ፈልግ

የምእመን ጸሎት በቅዱስ መስቀል ፊት፣ የምእመን ጸሎት በቅዱስ መስቀል ፊት፣  

የመስከረም 11/2012 ዓ.ም ሰንበት ዘፍሬ ቅ. ወንጌል እና የቅዱስ ወንጌል አስተንትኖ፣

የእለቱ ምንባባት

1.     2ቆር 9፡1-15  

2.      ያዕ 5፡1-9             

3.     ማር 4፡24-32

የእለቱ ቅዱስ ወንጌል

በመቀጠልም፣ “ስለምትሰሙት ነገር ጥንቃቄ አድርጉ፤ በምትሰፍሩበት መስፈሪያ ይሰፈርላችኋል፤ እንዲያውም ከዚያ የበለጠ ይጨመርላችኋል። ላለው ይጨመርለታል፤ ከሌለው ላይ ግን፣ ያው ያለው እንኳ ይወሰድበታል” አላቸው።

የአዳጊው ዘር ምሳሌ

ከዚያም፣ እንዲህ አለ፤ “የእግዚአብሔር መንግሥት ይህን ትመስላለች፤ አንድ ሰው መሬት ላይ ዘር ይዘራል። ሰውየው ሌሊት ይተኛል፤ ቀን ይነሣል፤ ነገር ግን እርሱ ሳያውቅ ያ ዘር በቅሎ ያድጋል፤ ምድርም ራስዋ በመጀመሪያ ቡቃያውን፣ ቀጥሎ ዛላውን፣ ከዚያም በዛላው ላይ የጐመራ ፍሬ ታስገኛለች፤ ፍሬው እንደ በሰለም መከር በመድረሱ፣ ሰውየው ወዲያው ማጭዱን አንሥቶ አጨዳ ይጀምራል።”

የሰናፍጭ ቅንጣት ምሳሌ

ደግሞም እንዲህ አለ፤ “የእግዚአብሔርን መንግሥት ከምን ጋር እናነጻጽራታለን? በምንስ ምሳሌ እንገልጻታለን? በምድር ላይ ከሚዘራው ዘር ሁሉ እጅግ ያነሰችውን የሰናፍጭ ቅንጣት ትመስላለች፤ ተዘርታ ካደገች በኋላ ግን፣ በአትክልቱ ቦታ ከሚገኙት ዕፀዋት ሁሉ ትበልጣለች፤ የሰማይ ወፎችም በትላልቅ ቅርንጫፎቿ ጥላ ሥር ያርፋሉ።”

ኢየሱስም ሰዎች መረዳት በሚችሉበት መጠን፣ እነዚህን በመሳሰሉ ብዙ ምሳሌዎች ነገራቸው። ምንም ነገር ያለ ምሳሌ አይነ ግራቸውም ነበር። እርሱና ደቀ መዛሙርቱ ብቻ በሚሆኑበት ጊዜ ግን ሁሉንም ነገር በዝርዝር ያስረዳቸው ነበር።

ኢየሱስ ማዕበሉን ጸጥ አደረገ

ያ ቀን በመሸ ጊዜ፣ “ወደ ማዶ እንሻገር” አላቸው። እነርሱ ሕዝቡን ትተው በጀልባዋ ውስጥ እንዳለ በዚያው ይዘውት ሄዱ፤ ሌሎች ጀልባዎችም አብረውት ነበሩ። በዚህ ጊዜ ኀይለኛ ዐውሎ ነፋስ ተነሣ፤ ማዕበሉም ውሃ እስኪሞላት ድረስ ጀልባዋን ያናውጣት ነበር። ኢየሱስ ግን ትራስ ተንተርሶ ከጀልባዋ በስተ ኋላ በኩል ተኝቶ ነበር። እነርሱም ቀስቅሰውት፣ “መምህር ሆይ፤ ስናልቅ አይገድህምን?” አሉት።

ዛሬ በተነበበልን ቅዱስ ወንጌል ውስጥ (ማርቆስ ወንጌል 4፡26-34) ኢየሱስ ስለእግዚአብሄር መንግሥት እና የእድገቱን ጥንካሬ በተመለከተ ሁለት አጫጭር ምሳሌዎችን በመጠቀም ለሕዝቡ ይናገራል።

በመጀመሪያው ምሳሌ ላይ (ማር. 4፡26-29) የእግዚኣብሔርን መንግሥት ከአንድ ምስጢራዊ በሆነ መልኩ ከምታድግ ዘር ጋር በማነጻጸር አንድ ሰው መሬት ላይ ዘር ይዘራል። ዘሪው ምንም ሳያውቅ ያ ዘር በቅሎ ያድጋል፤  በመጀመሪያ ቡቃያ፣ ቀጥሎ ዛላ፣ ከዚያም በዛላው ላይ የጐመራ ፍሬ ታስገኛለች በማለት ይናገራል። ይህ ምሳሌ የሚያስተላልፍልን መልእክት የሚሆነው ኢየሱስ በስብከቱ እና በተግባሩ አማካይነት ያወጀው እግዚኣብሔርን መግሥት ልክ እንደ ዘር በዓለም ውስጥ በመዘዋወር በራሱ ኃይል እንደ ሚበቅል እና እንደ ሚያድግ፣ በሰውኛ አመለካከት ሊገለጽ በማይችል መልኩ በራሱ እንደ ሚበቅል የሚያመለክት መልእክት ያስተላልፍልናል። በታሪክ ውስጥ የእድገቱ እና የእድገቱ ሂደት በሰው ስራ ላይ ብዙ የማይመረኮዝ፣ ነገር ግን በተቃራኒው በእግዚኣብሔር ኃይል እና መልካምነት ላይ ብቻ የተመረኮዘ እንደ ሆነ፣ በእግዚአብሔር ሕዝብ ውስጥ ክርስቲያናዊ ሕይወትን የሚመራ የመንፈስ ቅዱስ ኃይል መሆኑን ያመለክታል።

አንዳንድ ጊዜ በእዚህ ታሪክ ውስጥ የተጠቀሱት ተግዳሮቶችን እና ተዋናዮች ሰማያዊ አበታችን ለልጆቹ ሁሉ ያለውን የወንድማማችነት፣ የፍትህ እና የሰላም እቅድ በተቃራኒ አቅጣጫ በመሄድ ይመስላል። ነገር ግን እኛ በእነዚህን ጊዜያት ለመፈተን፣ ተስፋ ማድረግን እና በመጠባበቅ ላይ እንድንቆይ ተጠርተናል። በእርግጥ ልክ እንደ ትላንቱ ዛሬም የእግዚአብሔር መንግሥት በዓለም ውስጥ ምስጢራዊ በሆነ መልኩ እያደገች በሚያስደንቅ መንገድ ትናንሽ በምትባል ዘር ውስጥ በተደበቀ ኃይል አማካይነት ድል እየተቀናጀች ትገኛላች። አንዳንድ ጊዜ በግል ተግዳሮቶች እና በማሕበራዊ ጥፋቶች ምክንያት ተስፋችንን የሚጨለመ ቢመስልም ነገር ግን ኃይለኛ በሆነው የእግዚአብሔር ተግባር ላይ እምነት ሊኖረን ይገባል። በእዚህ ምክንያት በጨለማ እና በችግሮች ውስጥ በምንገባበት ወቅቶች ሁሉ እኛ መርበትበት አይኖርብንም፣ በእግዚኣብሔር በመተማመን በእርሱ ላይ ጸንተን ልንኖር ይገባ፣ ሁልጊዜ በሚያድነው በእግዚኣብሔር ተስፋ መተማመን ይኖርብናል። ይህንን ሁል ጊዜ አስታውሱ፡ እግዚኣብሔር ሁሌም ያድናንል። እርሱ አዳኝ ነውና።

በሁለተኛው ምሳሌ ላይ (ማርቆስ 4፡30-32) ኢየሱስ የእግዚኣብሔርን መንግሥት ከአንድ የሰናፍጭ ዘር ጋር በንጽጽር ሲያቀርብ እናገኛለን። በምድር ላይ ከሚዘራው ዘር ሁሉ እጅግ ያነሰችውን የሰናፍጭ ቅንጣት ትመስላለች፤ ተዘርታ ካደገች በኋላ ግን፣ ያልተጠበቀ አስገራሚ ዕድገት እንደ ምታሳይ ይናገራል። ለእኛ በእዚህ የእግዚኣብሔር አስተሳሰብ ውስጥ መግባት ወይም ይህንን መረዳት በጣም ቀላል የሆነ ነገር እና በሕይወታችን ውስጥ ይህንን እውነተ መቀበል በጣም ቀላል የሆነ ነገር አይደለም። ነገር ግን ዛሬ የእኛን እቅዶች፣ ስሌቶች፣ ትንበያዎቻችንን የሚያሸንፍ የእምነት አቋም እንዲኖረን ጌታ ያበረታታናል። እግዚአብሔር ሁሌም ያልታሰበ ነገር የሚያደርግ አምላክ ነው። ጌታ ሁሌም ያስገርመናል። በግለሰብ እና በማህበረሰብ ደረጃ ለእግዚኣብሔር የርኅራኄ እቅዶች በይበልጥ ራሳችንን እንድንከፍት የቀረበልን ግብዣ ነው። በማኅበርሰባችን ውስጥ ለሚገኙ ደካማ ለሆኑ ሰዎች ጥንቃቄ ማድረግ እንደ ሚገባን እና ጌታ ለእኛ ባሳየው በጎነት እንደ ታላቅ አጋጣሚ በመጠቀም በእርሱ ፍቅር፣ መስተንግዶ እና በሁሉም የምህረት ተግባራት ተነሳሽነት ውስጥ ተሳታፊ እንዲሆኑ ያደርጋል።

የቤተክርስቲያኗ ተልዕኮ እውነተኛነት የሚረጋገጠው ስኬታማ በመሆኗ ላይ ወይም ደግሞ አስደሳች የሆነ ውጤት በማስመስገቧ ላይ የተመሰረተ ሳይሆን ነገር ግን በታላቅ ብርታት በእግዚኣብሔር በመተማመን እና በእርሱ በመታቀፍ ወደ ፊት በመጓዟ ላይ የተመሰረተ ነው። እርሱን በመምሰከር እና በመንፈስ ቅዱስ ኃይል ወደ ፊት መጓዝ።  የእርሱ  ትንሽ እና ደካማ መሳሪያ መሆናችንን ከግንዛቤ በማስገባት ራሳችን በእግዚኣብሔር እጅ ውስጥ በማድረግ እና በእርሱ ጸጋ በመተማመን ታላላቅ የሚባሉ ተግባራትን በመፈጸም የእርሱ መንግሥት መገለጫ የሆኑትን “ፍትህ፣ ሰላም፣ እና በመንፈስ ቅዱስ አማክይነት የሚገኘውን ደስታ” ለማስፋፋት እንችላለን።

በዛሬው ወንጌላችን ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ትልቅ ተአምራትን ሲሰራ ያሳየናል፡፡ ተአምር ማለት አስደናቂ ሥራ ነው፡፡ እግዚአብሔር አምላክ በብሉይ ኪዳን ለሕዝቡ ማንነቱን ለማሳየትና ለማስተማር የተለያዩ ተአምራትን አድርጓል፡፡ ለምሳሌም በሙሴ በእያሱ በኤልያስ በመሳሰሉት ነብይት ተአምራትን አሳይቷል፡፡ በአዲስ ኪዳንም ጌታችንን መዳኃኒታችን ብዙ ተአምራትን እንዳደረገ አይተናል፡፡ ለምሳሌ በእናታችን ምልጃ ውሃን ወደ ወይን ለወጠ ፣ በውሃ ላይ ተራመደ ፣ ንፋስን ፀጥ በማድረግ ስልጣኑን አሳየ፡፡ አጋንንትን አወጣ ፣ ሰዎችን ከብዙ ደዌዎችና በሽታዎች ፈወሰ፡፡ ሦስት ሰዎችን ከሞት አስነሳ፡፡ ተአምራዊ ስራዎቹ እጅግ ብዙ ናቸው፡፡

የሰው ልጅ በሕይወት ዘመኑ ሁሉ የማይገጥመው የኑሮ ውጣውረድ ፣ የኑሮ ማዕበል ውሽፍርና ሞገድ የለምና የዚህ አይነት መከራ በራሱም በቤተሰቡም ይመጣበታል ፤ በሽታ ፣ ችግር ፣ የኑሮ ውድነት ተጠቃሾች ናቸው፡፡ የሰው ልጅ በነዚህ ችግሮች ሲወድቅ ሊመካበት ችግሩን ሊቋቋምበት የሚችልበትን ሀብት ፣ወገን ሊሻ የግድ ይለዋል፡፡በዚህ ወቅትም የራሱ ወገንም ሆነ ሀብት ይሸሹታል በዚህ ችግር ወቅት አይዞህ ባይ በርታ ባይ ያስፈልገዋል፡፡ በዚህ ችግር ወቅት አይዞህ ባይ በርታ ባይ ሲያጣ ተስፋ ይቆርጥል ፤ ራሱንም ይጠላና ራሱን ለማጥፋት ያስባል ምክንያቱም በዚህ ችግርና መከራ ውስጥ አይዙህ ባይ ከማጣቱም ባሻገር የራሱ የሆነ ጉልበት ሁሉ ይክደወል፡፡

ታዲያ ለዚህ መድኃኒቱ ምን ሊሆን ይችላል? ምንም ቢባል መልሱ አንድና አንድ ብቻ ነው፡፡ የሰናፍጭን ቅንጣት የምታክል እምነት ካለን በቂ እንደሆነ ንፋስም ባሕርም የሚታዘዙለት ፤ ባሕሩንም ሞገዳችንንም ፣ ችግሮቻችንንም ፣ በሽታዎቻችንንም ሁሉ ፀጥ ለጥ ብለው የሚገዙለት አምላክ ከእኛ ጋር  ነውና ለሱ መንገር ብቻ ነው፡፡

እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማሪያም ትሁት እና ጠንቃቆች በመሆን ከእምነታችንን ጋር በመተጋገዝ የእግዚኣብሔር መንግሥ በልባችን እና በታሪክ ውስጥ እንድታድግ በምናደርገው ጥረት ውስጥ እመቤታችን ትርዳን።

21 September 2019, 08:38