ር.ሊ.ጳ ፍራንቸስኮስ “ቅዱስ ወንጌልን ማብሰር እና መስቀሉን መሸከም የተያያዙ ነገሮች ናቸው” አሉ!

የጎርጎሮሳውዊያኑን የቀን አቆጣጠር በሚከተሉ የካቶሊክ ቤተክርስቲያን ምዕመናን ዘንድ አሁን የምንገኝበት ወቅት የሕማማት ሳምንት ውቅት እንደ ሆነ ይታወቃል። በእዚህ የሕማማት ሳምንት ውስጥ በካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ስርዐተ አምልኮ ደንብ መሰረት እኛን ለማዳን እና ከእግዚኣብሔር ጋር እኛን ለማስታረቅ ራሱን መስዋዕት አድርጎ ያቀረበው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተላልፎ መሰጠቱን፣ መንገላታቱን፣ በመስቀል ላይ እንደ ሌባ መሰቀሉን፣ መሞቱን፣ መቀበሩን እና ከሙታን መነሳቱን እነዚህ ሁሉ ነገሮች የተከናወኑባቸው ሦስት ዋና ዋና ቀኖች በተለየ ሁኔታ በታላቅ መንፍሳዊነት ይከበራሉ። ከእነዚህ ቅዱሳን ከሆኑ ቀናት መካከል በቀዳሚነት የሚገኘው የጸሎተ ሐሙስ ቀን ሲሆን በዚህ እለት ኢየሱስ መከራውን ከመቀበሉ በፊት ከደቀ-መዛሙርቱ ጋር የመጨረሻውን ራት ከመብላቱ በፊት የሐዋሪያቱን እግር ያጠበበት፣ እርሱ በምድር ላይ በነበረበት ወቅት የጀመረውን መንፈሳዊ ተልዕኮ እንድያስቀጥሉ በማሰብ ምስጢረ ክህነትን የመሰረተበት፣ የመጨረሻ ራት ከደቀ-መዛሙርቱ ጋር ከተካፈለ በኃላ “ይህንን ለእኔ መታሰቢያ አድርጉ” በማለት ምስጢረ ቅዱስ ቁርባንን የመሰረተበት፣ ብጹዕን ጳጳሳት በእየአገረ ስብከታቸው ከካህናቶቻቸው ጋር መስዋዕተ ቅዳሴን በማሳረግ ምስጢረ ክህነት የተመሰረተበትን ቀን በማስታወስ በጋራ መስዋዕተ ቅዳሴን የሚያሳርጉበት፣ ለምስጢረ ቀንዲል (ሕሙማንን ለመፈወስ የሚያገልግል ቅባ ቅዱስ)፣ ለሚስጢረ ጥምቀት እና ለምስጢረ ክህነት አግልግሎት የሚውሉ ቅባ ቅዱሶች በብጽዕን ጳጳሳት የሚባረኩበት እለት ተከብሮ ማለፉ ታውቁዋል። በእለቱ ቅዱስንታቸው ያደርጉት ስብከት በእለቱ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የመሰረተውን የምስጢረ ክህነት ምስጢር ላይ ትኩረቱን ያደረገ እንደ ነበር ተገልጿል።  

የዚህ ዝግጅት አቅራቢ መብራቱ ኃ/ጊዮርጊስ-ቫቲካን

ይህ በዓል በመጋቢት 23/2013 ዓ.ም በቫቲካን በሚገኘው በቅዱስ ጴጥሮስ ባዚሊካ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ ባሳረጉት መስዋዕተ ቅዳሴ ተከብሮ ማለፉ የታወቀ ሲሆን በእለቱ ቅዱስነታቸው ባሳረጉት መሳዋዕተ ቅዳሴ ላይ ባሰሙት ስብከት እንደ ገለጹት “ቅዱስ ወንጌልን ማብሰር እና መስቀሉን መሸከም የተያያዙ ነገሮች ናቸው” ማለታቸው ተገልጿል።

ክቡራን እና ክቡራት የዝግጅቶቻችን ተከታታዮች ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ በወቅቱ በቫቲካን በሚገኘው በቅዱስ ጴጥሮስ ባዚሊካ ባሳረጉት መስዋዕተ ቅዳሴ ላይ ያሰሙትን ስብከት ሙሉ ይዘቱን እንደ ሚከተለው አሰናድተነዋል ተከታተሉን።

የዛሬው ቅዱስ ወንጌል ጌታን በሚያዳምጡ ሰዎች መካከል የታየውን የልብ መለወጥ ያሳየናል። ለውጡ አስገራሚ ነበር ፣ እናም ስደት እና መስቀሉ ከወንጌል አዋጅ ጋር ምን ያህል እንደተያያዙ ያሳያል። ኢየሱስ በተናገረው በጸጋ የተሞሉ ቃላት የተቀሰቀሱት አድናቆቶች በናዝሬት ሰዎች አእምሮ ውስጥ ለረጅም ጊዜ አልቆዩም ነበር። አንድ ሰው በማጉረምረም የሰጠው አስተያየት በስውር እንደ ቫይረስ ተሰራጭቶ ስለነበር “ይህ የዮሴፍ ልጅ አይደለምን?” (ሉቃስ 4፡22) ይባባሉ ነበር።

በመሰራጨት ላይ ከነበሩ ከተደበቁ አሻሚ መግለጫዎች አንዱ ነበር። አንድ ሰው “እንደዚህ ዓይነት ትሑት ሰው በዚህ ሥልጣን መናገሩ እንዴት ደስ ይላል!” በማለት ስለእርሱ በማንደቅ ሊጠቀምበት ይችላል! ሌላ ሰው “እና ይሄኛው ከየት ነው የመጣው? በማለት በንቀት ለመናገር ሊጠቀምበት ይችላል፣ እሱ ማን ነው ብሎ ያስባል? ” ስለእሱ ካሰብን ሐዋርያት በመንፈስ ቅዱስ ተሞልተው ወንጌልን መስበክ በጀመሩበት በበዓለ ሃምሳ ቀን የተነገሩትን ተመሳሳይ ቃላት መስማት እንችላለን። አንዳንዶቹ “እነዚህ የሚናገሩት ሁሉ የገሊላ ሰዎች አይደሉምን?” (የሐዋርያት ሥራ 2: 7) በማለት አንዳንዶቹ ቃሉን ሲቀበሉ ሌሎቹ ደግሞ ሐዋርያቱ ሰክረዋል ብለው ያስቡ ነበር።

በትክክል ለመናገር ያህል በናዝሬት የተነገሩት እነዚህ ቃላት በየትኛውም መንገድ ሊተረጎሙ ይችላሉ፣  ነገር ግን የተከሰተውን ነገር ከተመለከትን በዚያን ጊዜ በኢየሱስ ላይ ይዘራ የነበረው የዓመፅ ዘር ፍሬ እያፈራ እንደ መጣ ግልፅ ነው።

እነሱ “የማረጋገጫ ቃላት” ነበሩ ፣ ለምሳሌ አንድ ሰው “ይህ በጣም እጅግ የበዛ ነገር ነው!” ይልና ከዝያን በኋላ በሌላው ሰው ላይ ጥቃት ይፈጽማል ወይም ትቶት ይሄዳል።

በዚህያን ጊዜ ​​አንዳንድ ጊዜ ምንም ነገር የማይናገር የሚመስል ወይም በቀላሉ እንዲህ ዓይነት ነገር ሲያጋጥመው ትቶ የሚሄደው ጌታ አስተያየታቸው እንዲያው በከንቱ እንዲያልፍ አልፈቀደም። ይልቁንም በቀላሉ በመንደር ውስጥ የሚነዛው ሀሜት ሽፋን የተደበቀውን መጥፎ ድርጊት ገለጠ። ይህ በአንተ ላይ የደርሰ ነገር ቢሆን ኖሮ “‘ባለ መድኀኒት ሆይ፤ ራስህን ፈውስ። በቅፍርናሆም እንዳደረከኸውን እና እኛ የሰማነውን ነገር እዚህ በአገርህ እንዲሁ አድርግ! ” (ሉቃስ 4 23) “ራስህን አድን…” በማለት ልትጠቅስ እንችላለን።

“ራስህን አድን”። እዚህ ጋር እንድ የተያዘ አቋም አለ! እነዚያ ተመሳሳይ ቃላት ጌታን እስከ መስቀል ሞት ድረስ ይከተላሉ- “ሌሎችን አዳነ ፣ እስቲ ራሱን ያድን” (ሉቃ 23፡35)። “አንተ ክርስቶስ አይደለህምን? እስቲ፣ ራስህንም እኛንም፣ አድን” (ሉቃስ 23፡ 39) በማለት ከእርሱ ጎን ከተሰቀሉት ከሌቦቹ አንዱ ይናገራል።

እንደ ሁልጊዜው ጌታ ከክፉው መንፈስ ጋር ለመነጋገር ፈቃደኛ አይሆንም ፣ እሱ የሚመልሰው በቅዱሳት መጻሕፍት የተጠቀሱትን ቃላት ተጠቅሞ ብቻ ነው። ነቢያት ኤልያስ እና ኤልሳዕ በበኩላቸው በገዛ አገራቸው ሰዎች ሳይሆን አቀባበል የተደረገላቸው ነገር ግን በፊንቄያዊቷ መበለት እና በለምጽ በሽታ ተይዞ በነበረው በሶሪያዊው ነማን ነበር ተቀባይነትን ያገኙት፣ -ሁለት የውጭ አገር ዜጎች ፣ ሁለት የሌላ ሃይማኖት ተከታይ የነበሩ ሰዎች። ይህ ራሱ አስገራሚ የሆነ ነገርና በእድሜ የገፋው ስምዖን በመንፈስ ቅዱስ አነሳሽነት ስለኢየሱስ የተነገረው ትንቢት ምን ያህል እውነት እንደነበረ ያሳያል “ይህ ሕፃን በእስራኤል ለብዙዎች መነሣትና መውደቅ ምክንያት እንዲሆን፣ ደግሞም ክፉ ለሚያስወሩበት ምልክት እንዲሆን ተወስኖአል” (ሉቃ 2፡34) እንደ ተጠቀሰው።

የኢየሱስ ቃላት እያንዳንዳችን በልባችን ጥልቀት ውስጥ የያዝነውን ማንኛውንም ነገር ወደ ብርሃን የማምጣት ኃይል አላቸው ፣ ብዙውን ጊዜ እንደ ስንዴ እና እንክርዳድ የተደባለቀ ነገር በውስጣችን ቢኖርም እንኳን ሁሉንም ነገር ወደ ብርሃን ያመጣቸዋል። እናም ይህ መንፈሳዊ ግጭት እንዲከሰት ይቀሰቅሳል። የጌታን እጅግ የበዛ የምሕረት ምልክቶች በማየታችንና “በተራራ ላይ የተሰበከውን የብጽዕና መስመሮች” መስማት እንዲሁም በቅዱስ ወንጌል ውስጥ የተጠቀሰውን “ወየውላችሁ” በሚለው ቃል እራሳችንን እንድንገነዘብ እና እንድንወስን ተገደናል። በዚህ ሁኔታ የኢየሱስ ቃላት ተቀባይነት አላገኙም ነበር፣ እናም ይህ በቁጣ የተሞላው ህዝብ እሱን ለመግደል ሙከራ አደረገ። ነገር ግን ገና የእርሱ “ሰዓት” አልደረሰም ነበርና፣ እናም ቅዱስ ወንጌል እንደ ምነግረን በእዚህ ምክንያት ጌታ “በመካከላቸው አልፎ ሄደ” ይለናል።

የእርሱ ሰዓት አልነበረም ፣ ሆኖም የሕዝቡ ቁጣ የተገለጠበት ፍጥነት እና ጌታን በቦታው ለመግደል የተደረገው በቁጣ የተሞላ ጭካኔ ሁል ጊዜ የእርሱ ሰዓት መሆኑን ያሳየናል። ውድ ካህናት ዛሬ ለእናንተ ላካፍላችሁ የምፈልገው - የደስታ አዋጅ ሰዓት ፣ የስደት ሰዓት እና የመስቀል ሰዓት አብረው እንዲሄዱ ልገልጽላችሁ እወዳለሁኝ።

የቅዱስ ወንጌል ስብከት ሁል ጊዜ ከተወሰነ መልኩ መስቀሉን ከማቀፍ ጋር የተቆራኘ ነው። የእግዚአብሔር ቃል ረጋ ያለ ብርሃን በጥሩ ልብ ውስጥ በደንብ ያበራል ፣ ነገር ግን በሌሎች ሰዎች ውስጥ ግራ መጋባትን እና አለመቀበልን ያነቃቃል። በቅዱስ ወንጌሎች ውስጥ ይህንን ደጋግመን እናየዋለን።

በእርሻው ውስጥ የተዘራው ጥሩ ዘር ፍሬ ያፈራል - መቶ፣ ስልሳ እና ሰላሳ እጥፍ ያፈራል- ነገር ግን ደግሞ በሌሊት አረም ለመዝራት የሚመጣውን የጠላት ምቀኝነት ያስነሳል (ማቴዎስ 13: 24-30.36-43) .

ርህሩህ የሆነው መሐሪ አባት የጠፋው ልጅ ወደ ቤት እንዲመለስ ያደርገዋል፣ ነገር ግን በታላቁ ልጅ በኩል ደግሞ ቁጣ እና ቂም ያስከትላል (ሉቃ. 15፡11-32)። የወይን እርሻው ባለቤት የነበረው ሰው ልግስና በመጨረሻው ሰዓት ለተጠሩት ሠራተኞች አመስጋኝ እንዲሆኑ ያደረጋቸው ሲሆን ነገር ግን በመጀመሪያ ወደ ሥራው የተጠሩ ሰዎች መካከል በርካታዎቹ በአሰሪው ልግስና ቅር ተሰኝተው የመረረ ምላሽ እንዲሰጡ ያደርጋቸዋል (ማቴዎስ 20፡1-16)።

ከኃጢአተኞች ጋር አብሮ የሚበላው የኢየሱስ ቅርበት እንደ ዘኬዎስ ፣ እንደ ቀራጩ ማቴዎስ እና እንደ ሳምራዊቷ ሴት ያሉ ልቦችን ያሸንፋል ፣ ነገር ግን በራሳቸው ፍላጎት በሚመጻደቁ ሰዎች ላይ እንዲሁ የንቀት ስሜትን ያስነሳል።

የወይን እርሻውን በተከራዩ ገበሬዎች ዘንድ “ልጄን ያከብሩታል” ብሎ በማሰብ በመጨረሻው ላይ ልጁን የላከው ንጉሥ ታላቅነት በውስጣቸው ከምንም በላይ ጭካኔን ያስነሳል። እዚህ ላይ እኛ ወደ ጻድቁ ግድያ የሚወስድ የክፋት ምስጢር ፊት እራሳችንን እናገኛለን (ማቴ. 21 33-46 ይመልከቱ)።

ውድ ወንድሞቼ ካህናት ይህ ሁሉ የምሥራቹ ቃል ስብከት በምስጢር ከስደት እና ከመስቀል ጋር የተቆራኘ መሆኑን እንድናስተውል ያደርገናል።

የሎዮላ ቅዱስ ኢግናሲዮስ ሲናገር “ቤተሰብን ማስተዋወቅ” በተመለከተ ይቅርታን ከመጠየቅ በመነሳት ሲናገር - በጌታ ልደት ላይ በማሰላሰል ይህንን የወንጌላዊነት እውነት ይገልጻል። እዚያም “በከፍተኛ ድህነት እና ከብዙ ድካም በኋላ ጌታ እንዲወለድ - ቅዱስ ዮሴፍ እና እመቤታችን ጉዞአቸውን ሲያደርጉ ያዩትን እናስተውል” - ረሃብ ፣ ጥማት ፣ ሙቀት እና ብርድ ፣ የአካል ጉዳት እና ንቀት - በመስቀል ላይ ሞተ ፣ እና ይህ ሁሉ ለእኔ ” በመቀጠልም “በዚህ ላይ በማስተንተን ጥቂት መንፈሳዊ ትርፍ እንድናገኝ” ይጋብዘኛል በማለት ይናገራል። የጌታ ልደት ደስታ፣ የመስቀሉ ሥቃይ፣ ስደት ያስከትላል በማለት ይናገራል።

በቅዱስ ወንጌል ስብከት መጀመሪያ እና እምብርት ወይም ማዕከል ላይ ይህን የመጀመሪያ የመስቀል ገጽታ - አለመግባባት ፣ ውድቅ እና ስደት በማሰላሰል ለክህነት ህይወታችን “ጥቂት ትርፍ” ለማግኘት ምን ዓይነት አስተንትኖ ማድረግ እንችላለን?

ሁለት ሀሳቦች ወደ እኔ ይመጣሉ!

አንደኛ-ገና ከመወለዱም በፊት በአገልግሎቱ መጀመሪያ ላይ በጌታ ሕይወት ውስጥ ከመወለዱ በፊት እንኳን ሳይቀር መስቀልን በጌታ ሕይወት በማየት ተደንቀናል። በመልአኩ መልእክት ላይ በማርያም የመጀመር ያ ግራ መጋባት ውስጥ ቀድሞውኑ የተገለጸ ነው፣ ዮሴፍ በእንቅልፍ ላይ ሆኖ ማርያምን ማንም ሳይውቅ በድብቅ ሊተዋት ግዴታ እንዳለበት ሲሰማው ከእዚያ ይጀምራል። ከትውልድ አገራቸው በስደት ለመኖር እንደ ተገደዱ ሌሎች ብዙ ቤተሰቦች ሁሉ በሄሮድስ ስደት እና በቅዱስ ቤተሰብ በተፈጠረው ችግር ውስጥ  የመስቀሉ ጅማሬ ይታያል።

ይህ ሁሉ የመስቀሉ ምስጢር “ከመጀመሪያው” ጀምሮ እንደሚገኝ እንድንገነዘብ ያደርገናል። መስቀሉ በጌታ ሕይወት ውስጥ በአጋጣሚ የተከሰተ ነገር እና ከእዚያም አልፎ ተርፎ በኋላ ላይ የተከሰተ ነገር አድርገን የምናስብ አለመሆኑን እንድንገነዘብ ያደርገናል። እውነት ነው ሌሎችን በታሪክ ሂደት ውስጥ ሁሉ የሚሰቅሉ ሰዎች ሁሉ እያደረጉት የሚገኘው የስቅለት ተግባር የጎኒዮሽ እክል አድርገው መቁጠር ይመስላቸዋል፣ ነገር ግን ያ እንደዛ አይደለም - መስቀሉ በአጋጣሚ የመጣ ነገር ሆኖ ሊታይ በፍጹም አይገባውም። ትላልቅ እና ትናንሽ የሰው ልጆች መስቀሎች ፣ የእያንዳንዳችን መስቀሎች በአጋጣሚ የተከሰቱ አይደሉም።

ጌታ ለምን ድነው መስቀሉን ሙሉ በሙሉ እና እስከ መጨረሻው መሸከም የፈለገው? ለምንድነው ኢየሱስ ሙሉ ሕማሙን ለመቀበል የፈቀደው? -ከመጨረሻው እራት በኋላ በጓደኞቹ ክህደት እና መተው ፣ ህገ-ወጥ እስር ፣ የፍርድ ሂደት እና ያልተመጣጠነ ፍርድ ፣ በጭካኔ የተደበደበበት እና ከቶውኑ ሊተላለፍበት የማይችል አመፅ ...ወዘተ ለምን ተፈጠረ? ተራ ሁኔታዎች የመስቀልን የማዳን ኃይል ሁኔታ ቢያመቻቹ ኖሮ ጌታ ሁሉንም ነገር ባልተቀበለ ነበር። ነገር ግን ጊዜው ሲደርስ መስቀሉን ሙሉ በሙሉ አምኖ ተቀበለ። በመስቀል ላይ ምንም አሻሚ ነገር ሊኖር አይችልም! መስቀሉ ለድርድር የማይቀርብ ነገር ነው።

ሁለተኛው ሀሳብ-እውነት የተሰኘው ነው ፣ የእኛ ሰብአዊ ሁኔታ ፣ ገደቦቻችን እና ደካማነታችን ወሳኝ አካል የሆነ የመስቀል ገጽታ አለ። ሆኖም በመስቀሉ ላይ ከሰው ልጅ ድክመቶች ጋር የማይገናኝ፣ ነገር ግን የእባቡን ንክሻ የሚመለከት አንድ ነገር መከሰቱ እውነት ነው ፣ ተከላካይ የሌለው የሚመስለውን የተሰቀለውን ጌታ ተመልክቶ ሥራውን ሁሉ ለመመርዝ እና ለመቀልበስ ይሞክራል። ለማሸማቀቅ የሚሞክር ንክሻ - እና ይህ መጥፎ ምሳሌ የሚተው ጊዜ ነው - ዋጋ ቢስ፣ ትርጉም የለሽ እና ሁሉንም አገልግሎት፣ የሌሎች መስዋዕትነት ለማሰናከል እና ለማቅረብ የሚሞክር ንክሻ። እሱ አጥብቆ የሚዋጋን እና የሚቀጥለው ጊዜ ክፉው የሆነ መርዝ ነው ራሳችሁን ከእዚህ ጠብቁ።

የእግዚአብሔርን ድል በመጨረሻ የምታየው ሞትን ለማምጣት በሚፈልግ በዚህ ከባድ እና ህመም “ንክሻ” ውስጥ ነው። የምስጢረ ንስሐ አገልግሎት ይሰጥ የነበረው ቅዱስ ማክሲሞስ በተሰቀለው ኢየሱስ ውስጥ የተገላቢጦሽ ሁኔታ እንደተከናወነ ይነገራል። የጌታን ሥጋ በመንከሱ የተነሳ ዲያቢሎስ አልተመረዘም፣ በእርሱ ውስጥ ያጋጠመው ነገር ቢኖር ማለቂያ የሌለው የዋህነት እና የአብን ፈቃድ በታዛዢነት ብቻ መፈጸሙን የሚያመልክት መንፈስ ነው። ይልቁንም በመስቀሉ መንጠቆ ተይዞ ለእርሱ መርዛማ ሆኖ የቀረውን የጌታን ሥጋ  በላ፣ ለእኛ ግን ይህ ሥጋ የክፉውን ኃይል ገለል የሚያደርግ መድኃኒታችን መሆን ነበረበት።

እነዚህ የእኔ ነጸብራቆች ናቸው። ከዚህ ትምህርት ተጠቃሚ ለመሆን ጸጋውን ጌታን እንለምነው ። እውነት ነው እኛ በወንጌል ስብከታችን መስቀሉ በማዕከሉ አለ ፣ ነገር ግን እሱ የመዳናችን መስቀል ነው። ለኢየሱስ እርቅ ደም ምስጋና ይግባውና ክፉን የሚያሸንፍ እና ከክፉው የሚያድነን የክርስቶስን ድል ኃይል የያዘ መስቀል ነው ። ከኢየሱስ ጋር ለመቀበል እና ከእኛ በፊት እንዳደረገው ፣ ወደ ውጭ ለመሄድ እና ለመስበክ በሕይወታችን ውስጥ ባልታሰበ ሁኔታ መስቀል በሚታይበት ጊዜ ሁሉ ዲያብሎስ እኛን ለመመርዝ በሚፈልግበት ጊዜ ሁሉ የቅሌትን መርዝን ለመለየት እና ውድቅ ለማድረግ ይረዳናል።

እነዚህ የእኔ አስተንትኖዎች ናቸው። ከዚህ ትምህርት ተጠቃሚ ለመሆን ጸጋውን ይሰጠን ዘንድ ጌታን እንለምነው። እውነት ነው፣ እኛ በወንጌል ስብከታችን ውስጥ መስቀሉ አለ ፣ ነገር ግን እሱ የመዳናችን መስቀል ነው። አስታራቂ ለሆነው ለኢየሱስ ደም ምስጋና ይግባውና ክፉን የሚያሸንፍ እና ከክፉው የሚያድነን የክርስቶስን ድል አድራጊነት ኃይል የያዘ መስቀል ነው። ከኢየሱስ ጋር መስቀሉን ለመቀበል እና እርሱ ከእኛ በፊት ቀድሞ እንዳደርገው፣ ለመውጣት እና እርሱን ለመስበክ በሕይወታችን ውስጥ ባልታሰበ ሁኔታ መስቀል በሚታይበት ጊዜ ሁሉ ዲያብሎስ እኛን በመርዝ ሊመርዘን በሚፈልግበት ፈታኝ በሆኑ ጊዜያት መርዛም የሆኑ ነገሮችን ለመለየት እና እንድንወድቅ የሚያደርጉንን ነገሮች ለይተን ማወቅ ይኖርብናል። ይህንን በተመለከተ ብዙ አስተንትኖዎች ተሰጥተዋል። በእነዚህ አስተምህሮዎች ጸጋን ማግኘት እንችል ዘንድ ጌታን እንለምነው።

የዕብራዊያን መጽሐፍ ጸሐፊ እንደ ተናገረው “እኛ ግን አምነው ከሚድኑት ወገን እንጂ፣ ወደ ኋላ አፈግፍገው ከሚጠፉት አይደለንም” ዓይነት ሰዎች ነን(ዕብራዊያን 10፡39)። “እኛ ተሸማቀው ወደ ኋላ ከሚመለሱ ሰዎች መካከል  አይደለንም” ። ይህ የዕብራዊያን መልእክት ጸሐፊ የሚሰጠን ምክር ነው። እኛ በእነዚህ ዓይነት ነገሮች ውስጥ ገብተን አንሰናከልም፣ ምክንያቱም ኢየሱስ ራሱ በደስታ ለድሆች በሚያደርገው የደኅንነት ስብከት በሙሉ ልቡ እንዳልተቀበሉት ቢያውቅም በእዚህ ነገር ግን አልተሸነፈም፣  ነገር ግን ቃሉን ለመስማት አሻፈረኝ ያሉ ወይም ቃሉን ለመስማት ፈቃደኛ ያልሆኑ ወይም ሕጋዊ ወደ ሆኑ የሕግ ድንጋጌዎች ለመቀነስ የሚፈልጉ ሰዎች ጩኸት እና ዛቻ መካከል ተቀባይነትን አላገኘም።

እኛ ኢየሱስ ጥሩ ነገር ባደረገ ቁጥር በሚነሱ የሥነ ምግባር ፣ የሕግ እና የክህነት ውዝግቦች መካከል የታመሙትን በመፈወስ እና እስረኞችን እንዲፈታ በማድረጉ ሂደት ውስጥ በሚከሰቱ ነገሮች መሰናከል የለብንም።

ማየት ለማይችሉ ሰዎች የማየት ብቃታቸውን ተመልሰው እንዲያገኙ፣ ተዘግተው የነበሩ ዓይኖቻቸው ብርዐን እንዲያገኙ ለማደረግ የዓይነ ስውራን ዐይኖች ተመልሰው እንዲያዩ ማድረጉ እንቅፋት አልሆነብንም።

የወንጌል ስብከት ውጤታማ የሚሆነው በንግግራችን ቃላቶች ሳይሆን በመስቀሉ ኃይል ምክንያት ስለሆነ እኛ መከራዎችን ልንፈራ አይገባም (1 ቆሮ 1፡17)።

በቅዱስ ወንጌል ስብከታችን መስቀልን የምንቀበልበት መንገድ - በተግባር እና አስፈላጊ በሚሆንበት ጊዜ - ሁለት ነገሮችን ግልፅ ያደርገናል። ከቅዱስ ወንጌል የሚመጡ መከራዎች የእኛ አይደሉም ፣ ነገር ግን ይልቁን “በእኛ ውስጥ ያለው የክርስቶስ ሥቃይ” (2 ቆሮ 1 5) ውጤቶች ናችሁ፣ እናም “እኛ የምንሰብከው ክርስቶስ ኢየሱስ ጌታ መሆኑን እንጂ ራሳችንን አይደለምና፣  እኛም ራሳችን ስለ ኢየሱስ ስንል የእናንተ አገልጋዮች ሆነናል””(2 ቆሮ 4፡5)።

አንድ ከእዚህ ቀደም የገጠመኝ ትዝታዬን በማካፈል የዛሬውን አስተንትኖ ለማጠቃለል እፈልጋለሁ!  “በአንድ ወቅት በሕይወቴ በጨለማ ጊዜ ውስጥ ጌታ ከአስቸጋሪና ውስብስብ ሁኔታ ነፃ የሚያወጣኝን ጸጋ እንዲሰጠኝ ጠየኩ። የጨለማ ጊዜ ውስጥ ነበርኩኝ። እኔ ለአንዳንድ ጊዜ ለገዳማዊያን መንፈሳዊ ልምምዶችን ወይም ሱባሄ አጠናክረው ይቀጥሉ ዘንድ መንፈሳዊ አገልግሎት በመስጠት መስበክ ነበረብኝ ፣ በመጨረሻው ቀን በእነዚያ ቀናት እንደተለመደው ሁሉም ወደ ምስጢረ ንስሐ መጡ። አንዲት አዛውንት እህት ወደ እኔ መጡ፣ ግልፅ እይታ የነበራቸው እና ዓይኖቻቸው ግልጽ በሆነ ብርሃን የተሞሉ ነበሩ። የእግዚአብሔር ሰው የነበሩ እማሆይ ነበሩ። ምስጢረ ንስሐ ከመጠናቀቁ በፊት እርሳቸውን አንድ ውለታ ለመጠየቅ ፍላጎት ስለነበረኝ ‘እማሆይ ንስሐ ካደረጉ በኋላ ለኃጢአት ካሳ በሚያደርጉት ጸሎት ውስጥ ለእኔ የምሆን የተወሰነ ጸጋ እንዲለምኑልኝ’ እፈልጋለሁ አልኳቸው። ጌታን ጠይቁልኝ። ጌታን ጠይቁልኝ እርሱ በእውነት ይህንን ጸጋ ይሰጠኛል ’። ለትንሽ ጊዜ በዝምታ ከቆዩ በኋላ እና ጸሎት ካደረጉ በኋላ ከዚያም ወደ እኔ ተመለከቱና ‘ጌታ በእውነት ያንን ጸጋ ይሰጥዎታል ፣ ነገር ግን በዚህ ላይ አይሳሳቱ ፣ እሱ በራሱ መለኮታዊ መንገድ ነው ይህንን ጸጋ የሚሰጦት’ አሉኝ። ጌታ ምንጊዜም የምንለምነውን እንደሚሰጠን ፣ ነገር ግን በመለኮታዊው መንገድ እንደሚያደርግ በመስማቴ ይህ በጣም ጥሩ ነገር እንዲሰማኝ አደረገኝ። ያ መንገድ የመስቀል መንገድን ያካትታል። ይህ በስቃይ ጎዳና በማለፍ ደስታን የመፈለግ ሂደት ሳይሆን፣ ነገር ግን የፍቅር የመጨረሻው ግብ ሊሆን የገባል።

01 April 2021, 22:08