የ53ኛው ዓለም አቀፍ የቅዱስ ቁርባን ምክር ቤት ስብሰባ አርማ ይፋ ሆነ
አዘጋጅ ዘላለም ኃይሉ ፥ አዲስ አበባ
ሰኞ እለት ፥ የዓለም አቀፉ የቅዱስ ቁርባን ምክር ቤት ጳጳሳዊ ኮሚቴ በኢኳዶር ሃገር - በኪቶ ከተማ ፥ ከጳጉሜ 3, 2016 ዓ.ም. - መስከረም 5, 2017 ዓ.ም. ድረስ የሚካሄደውን የ53ኛው ዓለም አቀፍ የቅዱስ ቁርባን ምክር ቤት ስብሰባ አርማ ይፋ አድርጓል።
የጉባኤው ዓርማ ጭብጥ “ፋተርኒዳድ ፓራሳርኤል ሙንዶ” (ኅብረት ዓለምን ለማዳን) የሚል ሲሆን ፥ በቅዱስ ማቴዎስ ወንጌል ላይ “ሁላችሁም ወንድማማች ናችሁ” ሲል ኢየሱስ በተናገረው ቃል ተንተርሶ እንዲሁም አሁኑ እየተካሄደ ያለውን የቤተክርስቲያኒቷ የሲኖዶስ ሂደትንም የሚያስታውስ ሆኖ ፥ በወንድማማችነት በማሳተፍ ፣ የጋራ እንደሆነ ሃብት እና በጥልቅ መስተንግዶም እንዲካሄድም ጥሪ ቀርቧል። የጉባኤው ዝግጅት መደምደሚያ “ስታቲዮ ኦርቢስ” (ለእያንዳንዱ ዓለም አቀፋዊ ጉባኤ የሚደረግ የጳጳሳት መዝጊያ ቅዳሴ) በማክበር ይጠናቀቃል ተብሏል።
በዚህ ወር መጀመሪያ ላይ የኮንግረሱ ዓርማ እና ኦፊሴላዊ መዝሙር በኢኳዶር ኤጲስ ቆጶሳት ጉባኤ ዋና መሥሪያ ቤት ቀርቧል።
ሰኞ ዕለት የተለቀቀው መግለጫ ስለ ዓርማው እያንዳንዱን አካል እና ትርጉሙን አብራርቷል።
ዓርማው
በመጀመሪያ ደረጃ ‘የክርስቶስን መስቀል’ ይገልፃል ፥ ወደ እያንዳንዳችን ዓለማዊ ሥጋ የሚገባው በኃጢአት የተከፈቱትን ቁስሎች ለመፈወስ ነው ፥ እነዚህም ሃጥያቶች ለእግዚአብሔር አለመታዘዝ ፣ ባልንጀራን መበደልና ሥነ ፍጥረትን በመበዝበዝ እና የመሳሰሉት ናቸው። ይህ አዲስ የታሪክ ዘውግ ነው። በዚያም የሰው ልጅ የተጫነበትን ሃጢያት የሚያድነው በእግዚአብሔር በግ አማካይነት ፥ እግዚአብሔር ፍቅሩን በልጁ በኢየሱስ ክርስቶስ አማካይነት በመስቀል ላይ በፈሰሰው ደሙ ፣ ከተከፈተው ጎኑ በሚፈሰው የውሃና የደም ምልክቶች ውስጥ ነው። የተሰቀለው ኢየሱስ ከሙታን የተነሣ ነው። የተዘረጉት እጆቹ ፥ ከአብ ጋር እንደታረቁ ወንድሞች ሁሉንም አቅፏል።
ሌላው በመስቀል ላይ የተከፈተው የክርስቶስ ልብ ምሳሌ “ሁሉንም ነገር አዲስ የሚያደርገው የፍቅር ምንጭ” ን ይወክላል።
“የእሱ ቁስሎች ከአሁን በኋላ ሞትን ወደ እኛ አያመጡም ፥ ነገር ግን የህይወት እና የእርቅ ምንጭ ናቸው። ስለዚህ በትንሳኤው ሃይል የተነሳው የክርስቶስ የተከፈቱት ቁስሎች በአሁኗ ሰዓት ፥ ከጥላቻ ፣ ከክፋት ፣ ከአመፃ እና ከሞት የሚፈዉሱ አዲስ የፍቅር ቁስሎች ናቸው ቁስሎቹ” ይላል መግለጫው
የሚታየው ህብስት የሚያመለክተው ቅዱስ ቁርባንን ሲሆን እርሱም የሁሉም ክርስቲያን ሕይወት ሁሉ ጫፍ እና ምንጭ ነው።
“የቅዱስ ቁርባን ብርሃን” ይላል መግለጫው “ለሰው ልጅ ታሪክ አዲስ መመሪያን ይሰጣል ፥ ምክንያቱም እግዚአብሔር ህዝቡን ከምሥራቅ እስከ ምዕራብ በመሰብሰብ ፥ ህዝቡን የህይወት ምንጭ በሆነው ቃሉ
እና ከሰማይ የወረደው የህይወት መና ዙሪያ ህዝቡን ይሰበስባል። የቁርባን በዓል እንደ አንድ አባት ልጆች ወደ አንድ ገበታ ይሰበስበናል።
ዓርማው ጉባኤዉን የሚያስተናግደውን ከተማንም አጉልቶ ያሳያል።
የዓርማው ማብራሪያ ማስታወሻ በመቀጠል "በዓለም መሀል ላይ ያለች ኪቶ ከተማ ፥ በዜሮ ኬክሮስ ላይ የምትገኝ ከተማ ፥ ድንኳኗን ታሰፋለች፥ ታላቅ የቅዱስ ቁርባን ከተማ እንድትሆን ሁላችንም በዚህ ታላቅ ህልም ውስጥ ፍጹም በሆነው በክርስቶስ ፍቅር የተዋጁ እና የተፈወሱ ወንድማማችነት እንድንሳተፍ ተጋብዘናል ፥ ይህም የክርስቶስ ፍቅር ይሄንን እንድንረዳ በዚህ ታሪካዊ ጊዜ የሚረዳን ፥ ሁሌም የሚኖር ፍቅር ነው። ‘እናንተ ሁላችሁ ወንድማማቾች ናችሁ’ (ማቴ 23፡8) የሚለውን እንድንገነዘብ የሚረዳን ፍቅር ነው።