ሴቶች በህብረተሰቡ ውስጥ ያላቸውን ተሳትፎ እና ሚና ማበረታታት እንደሚያስፈልግ ተገለጸ።
ዘላለም ኃይሉ ፥ አዲስ አበባ - ኢትዮጵያ
ሲ/ር ኔሊ ሴቶች በማህበረሰብ ውስጥ ያላቸውን ተሳትፎ የሚያበረታቱ ትርጉም ያሏቸው ለውጦችን ለማምጣት እንደሚሰሩ ተናግረዋል።
"በቤተሰብ ፣ እምነትን በማስተማር ፣ በሃዋሪያዊ ሥራ እና በትምህርት ቤት ሥራ ብቻ ተገድበው ያሉትን ሴቶች በማህበራዊ ፣ ባህላዊ እና ኢኮኖሚያዊ መዋቅሮች ውስጥ ያሏቸዉን ድርሻ እና አስተዋፅኦ እንዲያጎለብቱ አበረታታለሁ ፥ እናንተ ሴቶች የእግዚአብሔርን የርኅራኄ ፊት እና ምህረቱን ፥ ይህም ቦታን ከመያዝ ይልቅ ጊዜን መስጠትን ፣ ከማግለል ይልቅ መቀበልን እንዴት እንደሚገለፅ ታውቃላችሁና።” (ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቺስኮስ)
የእህቶች ጥሪ በጉባኤ ውስጥ
ሲ/ር ኔሊ ላምሲስ እንደሚናገሩት የዶሚኒካን የብስራት እህትማማቾች ማህበር ፥ በሳን ካርሎስ ሲቲ ፣ ፓንጋሲናን እና ፊሊፒንስ ውስጥ የሚገኘው ጉባኤያቸው የገዳማዊያኑን ጥሪ በንቃት እያበረታታ ነው ብለዋል።
“የእኛ ሥራ ወጣቶችን ማደራጀት እና ትምህርት ላይ የሚያተኩር ነው ፥ ይህንንም የምናከናውነው በጸሎት በመታገዝ ሲሆን ፥ ልጆች ፣ ወጣቶች እና ወላጆች ላይ በመተግበር እንጠብቀዋለን” ሲሉ ለቫቲካን ዜና ተናግረዋል።
የነበረው የሴቶች የትምህርት እድል እጦት የዶሚኒካን እህትማማቾች ማህበር መስራች ጉባኤውን እንዲመሰርቱ አነሳስቷቸዋል ነው የተባለው።
''መስራቻችን ማህበረ ቅዱሳንን ካቋቋመበት ዋና ምክንያቶች አንዱ የሴቶችን አቅም ለማጎልበት እንደሆነ እና በዚያን ጊዜ ሴቶች የትምህርት ዕድል አያገኙም ነበር” በማለት አስታውሰዋል ሲስተሯ።
ገዳማዊያኑ ከማስተማር ጎን ለጎን ፥ ሴቶችን ፣ ህፃናትን እና እናቶችን ይደግፋሉ።
"አባ ኮል ሴቶቹን የገነቡት ሌሎች ሴቶችን እና ህጻናትን ለመርዳት እንዲችሉ አድርገው ነው ያቋቋሙት ፥ እኔ በተመደብኩበት ቦታ ለእናቶች ብቻ የተመደቡ የክርስቲያን አደረጃጀት አሏቸው" ሲሉ ገልፀዋል።
ለ23 ዓመታት የካቶሊክ ቤተክርስቲያን አገልጋይ ሆነው የቆዩት ሲ/ር ኔሊ ፥ ይህንን ለማድረግ እና በዚህም ጥሪ ለመቀጠል እንዲሁም ህይወታቸውን በሙሉ ለዚህ ዓላማ ለመስጠት ያበረታታኝ ትልቁ ነገር ‘ጌታን ማገልገል ሙሉ ሰው እንደሚያደርግ’ በማወቄ ነው ብለዋል። ጨዋነት እና ትህትና በእምነት ውስጥ
በአገልግሎታቸው ሁሉ በእምነት ውስጥ የጨዋነት እና ትህትናን አስፈላጊነት ተረድተዋል።
“ሃይማኖታዊ ሕይወት መግባቴ ልቤን ለስላሳ አድርጎታል ፣ ግትር ባህሪዬንም ቀይሮ ትሁት አድርጎኛል። ይህም በእምነታችን ውስጥ በጣም አስፈላጊው ነገር ነው” ብለዋል ሲስተር ኔሊ።
በተጨማሪም ሌሎችን ማዳመጥ የማስተዋል ችሎታችንን እንደሚያጎለብት አምናለሁ ብለው በማከልም ፥ “ገርነት እና ትህትና የበለጠ እንድንሰማ ይረዳናል ምክንያቱም ስናዳምጥ አእምሯችን ይበልጥ ግልጽ ይሆናል ፥ አእምሯችን ንፁህ በሚሆንበት ጊዜ በድርጊታችን የበለጠ ቆራጥ እና እርግጠኞች እንሆናለን” ብለዋል።
ሴቶች ደካማ ጎናቸውን ለማሳየት መፍራት እንደሌለባቸው እና ሁልጊዜ ከጌታ ጋር በመሆን እንዲቀጥሉ አበረታተዋል።
“ደካማ ጎን ካላችሁም አትፍሩ ፥ ከእግዚአብሔር ጋር ለመገናኘትም አትፍሩ” ሲሉ ሲ/ር ኔሊ መክረዋል።
በገዳማዊያኑ የጥሪ ተግባራት ወቅት በዋናነት ሴቶች ከሆኑ ተሳታፊዎች ጋር ጊዜ ወስደው እነዚህን ባህሪያት አስተምረዋቸዋል።
“እኔ አብዛኝውን ጊዜ ከወጣቶች ፣ ከካቴኪስቶች እና ከማህበራት ጋር ነው የምውለው ፥ ይህም ስብስብስ ባብዛኛው ሴቶችን ያቀፈ ነው። የእኔ ትልቁ ትኩረቴ በወንጌል ላይ ነው ፥ ሴቶችን ማብቃት ደግሞ ወንጌልን መስበክ ነው" በማለት አብራርተዋል።
በማህበረሰብ እና በቤተሰብ ውስጥ የሴቶች ሚና እና ተሳትፎ
እንደ ገዳማዊያን ሴቶች ፥ ሲ/ር ኔሊ እና ሌሎች የዶሚኒካን እህቶች የሴቶች ተሳትፎ በማህበረሰቡ ውስጥ ያለውን ጠቀሜታ ከፍ አድርገው ይመለከቱታል።
እሳቸውም “ሴቶች በህብረተሰቡ ውስጥ ያላቸውን ሚና ማጉላት አስፈላጊ ነው” በማለት አፅንዖት ሰጥተዋል።
በቤተሰብ ውስጥ የሴቶች ሚና ለውጥ እንደሚያመጣም ያምናሉ።
“በሥነ ልቦና እና በአካል ፥ ሴቶች እና ወንዶች የተለያዩ ናቸው ይህም በቤተሰ ብ ውስጥ የተለያዩ ሚናዎችን እንዲጫወቱ ያደርጋቸዋል ፤ ሴቶች በቤተሰብ ውስጥ እንደ እናት ፣ እህት ፣ እንዲሁም ሴት ሆነው ሚናቸውን ከተጫወቱ ፥ እኛም በህብረተሰቡ ውስጥ ውጤታማ ሚና እንጫወታለን። በተጨማሪም ሴቶች በህብረተሰቡ ውስጥ ላሉ ያልተሰሙ እና የድሆች ድምጽ ሆነው ያገለግላሉ” ሲሉም አክለዋል።
ሴቶችን ማብቃት
ሲ/ር ኔሊ የሴቶችን እምነት እና እውቀት እንዲጎለብት ጥረት ያደርጋሉ ፥ ይህም ሴቶቹን ለማበረታታት ይረዳል።
‘ሴቶችን ማብቃት በኛ የተልዕኮ ሥራ ዉስጥ አስፋፍቻለሁ ፥ የእኛ ተልዕኮም ልጆችን እና ህፃናትን በትምህርት መድረስ ነው’ በማለት አክለዋል።
ብዙ የሴቶች ቡድኖች በትምህርት ተደራሽነት ውስንነት የተነሳ ፈተናዎች እንደሚገጥሟቸውም በመጠቆም ፥ "የትምህርት እጦት ሴቶች ለራሳቸው ያላቸው ግምት እንዲቀንስ ያደረጋቸው ሲሆን ፥ ይህም በአሁኑ ጊዜ ህብረተሰቡ ለሴቶች ያለውን አመለካከት እንዲቀንስ አድርጎታል ፤ እነሱን በማስተማር በሴቶች ላይ የሚደርሰውን በደል ለመዋጋት ይረዳል እናም በመጨረሻም ያስወግዳል” በማለትም መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።
እንደ አንድ ተልዕኮ ያለው ሰው በቃል እና በተግባር ወጥ የሆነ ህይወትን በመምራት እና ወንጌልን በማስፋፋት ፥ የቤተክርስቲያኗን እና የሴቶችን የማብቃት ጥሪ በቀጣይነት እንደሚያጎለብቱትም ገልጸዋል።
ሲስተር ኔሊ ላምሲስ የሴቶች ሚና በህብረተሰብ ውስጥ በጣም ወሳኝ እንደሆነ እና የካቶሊክ እምነትን በዓለም ላይ በማስፋፋት ረገድ አወንታዊ ለውጦችን እንደሚያመጣ ያላቸውን ጽኑ እምነት በመግለጽ ቃለ መጠይቁን አጠናቀዋል።