እጅግ በጣም ረቂቅ እና ውስብስብ ነው፥ ለመረዳት የምያስቸግር ጭምር ነው። በተጨማሪም ተመሳሳይ ፆታ ያላቸው በተረጋጋ ኅብረት ውስጥ የሚኖሩ ሰዎች የራሳቸውን አቋም ሕጋዊነት እንደማይቀበሉ ለማሳመን አሁንም በጣም ከባድ ነው” ሲል መግለጫው አክሎ ገልጿል።

በተመሳሳይ ጊዜ ቤተክርስቲያን በአፍሪካ “ለቀጣይ የሐዋርያዊ እንክብካቤ እርዳታ ለሁሉም አባሎቿ” ለመስጠት ያላትን ቁርጠኝነት ያረጋግጣል መግለጫው።

ካርዲናል አምቦንጎ ቀሳውስቱ “በተለይ መደበኛ ባልሆነ ሁኔታ ውስጥ ያሉ ጥንዶችን ማግለል ሳይሆን ተቀብሎ ተገቢውን የሐዋርያዊ እንክብካቤ አገልግሎት እንዲሰጡ ይበረታታሉ” ብለዋል።

“የአፍሪካ ጳጳሳት ጉባኤዎች የግብረ ሰዶማዊነት ዝንባሌ ያላቸው ሰዎች በአክብሮትና ሰብዓዊ መብታቸው ተጠብቆ ሊኖሩ እንደሚገባ አጽንኦት ሰጥተው ሲናገሩ፣ ተመሳሳይ ጾታ ያላቸው ሰዎች ማኅበር የእግዚአብሔርን ፈቃድ የሚጻረር በመሆኑ የቤተ ክርስቲያንን ቡራኬ መቀበል እንደማይቻል በማሳሰብ” አስፈላጊው እና ተገቢ የሆነ ሐዋርያዊ እንክብካቤ ሊደረግላቸው ይገባል ብለዋል ካርዲናል ።

ቤተ ክርስቲያን የግብረ ሰዶም ድርጊቶች “ከተፈጥሮ ሕግ ጋር የሚቃረኑ” እንደሆኑ ያለማቋረጥ ስታስተምር ኖራለች ያለው መግለጫው "አንዳንድ አገሮች የነዚህን ቡራኬዎች ዕድል የሚሰጥ ነገር ግን የማይጭንባቸው ለአዋጁ ጥልቅ ጊዜ ተጨማሪ ጊዜ ማግኘትን ይመርጣሉ" ብሏል። "በማንኛውም ሁኔታ፣ መደበኛ ባልሆነ ሁኔታ ውስጥ ላሉ ጥንዶች ከሚሰጡት ቡራኬዎች በተጨማሪ በዕለት ተዕለት የሐዋርያዊ አገልግሎት እንክብካቤ ውስጥ ድንገተኛ ቡራኬዎች ከማግኘታችን በተጨማሪ የዚህን ሰነድ አጠቃላይ ጭብጥ ያለውን ጠቀሜታ ማሰላሰላችንን እንቀጥላለን" ሲል መግለጫው አክሎ ገልጿል።

በማጠቃለያው ብፁዕ ካርዲናል አምቦንጎ የክርስቲያን ማህበረሰቦች “እራሳቸው እንዳይናወጡ” አሳስበዋል።

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራችስኮስ “በአፍሪካ ውስጥ የሚደረገውን ማንኛውንም ዓይነት የባህል ቅኝ ግዛት አጥብቀው የሚቃወሙ፣ የአፍሪካን ሕዝብ በሙሉ ልባቸው ይባርካሉ እናም እንደ ሁልጊዜው የክርስቲያናዊ እሴቶችን ለመጠበቅ ታማኝ ሆነው እንዲቀጥሉ ስያበረታቱ ቆይተዋል” ብለዋል።

12 January 2024, 16:19