በቫቲካን ውስጥ የሚገኘው ጳውሎስ 6ኛ የመሰብሰቢያ አዳራሽ ከታነጸ 50 ዓመት ሞልቶታል
የዚህ ዝግጅት አቅራቢ ዮሐንስ መኰንን - ቫቲካን
ለዚህ እጅግ ሰፊ እና ዘመናዊ የመሰብሰቢያ አዳራሽ የግንባታ ንድፍ አዘጋጅተው ያቀረቡት ታዋቂው ጣሊያናዊ አርክቴክ አቶ ፔር ሉዊጂ ስለነበሩ አልፎ አልፎ "Aula Nervi" ወይም ነርቪ የመሰብሰቢያ አዳራሽ እየተባለ ሲጠራ ይሰማል። አዳራሹ ባለፉት 50 ዓመታት ታሪኩ አምስት ርዕሳነ ሊቃነ ጳጳሳት የተገለገሉበት፣ በቁጥር በርካታ ምዕመናንን፣ መንፈሳዊ ተጓዦችን እና አገር ጎብኝዎችን ወደ አዳራሹ በመጋበዝ ሳምንታዊ የጠቅላላ ትምህርተ ክርስቶስ አስተምሮአቸውን ያቀረቡበት፣ መንፈሳዊ ስብሰባዎችን እና ሌሎች ልዩ ልዩ ዝግጅቶችን የመሩበት ምቹ ሥፍራ ነው።
ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ቅዱስ ጳውሎስ 6ኛ ረቡዕ ሰኔ 23/1963 ዓ. ም. በመሰብሰቢያው አዳራሽ የምረቃ ሥነ-ሥርዓት ላይ ለተገኙት በርካታ ምዕመናን ባሰሙት ንግግር አዳራሹ የተገነባው ርዕሳነ ሊቃነ ጳጳሳት ከሐዋርያዊ ተልዕኮዋቸው አንዱ የሆነውን ሳምንታዊ የረቡዕ ዕለት የጠቅላላ ትምህርተ ክርስቶስ አስተምህሮአቸውን ከዓለም ዙሪያ ለሚመጡት እንግዶች የሚያቀርቡበትን ምቹ ሥፍራን ለማዘጋጀት መሆኑን አስረድተዋል።
በቫቲካን ውስጥ የሚገኘው ጳውሎስ 6ኛ የመሰብሰቢያ አዳራሽ ላለፉት ሃምሳ ዓመታት ከመላው የዓለማችን ክፍሎች የሚመጡ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ምዕመናንን፣ መንፈሳዊ ተጓዦችን እና አገር ጎብኚዎችን ተቀብሎ ሲያስተናግድ መቆየቱ ይታወቃል። ከዚህም በላይ ርዕሳነ ሊቃነ ጳጳሳት በሮም ከተማ ውስጥ ከሚገኙ ድሃ እና መጠለያ አልባ ከሆኑ ሰዎች ጋር ማዕድ የሚካፈሉበት ሥፍራ ሆኖ በማገልገል ላይ ይገኛል። ባለፉት ቅርብ ወራትም በሮም ከተማ እና በቫቲካን ዙሪያ ለሚገኙ አቅመ ደካማ ተረጂዎች እና ለቫቲካን ተቀጣሪዎች የኮቪድ-19 ወረርሽኝ መከላከያ ክትባት ማዕከል ሆኖ ማገልገሉ ይታወሳል። የጳውሎስ 6ኛ መሰብሰቢያ አዳራሽ ሌላው አገልግሎት የመላዋ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን ብጹዓን ጳጳሳት ሲኖዶስ የሚሰበሰብበት ቦታ መሆኑ ይታወቃል።