ፈልግ

የነሐሴ 14/2015 ዓ.ም የ19ኛው እለተ ሰንበት ንባባት እና የቅዱስ ወንጌል አስተንትኖ

ቅዱስ ወንጌል ማዕበል ውስጥ በምንገባበት ወቅት በእግዚአብሔር እንድንታመን የመክረናል!

የእለቱ ንባባት

1.      1ነግሥት 19፡9.11-13

2.     መዝሙር 84

3.     ሮም 9፡1-5

4.    ማቴዎስ 14፡22-33

የእለቱ ቅዱስ ወንጌል

ኢየሱስ በባሕር ላይ በእግሩ ሄደ

ወዲያውኑ ደቀ መዛሙርቱ በጀልባ ተሳፍረው ወደ ማዶ እንዲቀድሙት አዘዛቸውና እርሱ ሕዝቡን ለማሰናበት ወደ ኋላ ቀረት አለ። ሕዝቡን ካሰናበተ በኋላም ለመጸለይ ብቻውን ወደ ተራራ ወጣ፤ በጨለመም ጊዜ ብቻውን በዚያው ነበር፤ በዚያ ጊዜ ጀልባዋ ባሕሩን ዘልቃ እየተጓዘች ሳለች ነፋስ ተነሥቶ በማዕበል ትንገላታ ጀመር።

ከሌሊቱ በአራተኛው ክፍል ኢየሱስ በባሕሩ ላይ እየተራመደ ደቀ መዛሙርቱ ወዳሉበት መጣ። ደቀ መዛሙርቱም በባሕሩ ላይ እየተራመደ ሲመጣ ባዩት ጊዜ ፈሩ፤ እነርሱም፣ “ምትሀት ነው!” በማለት በፍርሀት ጮኹ። ኢየሱስም ወዲያውኑ፣ “አይዟችሁ፤ እኔ ነኝ አትፍሩ” አላቸው።

ጴጥሮስም፣ “ጌታ ሆይ፤ አንተ ከሆንህስ፣ በውሃው ላይ እየተራመድሁ ወደ አንተ እንድመጣ እዘዘኝ” አለው።

እርሱም፣ “ና” አለው። ጴጥሮስም፣ ከጀልባው ወርዶ በውሃው ላይ እየተራመደ ወደ ኢየሱስ አመራ። ነገር ግን የነፋሱን ኀይል ባየ ጊዜ ፈራ፤ መስጠምም ሲጀምር፣ “ጌታ ሆይ፤ አድነኝ!” ብሎ ጮኸ።

ኢየሱስም ወዲያውኑ እጁን ዘርግቶ ያዘውና፣ “አንተ እምነት የጐደለህ፤ ለምን ተጠራጠርህ?” አለው። ኢየሱስና ጴጥሮስ ጀልባው ላይ እንደ ወጡ ነፋሱ ጸጥ አለ። 33ከዚያም በጀልባው ውስጥ የነበሩት፣ “በእውነት አንተ የእግዚአብሔር ልጅ ነህ” ብለው ሰገዱለት።

የእለቱ ቅዱስ ወንጌል አስተንትኖ

የተወደዳችሁ ወንድሞች እና እህቶች እንደምን አረፈዳችሁ!

የዛሬው ቅዱስ የወንጌል ምንባብ (ማቴ. 14፡22-33) ኢየሱስ በማዕበል በሚናወጠው ሐይቅ ላይ ስለመራመዱ ይናገራል። ባለፈው እሁድ እንዳየነው ሕዝቡን በአምስት ዳቦና በሁለት ዓሣ ከመገባቸው በኋላ - ኢየሱስ ደቀመዛሙርቱን ወደ ጀልባው እንዲገቡ እና ወደ ሌላኛው የባህር ዳርቻ እንዲጓዙ አዘዘ። ሕዝቡን ካሰናበተ በኋላ ከዚያም ለመጸለይ ብቻውን ወደ ኮረብታማ ስፍራ ወጣ። ከአብ ጋር ያለውን ሕብረት ያጠናክራል።

በሌሊት ሐይቁ በሚሻገሩበት ጊዜ የደቀ መዛሙርቱ ጀልባ በድንገት በከባድ ዐውሎ ነፋስ መናወጥ ይጀምራል። በእዚያን ወቅት በድንገት አንድ ሰው በውኃው ላይ እየተራመደ ወደ እነሱ ሲመጣ አዩ። እነርሱ ያዩት ነገር ምትሃት መስሎዋቸው በጣም ደንግጠው ስለነበረ በፍርሃት ጮኹ። ኢየሱስ “አይዞአችሁ እኔ ነኝ አትፍሩ” የሚል ማረጋገጫ ሰጣቸው። ጴጥሮስም “ጌታ ሆይ ፣ አንተ ከሆንክ በውኃው ላይ እየተራመድኩኝ ወደ አንተ እንድመጣ እዘዘኝ” ሲል መለሰለት። ኢየሱስም “ና” አለው። ጴጥሮስ ከጀልባው ወርዶ ጥቂት እርምጃዎችን በውሃ ላይ መራመድ በጀመረበት ወቅት ከዚያም በወቅቱ የተነሳው ነፋስ እና ማዕበል ከፍተኛ ስለነበረ እጅግ በጣም ስለፈራ መስመጥ ይጀምራል። “ጌታ ሆይ አድነኝ” እያለ ጮኸ ከእዚያም በኋላ ኢየሱስ እጁን ዘርግቶ ያዘውና “አንተ እምነት የጎደለህ ለምን ተጠራጠርክ?” ይለዋል። 

ይህ ታሪክ በሁሉም የሕይወት ዘመናችን በተለይም በፈተና እና በችግር ጊዜ እራሳችንን በታማኝነት ወደ እግዚአብሔር እንድናቀርብ የቀረበልን ጥሪ ነው። ጠንካራ የጥርጣሬ እና የፍርሀት ስሜት ሲኖረን እና እየሰመጥን ያለን ሲመስለን እንደ ጴጥሮስ “ጌታ ሆይ አድነኝ” ብለን ለመጮህ ማፈር የለብንም። እሱ የሚያምር ጸሎት ነው! እናም ወዲያው እጁን ዘርግቶ የጴጥሮስን እጅ የያዘው የኢየሱስ የእጅ ምልክት ለረጅም ጊዜ በጥልቀት መታሰብ አለበት። እርሱ ፈጽሞ የማይተወን የአብ እጅ ነው ፡፡ ሁልጊዜ ጥሩ እና ጥሩ የሆነውን ለእኛ የሚፈልገውን የአብ ጠንካራ እና ታማኝ አባት የሚወክ እጅ ነው። ስለ ነብዩ ኤልያስ የተነገረው በዛሬው በመጀመሪያው ምንባብ (1ኛ መጽሐፈ ነገሥት 19:11-13) ላይ የተጠቀሰው ታሪክ እግዚአብሔር አውሎ ነፋስ ፣ እሳት ፣ የመሬት መንቀጥቀጥ የሚወክለው አምላክ ሳይሆን በዝምታ ለእኛ ጥያቄዎች መልስ የሚሰጠ አምላክ እንደ ሆነ ያሳያል። እግዚአብሄር የማያስገድድ እና ለመስማት የሚጠይቅ የብርሃን እስትንፋስ ነው። እምነት ማለት በማዕበል ውስጥ በምንሆንበት ወቅት ልባችንን ወደ እግዚአብሔር ወደ እርሱ ፍቅር፣ ወደ አባቱ ወደ ርኅራኄው መመለስ ማለት ነው። ኢየሱስ ይህንን ለጴጥሮስና ለደቀመዛሙርቱ እንዲሁም ለእኛም ዛሬ ለማስተማር ፈለገ። እምነታችን ጎደሎ እንደ ሆነና መንገዳችንም በተጋላጭ ኃይሎች ሊደናቀፍ እንደሚችል በሚገባ ያውቃል። እርሱ ግን ወደ ደኅንነቱ እንድናመራ ለማድረግ አስቦ ወደ ሞት የገባው ጌታ ነው። እሱን መፈለግ ከመጀመራችን በፊት እንኳን እርሱ ከአጠገባችን ይገኛል። ከውድቀታችን በኋላ እኛን በማስነሳት በእምነት እንድናድግ ይረዳናል።

ማዕበሉ በተናወጠበት ወቅት የነበረችው ጀልባ በየትኛውም ዘመን የምትገኘው እና እርሷን በመቃረን የሚነፍሱ ንፋሶችን የምትጋፈጠው፣ አንዳንድ ጊዜ በጣም ከባድ ፈተናዎች የሚያጋጥማት የቤተክርስቲያን ምስል ነው።  በዚህ ዓይነት ሁኔታዎች ውስጥ ቤተክርስቲያን በምትገባበት ወቅት  እግዚአብሔር ትቶኛል ብላ የማሰብ ፈተና ሊገጥማት ይችል ይሆናል። ነገር ግን በተጨባጭ በእነዚያ ጊዜያት የእምነት ፣ የፍቅር እና የተስፋ ምስክርነት እጅግ የሚበራ ሆኖ በእነዚያ ጊዜያት ውስጥ ይታያል። አዳዲስ ክርስትያኖች በዓለም ሁሉ ላይ እንዲፈልቁ፣ ሰላም እና እርቅ በማውረድ ሂደት ውስጥ በከፍተኛ ሁኔታ ለሚሳተፉ ሰዎች ስማዕት እስከመሆን ድረስ የሚያደርስ ጸጋ በቤተክርስቲያኗ ውስጥ እንዲከናወን የሚያደርገውን የትንሳኤውን ክርስቶስ የመገናኛ መስመር ነው።

ጨለማ እና የሕይወት ማዕበል በሚያጋጥመን ወቅት በእግዚአብሔር ላይ ያለን እምነት ወደ ቀውስ ውስጥ ሲገባ በእምነት እና በተስፋ ፍቅር እንድንጸና ትረዳን ዘንድ የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያምን  አማላጅነት እንማጸናለን።

ምንጭ፡ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ በነሐሴ 03/2012 ዓ.ም በቫቲካን በሚገኘው በቅዱስ ጴጥሮስ አደባባይ ካደረጉት አስተንትኖ የተወሰደ።

አቅራቢ አባ መብራቱ ኃ/ጊዮርጊስ ቫቲካን

 

19 August 2023, 12:12