የርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ የሕክምና መገልገያ መሣሪያዎች ዕርዳታ የደረሳቸው ብጹዕ አቡነ ቪታል ኮርቤሊኒ፤ የርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ የሕክምና መገልገያ መሣሪያዎች ዕርዳታ የደረሳቸው ብጹዕ አቡነ ቪታል ኮርቤሊኒ፤  

ር. ሊ. ጳ. ፍራንችስኮስ ለብራዚል የሕክምና መገልገያ መሣሪያዎች ዕርዳታ አደረጉ።

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ በኮቪድ-19 ወረርሽኝ ሕዝቧ በከፍተኛ ጉዳት ውስጥ ለሚገኝባት ብራዚል የሕክምና መገልገያ መሣሪያዎችን ማድረጋቸው ታውቋል። የቅዱስነታቸው ዕርዳታ በብራዚል ገጠራማው አካባቢዎች ለሚኖሩ እና ባሁኑ ጊዜ በወረርሽኙ ክፉኝ በተጎዱት ድሃ ማኅበረሰብ አገልግሎት የሚውል መሆኑ ታውቋል።

የቫቲካን ዜና፤

የደቡብ አሜሪካ አገር በሆነች ብራዚል የኮቪድ-19 ስርጭት ስርጭት በከፍተኛ ፍጥነት እየተስፋፋ በመምጣቱ የተጠቂዎች ቁጥር ከቀን ወደ ቀን እየጨመረ መምጣቱ ታውቋል። ከቅዱስነታቸው የተላኩት የህክምና መገልገያ መሣሪያዎች በብራዚል ከቅድስት መንበር ጽሕፈት ቤት በኩል የደረሳቸው መሆኑን የማራባ ሀገረ ስብከት ጳጳስ ብጹዕ አቡነ ቪታል ኮርቤሊኒ አስታውቀዋል። ብጹዕ አቡነ ቪታል ቅዱስነታቸውን አመስግነው የህክምና አገልግሎት መስጫ መሣሪያውዎቹ የብዙዎችን ሕይወት ከሞት ሊያተርፍ የሚችል መሆኑን አስታውቀዋል። አክለውም ዕርዳታው በሀገረ ስብከታቸው ውስጥ በገጠራማው አካባቢ ለሚኖሩ ማኅበረሰብ የሚደርስ መሆኑን ለቫቲካን ኒውስ አስታውቀዋል።

የር. ሊ. ጳ. ፍራንችስኮስ ስጦታ ናቸው፤

ከርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ የተላኩት የህክምና መገልገያ መሣሪያዎች እሑድ ሐምሌ 5/2012 ዓ. ም. ወደ ሀገረ ስብከታቸው መድረሳቸውን ብጹዕ አቡነ ቪታል አስታውቀው የሕክምና መገልገያ መሣሪያዎቹ ንጹህ አየርን በቀላሉ ለመተንፈስ የሚያግዙ መሆኑን አስረድተው ከእነዚህ መሣሪያዎች በተጨማሪ የሙቀት መለኪያ መሥሪያዎች መኖራቸውን ብጹዕ አቡነ ቪታል ገልጸዋል። መሣሪያዎቹን በሀገረ ስብከታቸው ለሕክምና መገልገያ መሣሪያዎች አስተባባሪ ጽሕፈት ቤት ሰኞ ሐምሌ 6/2012 ዓ. ም. ማስረከባቸውን አስታውቀዋል።         

የር. ሊ. ጳ. ፍራንችስኮስን አለኝታ የሚገልጽ፤

“ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ መብታቸውን ላጡት ዘወትር ይጨነቃሉ” ያሉት ብጹዕ አቡነ ቪታል፣ በብራዚል ገጠራማው አካባቢ ለሚኖርት ሕዝቦች መንግሥት ብዙም ትኩረት የማይሰጣቸው መሆኑን አስረድተዋል። የእነዚህ ሕዝቦች መሬት፣ ደኖች እና ወንዞች ተወርሰዋል ያሉት አቡነ ቪታል፣ በኮቪድ-19 ወረርሽኝ ሲጠቁ መከራቸው የከፋ ስለሚሆን ዕርዳታን ማድረግ እጅግ አስፈላጊ መሆኑን አስረድተዋል። ቅዱስነታቸው የላኳቸው የህክምና መገልገያ መስጫ መሣሪያዎች የበርካታ ሰዎች ሕይወት ከሞት ሊያተርፍ እንደሚችል ብጹዕ አቡነ ቪታል አስረድተዋል። ባሁኑ ጊዜ በሀገረ ስብከታቸው በሚገኝ የአማፓ ግዛት ሆስፒታል ውስጥ ከሚገኙ አልጋዎች ዘጠና አንድ ከመቶ ከፍተኛ ክትትል በሚያስፈልጋቸው የኮቪድ-19 ታማሚዎች የተያዘ መሆኑን በብራዚል የማራባ ሀገረ ስብከት ጳጳስ ብጹዕ አቡነ ቪታል ኮርቤሊኒ ለቫቲካን ኒውስ አስታውቀዋል።

ር. ሊ. ጳ. ፍራንችስኮስ ከዚህ በፊት ለኮቪድ-19 ወረርሽኝ ሕክምና የሚያገለግሉ 35 የመተንፈሻ መሣሪያዎችን ለደቡብ አሜሪካ፣ ለእስያ፣ ለአፍሪካ እና ለአውሮፓ አገሮች ድጋፍ ማድረጋቸው ይታወሳል። የቅዱስነታቸው የዕርዳታ ማስተባባሪያ ሐዋርያዊ ጽሕፈት ቤት እንዳስታወቀው ዕርዳታ የተደረገላቸው አገራት በኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ክፉኛ የተጠቁ መሆናቸውን አስታውቆ ቅዱስነታቸው ካበረከቷቸው 35 የመተንፈሻ አገልግሎት መስጫ መሣሪያዎች መካከል አራቱ ወደ ሃይቲ፣ ሁለቱ ወደ ዶሜኒካን ሪፓብሊክ፣ ሁለቱ ወደ ቦሊቪያ እና አራቱ ወደ ብራዚል፣ የተቀሩት ወደ አፍሪካ እና እስያ አገሮች የተላኩ መሆኑን የቅዱስነታቸው ዕርዳታ ማስተባበሪያ ጽሕፈት ቤት አስታውቋል። የህክምና መገልገያ መሣሪያዎቹ በየአገራቱ በሚገኙ የቅድስት መንበር እንደራሴ ጽሕፈት ቤቶች እና ካቶሊካዊ ብጹዓን ጳጳሳት ጉባኤዎች በኩል ወደ አገራቱ መድረሳቸውን አክሎ አስታውቋል።

15 July 2020, 18:23