በህንድ ክርስቲያኖች ላይ የሚደረገው ትንኮሳ እንደቀጠለ ነው።
ባለፈው እሁድ ዕለት 10 ፓስተሮችን ጨምሮ ወደ 50 የሚጠጉ ክርስቲያኖች በቻትስጋርህ ግዛት በሆነችው በህንድ መንደር ውስጥ ሀይማኖታዊ ለውጥ ማድረጋቸውን ተከትሎ በአንድ አክራሪ የሂንዱ ፓርቲ ጥቃት ደርሶባቸዋል።
የአከባቢው ማህበረሰብ የሆኑት እነዚህ ክርስቲያኖች በአንድ የግል ቤት ለመጸለይ ተሰብስበው የነበረ ሲሆን ፥ የሂንዱ ብሔርተኛ ድርጅት አባል የሆነው ባጅራንግ ዳል ከሌሎች ታጣቂዎች ጋር በመሆን ቤቱን ከበው ወደ ውስጥ በመዝለቅ ክርስቲያኖቹ እንዳያመልኩ አስቁመዋቸዋል።
ክርስትያኖቹም ለደህንነታቸው በመፍራት እቤታቸው ውስጥ ዘግተው ፖሊስ ጠርተው እንደወጡ ነው የተዘገበው።
ነገር ግን ፖሊሶች ሲደርሱ የቤቱን ባለቤት ጨምሮ ፓስተሮቹን እና ሌሎች ጥቂት ክርስቲያኖችን ‘ሠላም በማደፍረስ’ በሚል ሰበብ ማሰራቸው ተዘግቧል ፤ ምንም እንኳን በዚያው ቀን ማምሻውን ከእስር ቢፈቱም። የፀሎት ስነስርዓቱ ተሳታፊ የነበረው አንኩሽ ባራዪከር ፥ ፓስተሮች በፖሊሶች ተደብድበዋል በማለት ክሱን ሲያቀርብ ፥ እነዚህም ወንጌላዊያን በአካባቢው ሆስፒታል እየታከሙ እንደሆነም ተናግሯል።
የአካባቢው የጥርስ ሐኪም ዶ/ር የሆኑት የቤቱ ባለቤት ቪናይ ሳሁ በበኩላቸው ማይክሮፎን እና ድምጽ ማጉያ አለመጠቀማቸው እና የድምፅ ብክለት እንዳላደረጉ ተናግረው ፥ ‘እነዚህ ጥቃቶች የተፈጸሙበትን ምክንያት ልንረዳ አልቻልንም’ ሲሉም አክለዋል።
ባራዬካር ከዩ ሲ ኤ ኒውስ ጋር ባደረገው ቃለ ምልልስ ፥ ‘የዶ/ር ሳሁ የሂንዱ ጎረቤቶች ከዚህ ቀደም ሃይማኖታዊ ስብሰባዎችን ሲቃወሙ እና እነሱን ለማቆም የሂንዱ አክራሪዎችን እርዳታ የጠየቁ ይመስላል’ በማለትም አስተያየቱን አክሏል።
ድርጊቱ በተፈፀመበት የአምለሽዋር መንደርን የፀጥታ ሁኔታ የሚከታተለው የፖሊስ ሱፐር ኢንቴንደንት ጥቃቱን "ይህ ትንሽ ክስተት ነው" በማለት ችግሩ ቀደም ብሎ መቀረፉን ተናግሯል።
ይህ ድርጊት ለመጀመሪያ ጊዜ አይደለም
ዶ/ር ሳሁ ፥ ባጅራንግ ዳል በ2021 ተመሳሳይ ተቃውሞ እንዳዘጋጀ ለሃገር ውስጥ መገናኛ ብዙሃን ተናግሯል። ክርስቲያኖቹ የጸሎት ስብሰባቸውን የሚቀጥሉ ከሆነ ጥቃት እንደሚደርስባቸውም የማስፈራሪያ ዛቻ ደርሶባቸዋል ብለዋል።
እ.አ.አ. በ 2023 መጀመሪያ ላይ በህንድ ቻትስጋርህ ግዛት ውስጥ በናራያንፑር እና ኮንዳጎን ወረዳዎች ውስጥ ከአንድ ሺህ የሚበልጡ ክርስቲያኖች በሚደርስባቸው በዓመፅ ዛቻ ምክንያት ቀያቸውን ለቀው ለመሰደድ መገደዳቸውም ተነግሯል።
እንዲያውም ገዥው የፖለቲካ ፓርቲ የሆነው ብሃራቲያ ጃናታ ፥ በመጋቢት 1998 ሥልጣኑን ከተረከበ በኋላ የፀረ-ክርስቲያን ጥቃት በከፍተኛ ደረጃ መጨመሩም ተገልጿል።
የሕንድ የሃገር ውስጥ ደኅንነት እና የብሔራዊ አናሳ ብሄሮች ኮሚሽን እንደገለፀው ፥ በየዓመቱ ከመቶ በላይ ሃይማኖትን ሰበብ ያደረጉ ጥቃቶች በክርስቲያኖች ላይ እንደተፈፀሙ ጠቁሞ ፥ ምንም እንኳን አንዳንድ የጥቃት ድርጊቶች ያልተመዘገቡ በመሆናቸው እንጂ እነዚህ ቁጥሮች ከዚህ እንደሚበልጡ ተመላክቷል።
“ማጋነን”
የባንጋሎር ሊቀ ጳጳስ የሆኑት ዶ/ር ፒተር ማቻዶ በመጋቢት 2022 በህንድ አንዳንድ አካባቢዎች በክርስቲያኖች ላይ የሚፈፀመውን ‘አስከፊ የጥቃት ክስተት’ እና ‘በክርስቲያኖች ላይ ያነጣጠረ የጥላቻ ንግግር’ እንዲቆም አቤቱታ አቅርበዋል።
ሊቀ ጳጳስ ማቻዶ አክለውም ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በክርስቲያኖች ላይ የሚፈጸሙ ጥቃቶች ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ እየጨመረ በመምጣቱ በሕንድ ያሉ ክርስቲያኖች በአሁኑ ጊዜ የሚኖሩት ‘በፍርሃት’ ውስጥ ነው ብለዋል።
ይህ በእንዲህ እያለ የሕንድ ጠቅላይ አቃቤ ህግ የሆኑት ቱሻር መህታ ፥ በሚያዚያ 14, 2023 እንደተናገሩት ፥ የሊቀጳጳሱን ክስ በመተቸት ‘ማሰሮው እንዲፈላ’ ብቻ ብለው በገለጹት አገላለፅ “ሊቀ ጳጳሱ ጥቃቶቹን እያጋነኑት ነው” ሲሉ የጳጳሱን ክስ እና የያገባኛል ጥያቄዎቹን “ውሸት” ሲሉ ውድቅ አድርገዋል።
ለተጠናከረው ዘገባ
ዘላለም ኃይሉ - አዲስ አበባ
ኢትዮጵያ