ብጹዕ ሞንሲኞር ሪኖ ፊዚኬላ ጋዜጣዊ መግለጫ በሰጡበት ወቅት፤ ብጹዕ ሞንሲኞር ሪኖ ፊዚኬላ ጋዜጣዊ መግለጫ በሰጡበት ወቅት፤ 

ለኮሮና ቫይረስ ተጠቂዎች የሚደረግ የህክምና እርዳታ ለሁሉም ሊዳረስ ይገባል ተባለ።

በቅድስት መንበር የስብከተ ወንጌል አገልግሎት ጳጳሳዊ ጽሕፈት ቤት ፕሬዚዳንት የሆኑት ብጹዕ ሞንሲኞር ሪኖ ፊዚኬላ፣ ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ 4ኛውን ዓለም አቀፍ የድሆችን ቀን ምክንያት በማድረግ ያስተላለፉትን መልዕክት መሠረት በማድረግ ቅዳሜ ሰኔ 6/2012 ዓ. ም. በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፣ ለኮሮና ቫይረስ ተጠቂዎች የሚደረግ የክምና እርዳታ ደሃ እና ህብታም ሳይለይ ለሁሉም ተደራሽነት ሊኖረው ይገባል ብለው፣ ክርስቲያን ማኅበረሰብ የድሆችን የስቃይ ጩሄት አድምጦ የዕርዳታ እጁን በመዘራጋት ቀዳሚ ሚና ታጫዋች እንዲሆን አደራ ብለዋል።

የቫቲካን ዜና፤

ከእግዚአብሔር ጋር የማያስቋርጥ ግንኙነት ካለ ሁለት የማይለያዩ ነገሮችን እነርሱም ጸሎታችንን ወደ እግዚአብሔር ዘንድ ማቅረብን እና በስቃይ ውስጥ ለሚገኙ ድሆች የእርዳታ እጃችንን መዘርጋት እንማራለን” ያሉት የርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ ዓለም አቀፍ የድሆች ቀን መልዕክት መሠረት በማድረግ ብጹዕ አቡነ ሪኖ ፊዚኬላ ጋዜጣዊ መግለጫቸውን ሰጥተዋል። በእግዚአብሔር አምሳያ መፈጠራችን ድሆችን እንድንመለከት ያስገድደናል ብለው ክርስቲያናዊ ሕይወታችንን በሙላት እንድንኖር ያግዘናል ብለዋል። እጃችንን ድሆችን ለማርዳት መዘርጋት ማኅበራዊ ችግር ውስጥ የወደቁ ድሆችን ለመርዳት የሚያዝ የእግዚአብሔር ትዕዛዝ በተግባር ለመመስከር ያስገድደናል ብለዋል።

የቤተክርስቲያን ቸርነት፣

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ በህዳር 6/2013 ዓ. ም. ለሚከበረው 4ኛ ዓለም አቀፍ የድሆች ቀን የመረጡት መሪ ቃል፥ “እጅህን ለድሆች ዘርጋ" (ሲራ. 7:32) የሚል መሆኑን ያስታወሱት ብጹዕ ሞንሲኞር ሪኖ ፊዚኬላ፣ የቅዱስነታቸው መልዕክታቸው በኮሮና ቫይረስ ምክንያት የዓለማችን ሕዝብ እየኖረ የሚገኘውን ይስቃይ ሕይወት የሚገልጽ ነው ብለው በወረርሽኙ ምክንያት የዕርዳታ ጠያቂዎች ቁጥር ሊጨምር እንደሚችል ገልጸዋል። በችግር ውስጥ ለወደቁት ሰዎች የዕርዳታ እጆቻችንን ማጠፍ የለብንም ብለው የተቸገረን መርዳት የቤተክርስቲያን የዘወትር ሐዋርያዊ ተግባሯ ነው፣ ቤተክርስቲያንም ይህን ሐዋርያዊ ተግባሯን ስታበረክት መቆየቷን አስታውሰዋል። የቤተክርስቲያንን ሐዋርያዊ ተግባር አስመልክቶ ለቀረበላቸው ጥያቄ መልስ ሲሰጡ፣ ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ በቅርቡ በኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ምክንያት በችግር ውስጥ የወደቁትን የሮም ከተማ ነዋሪዎች ለመርዳት “ኢየሱስ መለኮታዊ ሠራተኛ” በሚል ስያሜ የመረዳጃ ማኅበር ማቋቋማቸውን አስታውሰው የሐዋርያዊ ተግባር ጥሪ ለክርስቲያን ማኅበረሰብ ብቻ የቀረበ ጥሪ እንዳልሆነ አስረድተው ባሁኑ ጊዜ ዕርዳታን በማቅረብ ተግባር ላይ የተሰማሩ የተለያዩ በርካታ ድርጅቶች እና ግለ ሰቦች መኖራቸዋን አስረድተዋል።

የሳይንስ ግኝት ሁሉን የሚጠቅም መሆን አለበት፤

ሳይንሳዊ የምርምር ውጤቶችን ያስታወሱት ብጹዕ ሞንሲኞር ሪኖ ፊዚኬላ፣ የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ መድኃኒት ተደራሽነትን አስመልክተው እንደገልጹት፣ የቤተክርስቲያን ጥሪ የግል ሳይሆን ማኅበራዊ ጥቅምን ያማከለ በመሆኑ ሳይናሳዊ ግኝቶች የተወሰኑ ሰዎች ፍላጎትን ብቻ የሚያሟሉ ወይም በተወሰኑ ጂኦግራፊያዊ አካባቢዎች ብቻ ተወስኖ መቅረት እንደሌለባቸው አሳስበዋል። ከዚህ በፊት የተዛመቱ የቫይረስ ዓይነቶችን የጠቀሱት ብጹዕ ሞንሲኞር ሪኖ ፊዚኬላ፣ ከኣዓመታት በፊት የኤይድስ ቫይረስ ስርጭት በተከሰተበት ወቅት እንደ መከላከያነት የቀረበው መድኃኒቱ በአፍሪቃ ውስጥ ከሕዝቡ የመግዣ አቅም ጋር የማይመጣጠን እንደነበር አስታውሰው፣ ሳይንሳዊ ግኝቶች ወደ ሁሉም ዘንድ መድረስ እንዳለባቸው አሳስበው፣ ይህ ካልሆነ ግን ፍትህን እንደሚያዛባ እንዲሁም የእግዚአብሔርን እቅድ የሚጻረር መሆኑን አስረድተዋል።

ችግሮችን ለማስወገድ የተዘረጉ እጆች፣

ገንዘብን ለግል ጥቅም ብቻ በመሰብሰብ ላይ የሚገኙ እጆች ድህነትን ለማስወገድ የሚያደርጉት እገዛ የለም ያሉት ብጹዕ ሞንሲኞር ሪኖ ፊዚኬላ በመግለጫቸው እንደገለጹት፣ ባሁኑ ጊዜ ማኅበራዊ ሃላፊነት የጎደላቸው ተቋማት በመኖራቸው ምክንያት ድህነት ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ መምጣቱን ጠቁመው፣ የቸርነት እና የልግዝና ተግባር ከራስ ወዳድነት እጅግ በልጦ መገኘቱን ገልጸው፣ የዕርዳታ እጆችን በመዘርጋት የሰዎችን ስቃይ ማስወገድ እንደሚያስፈልግ አሳስበዋል። ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ በሰዎች መካከል የሚፈጠሩ ልዩነቶችን በመቃወም ብዙን ጊዜ መልዕክት ማስተላለፋቸውን ያስተወሱት ብጹዕ ሞንሲኞር ሪኖ ፊዚኬላ፣ ክርስቲያን ማኅበረሰብ ድሆችን በመርዳት ቀዳሚ ተዋናይ መሆን እንዳለባቸው አሳስበው፣ በቤተሰብ መካከል አንዱ ሲቸገር ሌላው በዝምታ መመልከት የለበትም ብለው የር. ሊ. ጳ. ፍራንችስኮስ መልዕክትም የተቸገሩትን እንድንረዳቸው የቀረበ ጥሪ መሆኑን አስረድተዋል።            

15 June 2020, 16:20