በኬንያ የኮቪድ-19 ወረርሽኝ መከላከያ ክትባት አሰጣጥ ሂደት በኬንያ የኮቪድ-19 ወረርሽኝ መከላከያ ክትባት አሰጣጥ ሂደት 

ኬንያ፣ የወረርሽኝ መከላከያ ክትባት ላልወሰዱት አገልግሎት መስጫዎቿን እንደምትገድብ አስታወቀች

ከዜጎቿ መካከል 8.8 ከመቶ ብቻ መሉ የኮቪድ-19 ወረርሽኝ ክትባትን የተቀበሉ ሰዎች ያላት ኬንያ፣ የመንግሥት አገልግሎቶችን የሚፈልጉ በሙሉ፣ ከታኅሳስ 12/2014 ዓ. ም. ጀምሮ ሙሉ የቫይረሱ መከላከያ ክትባቶችን የተቀበሉ መሆን እንዳለባቸው አሳስባ፣ መከላከያ ክትባቶችን ላልወሰዱት ዜጎች የመንግሥት አገልግሎት ተደራሽነትን እንደምትገድብ አስታውቃለች።

የዚህ ዝግጅት አቅራቢ ዮሐንስ መኰንን - ቫቲካን

አዋጁን ይፋ ያደረጉት የኬንያው ፕሬዝዳንት ኡሁሩ ኬንያታ፣ እሁድ ኅዳር 12/2014 ዓ. ም. እንደተናገሩት፣ 53 ሚሊዮን ከሚጠጉ የአገሪቱ ዜጎች መካከል ቢያንስ 10 ሚሊዮን የሚሆኑ እስከ አውሮፓውያኑ 2021 ዓ. ም. መጨረሻ ድረስ የኮቪድ-19 ክትባት ማግኘት እንዳለባቸው አሳስበዋል።

የሰብዓዊ መብት ታዛቢዎች በበኩላቸው እቅዱ ተግባራዊ ሊሆን እንደማይችል እና መንግሥትም በአራት ሳምንታት ጊዜ ውስጥ ከተገመተው ቁጥር ውስጥ ለአብዛኛው ክትባቱን ማድረስ እንደማይችል አስታውቀዋል። አክለውም በመንግሥት ውሳኔ የተደናገጡት ብዙ ሰዎች የዕለት መተዳደሪያቸውን ማግኘት እንደሚቸገሩ፣ በሕዝብ ማመላለሻዎች መገልገል እንደማይችሉ እና ልጆቻቸውን ወደ ትምህርት ቤት እንኳ ማድረስ ስለማይችሉ ያደረባቸውን ስጋት ገልጸዋል።

እገዳዎቹ ትምህርት ቤቶችን፣ ሆስፒታሎችን፣ ማረሚያ ቤቶችን እና የመጓጓዣ አገልግሎቶችን ጨምሮ በሁሉም የመንግሥት ተቋማት ሰራተኞች ላይ ተጽእኖ ከማሳደሩ በተጨማሪ፣ ጨዋታ ማዘወተሪያ ፓርኮች፣ ሆቴሎች፣ ቡና ቤቶች፣ ምግብ ቤቶች እና ሌሎች የንግድ ማዕከላት በአንድ ቀን ውስጥ 50 ሰዎች ወይም ከዚያ በላይ የሚያገኙበትን መንገድ እንደሚገድብ ተገልጿል።

ውሳኔው በምሥራቅ አፍሪካ ትልቁ የኢኮኖሚ ባለድርሻ አገር በሆነች ኬንያ ውስጥ የኮቪድ-19 ወረሽኝ መከላከያ ክትባትን በማዳረስ ወረርሽኙ ካስከተለው ኤኮኖሚያዊ ቀውስ ለማገገም መንግሥት ከወሰዳቸው እርምጃዎች መካከል አንዱ ነው ተብሏል።

23 November 2021, 16:31