ቅዱስ ወንጌል እና የዘመኑ ምልክቶች ቅዱስ ወንጌል እና የዘመኑ ምልክቶች 

ቅዱስ ወንጌል እና የዘመኑ ምልክቶች

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ  እንደገለጹት አሁን ያለውን ጊዜ በቅዱስ ወንጌል እይታ ለመረዳት ቅዱስ ዮሐንስ ጳውሎስ ሁለተኛ እንዳሉት ምንም እንኳን በዛሬው ዘመን የሚኖረው የሰው ልጅ ከዚህ በተቃራኒ የሚያስብ ቢሆንም ቅሉ አሁን ያለንበት ወቅት የምሕረት ወቅት እንደ ሆነ በቅርቡ በተደርገው የመማክርት ጉባሄ ላይ መጥቀሳቸው ይታወሳል።

አቅራቢ መብራቱ ኃ/ጊዮርጊስ ቫቲካን

ይህ ዓመት “የመለኮታዊ ምሕረት ሐዋርያ” የሚል መጠሪያ የተሰጣት ቅድስት ፋውስቲና ኮዋልሲካ የዛሬ 20 ዓመት ገደማ የቅድስና ማዕረግ ያገኘችበት ቀን በሚዘከርበት አመት ሲሆን በላቲን ቋንቋ “Dives in misericordia” በአማርኛው “የምሕረት ባለጸጋ” በሚል አርዕስት የዛሬ 40 አመት ገደማ አንድ ሐዋርያዊ መልእክት ይፋ መሆኑ ይታወቃል፣ በተመሳሳይ መልኩም ይህ ሐዋርያዊ መልእክት በመታሰብ ላይ ይገኛል። የቀድሞ የካቶሊክ ቤተክርስቲያን ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት የነበሩት ቅዱስ ዮሐንስ ጳውሎስ ሁለተኛ ትንቢታዊ በሆነ መልኩ ይህንን የምሕረት መንገድ ተከትለው የተጓዙ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት እንደ ነበሩ የሚታወቅ ሲሆን  የሁለተኛ የቫቲካን ጉባሄ አስተምህሮን በመከተል በዚህ ወሳኝ እና ከባድ በሆነ ወቅት “የአባቱን ፊት የሚገልጸውን የክርስቶስን ፊት በመፈለግ መሐሪ እና አጽናኝ የሆነውን እግዚአብሔርን መፈለግ እንደ ሚገባ” መግለጻቸው ይታወሳል። ብዙ የቤተክርስቲያኗ እና የዘመናችን ተሞክሮዎች የሚጠቁሙት ወደዚህ ምስጢር አሁን መመለሱ የተሻለ መሆኑን ነው፣ የብዙ ሰዎችን ልብ መሻት፣ ስቃዮች እና ተስፋዎች ፣ ጭንቀቶቻቸው እና ፍላጎቶቻቸው መልስ ሊያገኙ የሚችሉት በዚሁ መልክ እንደ ሆነ” መግለጻቸው ይታወሳል።

የዛሬው ዘመን ሰው የእግዚአብሔርን ምሕረት የሚቃወም ይመስላል

ቅዱስ ዮሐንስ ጳውሎስ ዳግማዊ በላቲን ቋንቋ “Dives in misericordia” በአማርኛው “የምሕረት ባለጸጋ”  በተሰኘው ሐዋርያዊ መልእክታቸው ውስጥ እንደ ጠቀሱት ሰው እና ዘመናዊው ዓለም በጣም የሚሹትን “የእግዚአብሔር ምሕረት በይበልጥ እንዲታወቅ ለማድረግ” ቤተክርስቲያኗ የራሷን አስተዋጾ ታደርግ ዘንድ ከፍተኛ የሆነ ተማጽኖ ማቅረባቸው ይታወሳል። የሰው ልጅ እና ዘመናዊው ዓለም የእግዚአብሐርን ምሕረት ብዙን ጊዜ በቅጡ ባይረዱትም እንኳን በውስጣቸው የሚሹት ነገር እንደ ሆነ በዚሁ ሐዋርያዊ መልእክት ውስጥ መጥቀሳቸው የሚታወስ ሲሆን ደግሞም “ባለፈው ዘመን ከነበረው የሰው አስተሳሰብ ይልቅ ፣ አሁን ያለው የሰው ልጅ የማሰብ ችሎታ የላቀ በመሆኑ የተነሳ የምህረት አምላክ የሚቃወም እና ደግሞም ከህይወታቸው እንዲርቅ በማድረግ እና የምህረትን ሀሳብ ከሰው ልብ የማውጣት አዝማሚያ ያለው ነው። የምህረት ቃል እና ፅንሰ-ሀሳብ ለሰው ልጆች የማይመች ይመስላል” ማለታቸው ይታወሳል።

ወቅቱ የምሕረት ወቅት ሊሆን ይገባዋል

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ አሁን ያለንበት ወቅት ከመቸውም ጊዜ በላይ የምሕረት ወቅት መሆን እንደ ሚገባው አበክረው የሚናገሩ ሲሆን ከሁለተኛው የቫቲካን ጉባሄ በኋላ የነበሩት የካቶሊክ ቤተክርስቲያን ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳትን ፈለግ ተክትለው ይህ የምህረት ጊዜ መሆኑን አጥብቀው መናገራቸው ይታወሳል (Misericordia et misera" 2016) በአማርኛው ምሕረት እና ሰቆቃ በተሰኘው ሐዋርያዊ መልእክታቸው ውስጥ እንደ ተጠቀሰው)። የብዙ ሰዎችን ልብ በደስታ በሚሞላው ስሜት የሚገልፅ የምሕረት አዋጅ ሲሆን ነገር ግን በአንዳንድ የቤተክርስቲያኗ ተቋማት ውስጥ እንኳን ሳይቀር ጥርጣሬ እና ግራ የመጋባት ምንፈስ አስከትሏል። ከ 2000 ዓመታት በፊት በቅዱስ ወንጌል ውስጥ በተገለፀው ተመሳሳይ ሁኔታ ውስጥ እናገኘዋለን ። ምህረት እጅግ በጣም ጥሩ የሚባል ቃል ነው፣ እናም ምሕረት ለማያስፈልጋቸው ሰዎች ግን ይህ ቃል ባዶ የሆነ ቃል ነው፣ ፍትህ ለማይገባቸው ሰዎች ምሕረት የሚለው ቃል እርግማን ይሆንባቸዋል፣ በእግዚአብሔር የሚገኝ ፍትህ ግን ያድናል።

“ምህረት የቅዱስ ወንጌል ዋና ማዕከል ነው” ቤኔዲክቶስ 16ኛ 

የቀድሞ የካቶሊክ ቤተክርስቲያን ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት የነበሩት በነዲክቶስ 16ኛ “ምሕረት በእውነቱ የወንጌል መልእክት ማዕከላዊ ምስጢር ነው፣ እሱ በብሉይ ኪዳኑ ውስጥ በተገባው ቃል ኪዳን መሰረት ምሕረት የእግዚአብሔር ስም ነው፣ ምሕረት እግዚአብሔር እኛን የሚመለከትበት ፊት ማለት ነው፣ ይህ ምሕረት በኢየሱስ ክርስቶስ አማካይነት ምልአት ያገኘ እና በፈጣሪ እና በቤዛነት ሙሉ በሙሉ የገለጠ የእግዚአብሔር ስም ነው” ማለታቸው ይታወሳል። ወንጌላዊያን እንደ ሚነግሩን ከሆነ በቀዳሚነት እየሱስን ይቃወሙ የነበሩት የሕግ መምህራን እና ፈሪሳውያን እንደ ነበሩ፣ በወቅቱ በጣም ከሚጠሉ እና ኃጢአተኞች ተብለው ከተፈረጁ ሰዎች ጋር ጌታ ያደርገው የነበረውን ቆይታ ይተቹ እና ይቃወሙ እንደ ነበረ፣ ከተናቁ እና ከተጠሉ ሰዎች ጋር አብሮ እንዳይሄድ ከኃጢአተኞች ጋር ሆኖ ወደ ምህረት መንገድ እንዲያመሩ የሚያደርገውን ሙከራ እንዲያቆም ይወተውቱት እንደ ነበረ፣ ኃጢያተኞችን እየተመለከቱ ከፈሪሳዊያን እና ከሕግ መምህራን አንጻር እነርሱ ራሳቸውን ጻድቅ እንደ ሆኑ አድርገው ይቆጥሩ እንደ ነበረ ቅዱስ ወንጌል በሚገባ ይተነትናል። “እግዚአብሔር ሩኅሩኅ ቸር አምላክ እግዚአብሔር ለቍጣ የዘገየ፣ ፍቅሩና ታማኝነቱ የበዛ፣ ፍቅርን ለሺዎች የሚጠብቅ፣ ክፋትን፣ ዐመፅንና ኀጢአትን ይቅር የሚል” (ዘፀአት 34፡6) በማለት እግዚአብሔር ለሰው ልጆች ምን ያህል ቅርብ እንደ ሆነ ይገልጽልናል። ነገር ግን እነርሱ በኃጢአተኞች ላይ እንደሚፈርድ እና ኃጢያተኞችን እንደሚቀጣ አድርገው እግዚአብሔርን ይመለከቱ ስለነበረ ኢየሱስ ከኃጢተኞች ጋር የነበረውን ቆይታ በሕግ አግባብ ብቻ በመመልከት ኢየሱስ ሕጋቸውን መተላለፉን በመጥቀስ ይዘልፉት እና አልፎ ተርፎም ኢየሱስ ጋኔን እንዳለበት አድርገው ይቆጥሩ እንደ ነበረ ከቅዱስ ወንጌል ለመረዳት የሚችላ ሲሆን ይህንን ሐስተሳሰባቸውን እና ቁጣቸውን በቀላሉ ለመረዳት ይቻላል፣ እነርሱ ይህንን ያደርጉት የነበረው እነርሱ ራሳቸውን ጻድቃን እንደ ሆኑ አድርገው ስለሚቆጥሩ ከፍተኛ የሆነ ተስፋ ስለነበራቸው ነው። እነሱ እግዚአብሔርን እየተከላከሉ እንደ ሆነ ሁኖ ይሰማቸዋል፣ እግዚአብሔር ግን ጠንከር ባለ ቃላት እርማት ይሰጣቸዋል።

ኢየሱስ ለሕግ መምህራን እና ለፈሪሳውያን የሰጠው ጠንካራ ማስጠንቀቂያ

ኢየሱስ ለሕገ መምህራን እና ለፈሪሳዊያን በታላቅ ቁጣ ከተናገራቸው ሰባት በጣም ከባድ ከሆኑት ቃላት መካከል በቀዳሚነት የሚጠቀሰውን እና በማቴዎስ ወንጌል ውስጥ የተጠቀሰውን በቀዳሚነት እንመልከት፣

“እናንተ ግብዞች የኦሪት ሕግ መምህራንና ፈሪሳውያን፤ ሰዎች ወደ መንግሥተ ሰማይ እንዳይገቡ በሰዎች ላይ በሩን ስለ ምትዘጉባቸው ወዮላችሁ! እናንተ ራሳችሁ አትገቡም፤ መግባት የሚፈልጉትንም አታስገቡም። እናንተ ግብዞች የኦሪት ሕግ መምህራንና ፈሪሳውያን፤ ወዮላችሁ የመበለቶችን ቤት እያራቈታችሁ፣ ለሰው ይምሰል ረዥም ጸሎት ስለምታደርጉ የከፋ ፍርድ ትቀበላላችሁ። “እናንተ ግብዞች የኦሪት ሕግ መምህራንና ፈሪሳውያን፤ አንድን ሰው ወደ አይሁድ ሃይማኖት ለማስገባት በባሕርና በየብስ ስለምትጓዙ፣ ባመነም ጊዜ ከእናንተ በእጥፍ የባሰ የገሃነም ልጅ ስለምታደርጉት ወዮላችሁ።

“እናንተ ዕውር መሪዎች፤ ወዮላችሁ! ‘ማንም በቤተ መቅደስ ቢምል ምንም አይደለም፤ ነገር ግን በቤተ መቅደሱ ውስጥ ባለው ወርቅ ቢምል መሐላው ይደርስበታል’ ትላላችሁ። እናንተ የታወራችሁ ተላላዎች! ከወርቁና ወርቁን ከቀደሰው ቤተ መቅደስ የቱ ይበልጣል? እንዲሁም፣ ‘ማንም በመሠዊያው ቢምል ምንም አይደለም፤ ነገር ግን በላዩ ላይ ባለው መባ ቢምል መሐላው ይደርስበታል’ ትላላችሁ፤ እናንተ ዕውሮች፤ ከመባውና መባውን ከቀደሰው መሠዊያ የቱ ይበልጣል? ስለዚህ፣ በመሠዊያው የማለ፣ በመሠዊያውና በላዩ ላይ ባለው ሁሉ ይምላል። እንዲሁም በቤተ መቅደሱ የማለ፣ በቤተ መቅደሱና በውስጡ በሚያድረው ይምላል። በሰማይ የማለም በእግዚአብሔር ዙፋንና በዙፋኑ ላይ በተቀመጠው ይምላል።

“እናንት ግብዞች የኦሪት ሕግ መምህራንና ፈሪሳውያን፤ ወዮላችሁ! ከአዝሙድ፣ ከእንስላልና ከከሙን ዐሥራት እየሰጣችሁ በሕጉ ውስጥ ዋነኛ የሆኑትን ማለትም ፍትሕን፣ ምሕረትንና ታማኝነትን ግን ንቃችኋልና፤ እነዚያን ሳትተዉ እነዚህን ማድረግ በተገባችሁ ነበር፤ እናንት የታወራችሁ መሪዎች፤ ትንኝን አጥርታችሁ ትጥላላችሁ፤ ግመልን ግን ትውጣላችሁ።

“እናንተ ግብዞች የኦሪት ሕግ መምህራንና ፈሪሳውያን፤ ወዮላችሁ! የጽዋውንና የወጭቱን ውጭ ትወለውላላችሁ፤ በውስጣቸው ግን ቅሚያና ስስት ሞልቶባቸዋል። አንተ ዕውር ፈሪሳዊ አስቀድመህ የጽዋውንና የወጭቱን ውስጥ አጽዳ፤ ከዚያም ውጭው የጸዳ ይሆናል። “እናንት ግብዞች የኦሪት ሕግ መምህራንና ፈሪሳውያን፤ ውጫቸው በኖራ ተለስነው የሚያምሩ፣ ውስጣቸው ግን በሙታን ዐፅምና በብዙ ርኵሰት የተሞላ መቃብሮችን ስለምትመስሉ ወዮላችሁ! እናንተም በውጭ ለሰዎች ጻድቃን ትመስላላችሁ፤ ውስጣችሁ ግን በግብዝነትና በክፋት የተሞላ ነው።

“እናንተ ግብዞች የኦሪት ሕግ መምህራንና ፈሪሳውያን፤ ወዮላችሁ! የነቢያትን መቃብር እየገነባችሁ፣ የጻድቃንንም ሐውልት እያስጌጣችሁ፣ ‘በአባቶቻችን ዘመን ብንኖር ኖሮ፣ የነቢያትን ደም በማፍሰስ አንተባበራቸውም ነበር’ ትላላችሁና። በዚህም የነቢያት ገዳዮች ለነበሩት አባቶቻችሁ ልጆች መሆናችሁን በራሳችሁ ላይ ትመሰክራላችሁ። እንግዲህ የአባቶቻችሁን ጅምር ተግባር ከፍጻሜ አድርሱ! “እናንተ እባቦች፤ የእፉኝት ልጆች! ከገሃነም ፍርድ እንዴት ልታመልጡ ትችላላችሁ” (ማቴዎስ 23፡13-33)

የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት ባሕል በመተላለፋቸው የተነሳ ይከሰሱ ነበር

የሕግ መምህራን እና ፈሪሳውያን የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት ባሕላቸውን ለምን እንደ ተላለፉ በጠየቁበት ወቅት. . .

ኢየሱስም እንዲህ ሲል መለሰላቸው፤ “እናንተስ ለወጋችሁ ስትሉ የእግዚአብሔርን ትእዛዝ ለምን ትሽራላችሁ? እግዚአብሔር፣ ‘አባትህንና እናትህን አክብር፤ በአባቱ ወይም በእናቱ ላይ ክፉ ቃል የሚናገር ይገደል’ ብሎ ሲያዝ፣ እናንተ ግን፣ ማንም ሰው አባቱን ወይም እናቱን፣ ‘ላደርግላችሁ የሚገባውን ማንኛውንም ነገር ለእግዚአብሔር መባ አድርጌ አቅርቤአለሁ’ ቢላቸው፣‘አንድ ሰው ይህን ካደረገ ዘንድ አባቱን ወይም እናቱን አክብሮአል’ ትላላችሁ። ስለዚህ ለወጋችሁ ብላችሁ የእግዚአብሔርን ቃል ትሽራላችሁ። እናንት ግብዞች፤ ኢሳይያስ ስለ እናንተ እንዲህ ብሎ በትንቢት የተናገረው ትክክል ነው፤ “ ‘ይህ ሕዝብ በከንፈሩ ያከብረኛል፤ ልቡ ግን ከእኔ የራቀ ነው፤ በከንቱ ያመልኩኛል፣ትምህርታቸውም የሰው ሥርዓት ነው’ ” (ማቴ 15፡3-9) በማለት ይመልስላቸዋል።

 

"ምህረትን እንጂ ምስዋዕትን አልፈልግም”

በዚያን ጊዜ ​​በርካታ የሃይማኖት መመሪያዎች ተከማችተው በዝርዝር ተቀምጠው የነበሩ ሲሆን እነዚህ ሃይማኖታዊ መመሪያዎች ደህንነትን ሊያስገኙ ይችሉ ነበር፣ ነገር ግን መሠረታዊ የሆኑ ነገሮች ይጎሏቸዋል። ከቀረጥ ሰብሳቢዎች እና ከኃጢአተኞች ጋር በመብላቱ የተነሳ በፈሪስዊያን ሲወነጀል “ኢየሱስም የተናገሩትን ሰምቶ እንዲህ አላቸው፤ “ሐኪም የሚያስፈልገው ለሕመምተኞች እንጂ ለጤነኞች አይደለም፤ ሄዳችሁ፣ ‘ከመሥዋዕት ይልቅ ምሕረትን እወዳለሁ፤’ የሚለውን ቃል ትርጕም አጢኑ፤ ኀጢአተኞችን እንጂ ጻድቃንን ልጠራ አልመጣሁምና” (ማቴ 9፡12-13) በማለት መልሶላቸው ነበር።

የክርስቲያን ማንነት

ፈሪሳውያኑ የተደበቀ አጀንዳቸውን ለመፈጸም ይህንን ድብቅ ሴራ እውን ለማደረግ ፈልገው እና ኢየሱስን ለማጥመድ እና ለማጥፋት አስበው የተለያዩ ጥያቄዎችን ይጠይቁት ነበር። አንዳንድ ጊዜ ቀለል ያሉ ፈተናዎችን በማቀረብ የፈታተኑታል። ከእነርስ አንዱ  የሕግ መምህር የሆነው ወደ ኢየሱስ ቀርቦ “ከሁሉም የሚበልጠው ትልቁ ትእዛዝ የተኛው ነው” በማለት ኢየሱስን በጠየቀ ጊዜ የክርስትና እምነት መሠረታዊ ነገር ልግስና መሆኑን በግልፅ በመናገር እንዲህ ብሎ ይመልሳል . . .

‘ጌታ አምላክህን በፍጹም ልብህ፣ በፍጹም ነፍስህ፣ በፍጹም ሐሳብህ ውደድ፤’ ይህ የመጀመሪያውና ከሁሉ የሚበልጠው ትእዛዝ ነው፤ ሁለተኛውም ያንኑ ይመስላል፤ ይህም፣ ‘ጎረቤትህን እንደ ራስህ ውደድ’ የሚለው ነው፤ ሕግና ነቢያት በሙሉ በእነዚህ ሁለት ትእዛዛት ላይ የተንጠለጠሉ ናቸው”(ማቴዎስ 22፡37-40)

የመጨረሻ ፍርድ ጥያቄዎች

በመጨረሻው ቀን ፍርድ ላይ የምንዳኘው እና የመጨረሻው የፍርድ ሂደት ምርመራ የሚቀርብልን ጥያቄ በምሕረት እና በፍቅር ሥራዎች ላይ መሰረታቸውን ያደረጉ ጥያቄዎች እንደ ሆኑ እናውቃለን።

የሰው ልጅ ከመላአክቱ ሁሉ ጋር በክብሩ ሲመጣ፣ በክብሩ ዙፋን ላይ ይቀመጣል፤ ሕዝቦች ሁሉ በፊቱ ይሰበሰባሉ፤ እርሱም፣ እረኛ በጎችን ከፍየሎች እንደሚለይ፣ ሕዝቡን አንዱን ከሌላው ይለያል፤ በጎቹን በቀኙ፣ ፍየሎቹን ግን በግራው ያቆማቸዋል። “በዚያን ጊዜ ንጉሡ በቀኙ በኩል ያሉትን እንዲህ ይላቸዋል፤ ‘እናንት አባቴ የባረካችሁ ኑ፤ ዓለም ከተፈጠረ ጀምሮ የተዘጋጀላችሁን መንግሥት ውረሱ፤ ምክንያቱም ተርቤ አብልታችሁኛል፤ ተጠምቼ አጠጥታችሁኛል፤ እንግዳ ሆኜ ተቀብላችሁኛል፤ ታርዤ አልብሳችሁኛል፤ ታምሜ አስታምማችሁኛል፤ ታስሬ ጠይቃችሁኛል’ (ማቴ 25፡31-36)።

ለጎረቤቶቻችን የምሕረት ምሳሌዎችን ማሳየት

እኛን ከሚገጥሙን ፈተናዎች መካከል በቀዳሚነት የሚገለጸው ኢየሱስን በግል እቅዶቻችን ውስጥ አስሮ ለማስቀመጥ የሚደርገው ሙከራ ሲሆን ነገር ግን እሱ በደጉ ሳምራዊ ምሳሌ አማካይነት እንዳስታውሰን (ሉቃ 25 ፣ 10-37) አንድ በጎ ተግባር ስለፈጸመ አንድ ሳምርዊ ሰው ምሳሌ በመጥቀስ ጉዳዩን በግድዬለሽነት ከተመለከቱት ከካህኑ እና ሌዋዊው ከነበረ ሰው በተቃራኒ በኩል የሚገኘው ደጉ ሳምራዊ ያደርገውን ዓይነት መልካም ተግባር እኛም እንድናከናውን በማሳሰብ ኢየሱስን በራሳችን እቅዶች ውስጥ ብቻ ቆልፈን ከመያዝ ባሻገር መጓዝ እንደ ሚኖርብን ያስታውሰናል። በሌላ በኩል ደግሞ ሳምራዊው ሰው ሩህሩህ የነበረ ሰው ሲሆን ቆም ብሎ በመመልከት በወንበዴዎች የተደበደበውን ሰው ሲንከባከብ እንመለከታለን። የእግዚአብሔር ፍርድ ከእኛ ፍርዶች የተለየ ነው። ኢየሱስ ከተናገራቸው ቃላት መካከል ለእራሳቸው ሳይሆን ለሴት ልጁ እና ለአገልጋዩ  ፈውስ ለጠየቁ ሁለት ሰዎች የተናገራቸው ቃላት ናቸው። እነዚህ ሁለት ሰዎች በግልጽ እንደ ሚታየው ከሩቅ ሁነው ይህንን ጥያቄ ለኢየሱስ ማቅረባቸው የሚታወስ ሲሆን ኢየሱስ የነዓናዊቷ ሴት እምነት ተመልክቶ “አንቺ ሴት እምነትሽ ታላቅ ነው እንደ ፈለግሽው ይሁንልሽ” አላት። ልጇም ከዚያ ሰዓት ጀምሮ ተፈወሰች” (ማቴ 15፡28) በማለት የልቧን መሻት ይፈጽማል። በመቀጠልም ኢየሱስም የመቶ አለቃው በሰጠው መልስ ተደንቆ ይከተሉት ለነበሩት እንዲህ አላቸው፤ “እውነት እላችኋለሁ፣ ከእስራኤል መካከል እንኳ እንዲህ ያለ እምነት ያለው አንድ ሰው አላገኘሁም [. . .] ኢየሱስም መቶ አለቃውን፣ “ሂድ እንደ እምነትህ ይሁንልህ” አለው። አገልጋዩም በዚያች ቅጽበት ተፈወሰ (ማቴ 8፡10፣ 13)።  ፍቅር ማንኛውንም መሰናክል ወይም መለያየት ያሸንፋል።

መንፈሳዊ ለውጥ ለማምጣት ትህትና ያስፈልጋል

ፈሪሳዊ መባል የሚፈልግ ማንም ሰው የለም። ነገር ግን በእያንዳንዳችን ውስጥ በባልንጀሮቻችን ላይ እንድንፈርድ የሚያደርገን እና ከሌሎች እደተሻልን ሁነን እንዲሰማን የሚያደርገን “የሕግ መምህር” መንፈስ በውስጣችን ይገኛል (ሉቃስ 18፡ 9-14)፣ ከዚህ ዓይነቱ ተግባር ለመውጣት መታረም ይኖርብናል። ከዚህ ዓይነቱ ተግባር ለመውጣት አንዳንዴ ጠንከር ያለ መናወጥ ሊደርስብን ይችላል። ለሁላችንም ኢየሱስ እንዲህ ብሏል “ጽድቃችሁ ከፈሪሳውያንና ከኦሪት ሕግ መምህራን ጽድቅ ልቆ ካልተገኘ መንግሥተ ሰማይ መግባት አትችሉም” (ማቴ 5፡20)። የኢየሱስ ፍትህ ጠላትን በመውደድ የሚገኝ ምሕረት ነው። የኢየሱስ ፍትህ ያዳናል።

የዘመኑ ምልክቶችን ያንብቡ

እርሱ መቼ እንደ ሚመጣ ለማወቅ እንችል ዘንድ መለየት እንድንችል የዘመኑን ምልክቶች እንድናነብ በወንጌል ውስጥ ጌታ ይጋብዘናል (ሉቃ 12፡ 54-59)። ከመጨረሻው የቤተክርስቲያኗ ጉባሄ በኋላ ቤተክርስቲያኗ የእግዚአብሔርን ምህረት እውነት በመረዳት ጉዞዋን ቀጥላለች፣ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ ቅዱስ ዮሐንስ ጳውሎስ ዳግማዊ አብነት በመከተል እንደ ገለጹት “ከእግዚአብሔር ምሕረት የተሻለ ለሰው ልጆች ሌላ የተስፋ ምንጭ በፍጹም ሊኖር አይችልም” በማለት መናገራቸው ይታወሳል።

10 July 2020, 18:11