ካርዲናል ኩፒች ለርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቺስኮስ ጸሎት እንዲደረግ ጠየቁ
የእዚህ ዝግጅት አቅራቢ ዘላለም ኃይሉ
ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቺስኮስ ሮም በሚገኘው ጂሜሊ ሆስፒታል ውስጥ በሳንባ ምች በሽታ ምክንያት ሕክምናቸውን እየተከታተሉ ባሉበት በዚህ ወቅት ፥ የሁሉም እምነት ተከታዮች ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳቱን በጸሎታቸው እንዲያስቧቸው የቺካጎው ብፁዕ ካርዲናል ብሌዝ ኩፒች ጠይቀዋል።
"ዛሬ ማታ ለመተኛት ወደ አልጋችሁ ስትሄዱ ፥ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳቱን አስታውሱ እና ጸልዩላቸው ፥ ይህም መልዕክት ለሁሉም እምነት ተከታዮች ነው ፥ ምክንያቱም እሱ በዓለም ዙሪያ በብዙ ሰዎች ዘንድ የተከበረ እና የተወደደ እንደሆነ አውቃለሁ" ሲሉ የአሜሪካው ካርዲናል መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።
ከቅድስት መንበር የዜና ማሰራጫ ጽ/ቤት ሐሙስ ዕለት የተለቀቀው መግለጫ እንዳስታወቀው ፥ እያደረጉት ባለው ህክምና ጤንነታቸው እየተሻሻለ እንደሆነ ነው የተገለፀው።
ከርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቺስኮስ ቁልፍ አማካሪዎች አንዱ የሆኑት ካርዲናል ኩፒች እንደተናገሩት "እሳቸው በጣም ጠንካራ የሆኑ ሰው እንደሆኑ ስለማውቅ ፥ አገግመው ለመውጣት የተቻላቸውን ሁሉ ያደርጋሉ" ብለዋል። "እሳቸው ከዚህ በፊትም እንደሚችሉ አሳይተውና ፥ ህይወታቸውን በሙሉ አሳይተውናል ፥ እናም አሁን ያንን ያደርጋሉ በእሳቸው ተስፋ አንቆርጥም” ብለዋል ካርዲናሉ።
ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቺስኮስ ሐሙስ ዕለት በተለጠፈው የትዊተር ገፃቸው ላይ እንዳሉት ፥ ዓለም ላይ ካሉ ሁሉም አቅጣጫዎች በሚላክላቸው ብዙ መልዕክቶች ልባቸው እንደተነካ እና ለሚያሳዩት ቀረቤታ እና ጸሎቶች ምስጋናቸውን ገልጸዋል።