ር.ሊ.ጳ ፍራንቸስኮስ በሞዛንቢክ፣ በማዳጋስካር እና በሞሪሼስ ሐዋርያዊ ጉብኝት እንደ ሚያደርጉ ተገለጸ። ር.ሊ.ጳ ፍራንቸስኮስ በሞዛንቢክ፣ በማዳጋስካር እና በሞሪሼስ ሐዋርያዊ ጉብኝት እንደ ሚያደርጉ ተገለጸ። 

ር.ሊ.ጳ ፍራንቸስኮስ በሞዛንቢክ፣ በማዳጋስካር እና በሞሪሼስ ሐዋርያዊ ጉብኝት እንደ ሚያደርጉ ተገለጸ

እ.አ.አ ከመጪው መስከረም 4-10/2019 ዓ.ም ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ 31ኛውን ሐዋርያዊ ጉብኝት በሞዛንቢክ፣ በማዳጋስካር እና በሞሪሼስ በቀድም ተከተል እንደ ሚያደርጉ ከቫቲካን ከደረሰን ዘገባ ለመረዳት የተቻለ ሲሆን ይህ ቅዱስነታቸው እ.አ.አ ከመጪው መስከረም 4-10/2019 ዓ.ም በሞዛንቢክ፣ በማዳጋስካር እና በሞሪሼስ በቅደም ተከተል የሚያደርጉት 31ኛው ሐዋርያዊ ጉብኝት ቅዱስነታቸው የካቶሊክ ቤተክርስቲያን ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ሆነው ከተመረጡ በኋላ በአፍሪካ አእጉር የሚያደርጉት አራተኛው ሐዋርያዊ ጉብኝት ሲሆን ከእዚህ ቀደም እ.አ.አ በ2015 ዓ.ም ኬኒያን፣ ሁጋንዳ እና በመካከለኛው አፍሪካ ሪፖብሊክ ሐዋርያዊ ጉብኝት ማደረጋቸው ይታወሳል።

የእዚህ ዜና አቅራቢ መብራቱ ኃ/ጊዮርጊስ-ቫቲካን

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ ከታኅሳስ 01/2008 ዓ.ም. እስከ ኅዳር 11/2009 ዓ.ም. ደርስ ለ349 ቀናት ያህል የቆዬው ልዩ ቅዱስ የምሕረት አመት ኢዩቤልዩ ያወጁት ከእዚያው በመካከለኛው አፍሪካ ሪፖብሊክ እንደ ነበረ የሚታወስ ሲሆን ይህንን ልዩ ቅዱስ የምሕረት ዓመት ያወጁት በወቅቱ በክርስቲያኖች እና በእስልምና እምነት ተከታዮች መካከል በመካከለኛው የአፍሪካ ሪፖብሊክ በተነሳው የእርስ በእርስ ግጭት ተጎሳቁላ በነበረች ሀገር በመገኘት የሁለቱንም የሐይማኖት ተቋማት ተወካዮች በአንድነት ፊት ለፊት አቀራርበው በማነጋገር እርቅ እንዲፈጥሩ መንገዱን በመክፈት በእዚያው በመካከለኛው የአፍሪካ ሪፖብልክ በባንጉዊ ከተማ በሚገኘው የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ካቴድራል ተገኝተው ልዩ ቅዱስ የምሕረት አመት ኢዩቤሊዪን ማስጀመራቸው የሚታወስ ሲሆን በእነዚህም 349 ቀናት ውስጥ ምዕመናን  መንፈሳዊ እና አካላዊ የምሕረት ተግባራት የሚፈጸሙበት ወቅት መሆኑን ገልጸው፣ በእዚህ ልዩ ቅዱስ የምሕረት አመት ክርስቲያኖች እርቅን እና ሰላምን ይፈጥሩ ዘንድ ማሳሰባቸው ይታወሳል።

ቅዱስነታቸው በወቅቱ በመካከለኛው አፍሪካ ሪፖብሊክ በነበራቸው ቆይታ ይህንን ሰላም የማውረድ ጥረታቸውን በመቀጠል በባንጉዊ በሚገኘው መስጊድ ውስጥ ተገኝተው የሚከተለውን ንግግር አድርገው ነበር፡

“እኛ ክርስቲያኖች እና እናንተ የእስልምና እምነት ተከታይ የሆናችሁ ሁላችሁ እኛ ወንድማማቾች ነን። ስለዚህ እራሳችንን እንደዚህ አድርገን በመቁጠር በዚህ አግባብ መኖር ይኖርብናል። በቅርቡ በአገራችሁ ውስጥ የተከሰቱት አሰቃቂ ክስተቶች እና ግጭቶች በሃይማኖት ምክንያት የተከሰቱ ችግሮች እንዳልሆኑ በሚገባ እንገነዘባለን። በአምላክ አምናለሁ የሚል ማነኛውም ሰው የሰላም ሰው መሆን ይኖርበታል። በአገራችሁ ክርስቲያኖች፣ ሙስሊሞች እና ባህላዊ የሆኑ እምነቶችን የሚከተሉ ሕዝቦች ሁሉ ለብዙ አመታት በሰላም አብረው ኖረዋል” በማለት መናገራቸው ይታወሳል።

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ እ.አ.አ በ2017 ዓ.ም በግብጽ እና በሞሮኮ በቀድም ተከተል ሐዋርያዊ ጉብኝት ማደረጋቸው የሚታወስ ሲሆን በግብፅ በነበራቸው ቆይታ ከታላቁ የአላዓዛር ኢማም የእስልምና መዕከል የበላይ አለቃ ከሆኑት ከሼክ አህመድ አል ጣይብ እና እንዲሁም የግብፅ ፕሬዚዳንት ከሆኑት አብደል ፋታህ ኣል አዚዝ ጋር ተገናኝተው በተለያዩ ጉዳዮች ላይ መምከራቸው ይታወሳል።

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ እ.አ.አ በሚያዚያ ወር 2017 ዓ.ም በግብፅ ሐዋርያዊ ጉብኝት ባደረጉበት ወቅት በወቅቱ የአልዓዛር ታላቁ መስጊድ እና ዮኒቬርሲቲ ታላቁ ኢማም ከሆኑት አህመድ ሙሀመድ ኣል ታይብ ጋር በተገናኙበት ወቅት የሚከተለውን ንግግር አድረገው ነበር . . .

“የሃይማኖት ተቋማት መሪዎች እንደመሆናችን መጠን ማነኛውንም ዓይነት ቅድስናን የሚያጎድፉ ብጥብጦችን እና ግጭቶችን፣ የኋጢኣት ሁሉ መንስሄ የሆነውን የራስ ወዳድነት መንፈስን በማውገዝ እውነተኛ የሆኑ የውይይት መድረኮችን መክፈት ይኖርብናል። በሰው ልጆች ክብር እና ሰብአዊ መብት ላይ የተፈጸሙ ጥሰቶችን ለማውገዝ፣ በሐይማኖት ተቋማት ውስጥ ጥላቻዎችን በመፍጠር፣ እነዚህን ጥላቻዎች በሐይማኖትና በእግዚኣብሔር  ስም እውነተኛ እንደሆኑ አስመስሎ ለማቅረብ የሚደርጉትን ጥረቶች በሙሉ ለማጋለጥ እና እነዚህን ጉዳዮች የእውነተኛው አምላክ ፍላጎቶች ሳይሆኑ ነገር ግን የጣዖት አምላክ ፍላጎቶች መሆናቸውን በማሳወቅ፣ የእውነተኛው እግዚኣብሔር ስም ቅዱስ፣ እርሱ የሰላም አምላክ፣ እግዚኣብሔር ሰላም መሆኑን በድፍረት መመስከር ይኖርብናል። ስለዚህ የተቀደሰ ነገር የሚባለው ሰላም ብቻ ነው፣ ስለሆነም በእግዚአብሔር ስም ምንም ዓይነት ግፍ፣ ብጥብጥ፣ ግጭት ሊፈጸም አይችልም፣ ምክንያቱም በእግዚኣብሔር ስም የሚፈጸሙ ግፎች ቅዱሱን የእግዚኣብሔር ስም ያረክሱታልና” በማለት መናገራቸው ይታወሳል።

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ ከመጋቢት 21-22/2011 ዓ.ም ድረስ “የእግዚኣብሔር አገልጋዮች አገልጋይ” በሚል መሪ ቃል በሞሮኮ ዋና ከተማ በራባት 28ኛውን ሐዋርያዊ ጉብኝት ማድረጋቸው የሚታወስ ሲሆን በእዚያው በነበራቸው ቆይታ ካሪታስ በመባል በሚታወቀው የካቶሊክ ቤተክርስቲያን የእርዳታ መስጫ ተቋም ሥር በሚተዳደረው የስደተኞች መኖሪያ ማዕከል ውስጥ ተገኝተው ባደርጉት ንግግር ቅዱስነታቸው እንደ ገለጹት “እናንተ አልተገለላችሁም፣ እናንተ አሁንም ቢሆን የቤተ ክርስቲያን ልብ ማዕከል ውስጥ ትገኛላችሁ” ማለታቸው ይታወሳል።

እ.አ.አ ከመጪው መስከረም 4-10/2019 ዓ.ም ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ በሞዛንቢክ፣ በማዳጋስካር እና በሞሪሺዬስ በቀድም ተከተል በሚያደርጉት ሐዋሪያዊ ጉብኝት 15 ያህል የተለያዩ ንግግሮችን እንደ ሚያደርጉ ከወዲሁ የተገለጸ ሲሆን ከአገራቱ ርዕሳነ ብሔራት፣ ከሲቪክ ማኅበርሰቡ እና ከቄሳውስት ጋር ተገናኝተው እንደ ሚወያዩ የተገለጸ ሲሆን የሞዛንቢክ ዋና ከተማ በሆነችው በማፑቶ እና በማዳጋስካር ዋና ከተማ ውስጥ የሚገኙትን በካቶሊክ ቤተክርስቲያን ጥላ ሥር የሚተዳደሩትን ሁለት ሆስፒታሎች እንደ ሚጎበኙ እና በእዚያው ሥፋር ጸሎት እንደ ሚያደርጉም ይጠበቃል።

በሞዛንቢክ የምትገኘው የካቶሊክ ቤተክርስቲያን እ.አ.አ በ14ኛው እና በ16ኛው ክፍለ ዘመን የተመሰረተች ጥናታዊ ቤተክርስቲያን እንደ ሆነች ከደረሰን ዘገባ ለመረዳት የተቻለ ሲሆን የዶሜኒካን፣ የኢየሱሳዊያን እና የላዛሪስት ማኅበር አባላት የተመሰረተች ቤተክርስቲያን ናት። የሞዛንቢክ ሕዝብ ብዛት 31 ሚልዮን የሚጠጋ ሲሆን ከአጠቃላይ የአገሪቷ ሕዝብ ውስጥ 6 ሚልዮን፣ በመቶኛ ሲሰላ 28 % የካቶሊክ ቤተክርስቲያን እምነት ተከታይ እንደ ሆነ፣ በሞዛንቢክ የእስልምና እምነት ተከታዮች እና እንዲሁም የፕሮቴስታን እምነት ተከታይ የሆኑ ምዕመናን እንደ ሚገኙም ተገልጹዋል።

በሞዛንቢክ የምትገኘው የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን በአገሪቷ በከፍተኛ ሁኔታ የሚንጸባረቀውን ሙስና፣ ድህነት እና የሰብዓዊ መብት ጥሰት ይወገድ ዘንድ ከፍተኛ በሚባል ደረጃ አስተዋጾ በማደረግ ላይ እንደ ምትገኝ የሚታወቅ ሲሆን ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ እ.አ.አ በመጪው መስከረም 5-6/2019 ዓ.ም በሞዛንቢክ ሐዋርያዊ ጉብኝት እንደ ሚያደርጉም ተገልጹዋል።

እ.አ.አ. በመጪው መስከረም 6-8/2019 ዓ.ም ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ ወደ ማዳካስካር በማቅናት በእዚያው ከአገሪቷ ባለስልጣናት፣ የሲቪክ ማኅበርሰብ ተወካዮች እና ከቄሳውስት እና ደናግላን ጋር እንደ ሚገናኙ የተገለጸ ሲሆን 25 ሚልዮን ከሚሆነው የማዳጋስካት አጠቃላይ ሕዝብ ውስጥ 8 ሚልዮን የሚሆነው ሕዝብ የካቶሊክ ቤተክርስቲያን እምነት ተከታይ ሲሆን በጠቃላይ በማዳጋስካር 58 % የሚሆነው ሕዝብ የክርስትና እምነት ተከታይ ነው። በአገሪቷ በርካታ የባሕላዊ እምነት ተከታይ ሕዝቦች እንደ ሚገኙም ለመረዳት ተችሉዋል።

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ ከእዚያም በመቀጠል እ.አ.አ በመስከረም 9/2019 ዓ.ም ወደ ሞሪሼስ በማቅናት ተመሳሳይ የሆነ ሐዋርያዊ ጉብኝት እንደ ሚያደርጉም ለቅዱስነታቸው ከወጣው የጉዞ መረሃ ግብር ለመረዳት የተቻለ ሲሆን የአገሪቷ አጠቃላይ የሕዝብ ብዛት 1,271, 445 ሚልዮን ሕዝብ ብዛት ያላት አገር ስትሆን የአገሪቷ ብዙሃን ሕዝብ የክርስቲያን እምነት ተከታይ ሲሆን ከአጠቃላይ የሕዝብ ብዛቷ ውስጥ 28% የካቶሊክ ቤተክርስቲያን እምነት ተከታይ ነው፣ የቡዳ እምነት ተከታዮች እና እንዲሁም ከአገሪቷ አጠቃላይ ሕዝብ ውስጥ 5% የሚሆኑት ደግሞ የእስልምና እምነት ተከታይ እንደ ሆኑ ከደርሰን ዘገባ ለመረዳት ተችሉዋል። የቀድሞ የካቶሊክ ቤተክርስቲያን ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት የነበሩት ዮሐንስ ጳውሎስ ዳግማዊ እ.አ.አ. በ1988 እና በ1999 ዓ.ም በሞዛንቢክ፣ በማዳጋስካር እና በሞሪሼስ ሐዋርያዊ ጉብኝት ማደረጋቸው ይታወሳል።

10 July 2019, 13:31