እ. አ. አ ከሐምሌ ወር ጀምሮ የሲኖዶሳዊነት ሂደት ትምህርት በአውታረ መረብ እንደሚሰጥ ተነገረ
የዚህ ዝግጅት አቅራቢ ዮሐንስ መኰንን - ቫቲካን
በአውታረ መረብ አማካይነት የሚሰጠው ትምህርቱ አህጉር አቀፍ እና የተለያዩ ባሕሎችን ያካተተ ሲሆን፣ ፕሮጀክቱ ሥነ መለኮትን የተከተል ሲኖዶሳዊ አሠራርን ለብጹዓን ጳጳሳት፣ ለካህናቱ፣ ለገዳማውያን እና ገዳማውያ እንዲሁም ለምእመናን ለማስተማር ታስቦ መረብ በኩል የቀረበ የሲኖዶሳዊ ጉዞ አካል ሆኖ የተነደፈ መሆኑ ታውቋል። ትምህርቶቹ በስፓኒሽ፣ በእንግሊዘኛ፣ በፖርቱጋልኛ፣ በፈረንሳይኛ እና በጣሊያንኛ ቋንቋዎች በነጻ የሚሰጡ ሲሆን ከሁሉም አህጉራት በተውጣጡ የተለያዩ ቋንቋ ተናጋሪ መምህራን የሚሰጡ እና የቤተ ክርስቲያንን ዓለም አቀፋዊነት ተከትለው ባሕላዊ እይታዎችን የሚያስረዱ መሆናቸው ታውቋል። በጎርጎሮሳውያኑ 2021 ተጀምሮ ጥቅምት ወር 2023 ዓ. ም በሚጠናቀቀው 16ኛ የብጹዓን ጳጳሳት ሲኖዶሳዊ ጉዞ ወቅት የቤተ ክርስቲያን ሲኖዶሳዊነትን በሚገልጹ ኅብረት፤ ተሳትፎ እና ተልእኮ በሚሉ ዋና ርዕሦች ላይ በማትኮር ጉዞን በኅብረት ላማካሄድ የተጠሩትን የእግዚአብሔር ሕዝቦች ለመደገፍ ያለመ መሆኑ ታውቋል።
የመጀመሪያ ዙር በሐምሌ ወር ላይ ይጀምራል
በሐምሌ ወር ውስጥ ለሦስት ሳምንታት የሚሰጥ የመጀመሪያ ዙር ትምህርቱ፣ የተለያዩ ትምህርቶችን፣ የስብሰባ ላይ ንግግሮችን፣ ግንዛቤ ማስጨበጫዎችን፣ በቤተ ክርስቲያን የውሳኔ አሰጣጥ ሂደቶች ላይ የልምድ ልውውጦችን ያካተተ መሆኑ ታውቋል። ትምህርቱ በአውታረ መረብ እንዲዘጋጅ የረዱት፣ የላቲን አሜሪካ አገሮች ብጹዓን ጳጳሳት ጉባኤዎች ምክር ቤት (Celam)፣ የአውሮፓ ብጹዓን ጳጳሳት ጉባኤዎች ምክር ቤት (Ccee)፣ የእስያ አገራት ብጹዓን ጳጳሳት ጉባኤዎች ምክር ቤት (Fabc)፣ ዓለም አቀፍ የገዳማት የበላይ አለቆች ኅብረት (Uisg)፣ የገዳማት አለቆች ኅብረት (Usg)፣ የላቲን አሜሪካ የገዳማውያን እና ገዳማውያት ኮንፌዴሬሽን (Ucesm) እና የላቲን አሜሪካ እና ካሪቢያን አገሮች ኢየሱሳዊ አውራጃዎች ጉባኤ (Cpal) መሆናቸው ታውቋል።