የእሳት አደጋውን በቁጥጥር ስር ለማዋል ጥረት ሲደረግ፣ የእሳት አደጋውን በቁጥጥር ስር ለማዋል ጥረት ሲደረግ፣  

ር. ሊ. ጳ ፍራንችስኮስ በኖተር ዳም ካቴድራል የእሳት ቃጠሎ አደጋ የተሰማቸውን ሐዘን ገለጹ።

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ በፈረንሳይ ፓሪስ ከተማ በሚገኝ ኖትር ዳም እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ካቴድራል ላይ በደረሰው የእሳት ቃጠሎ አደጋ የተሰማቸውን ሐዘን ገልጸው ከአገሩ ካቶሊካዊ ምዕመናን ጋር የሐዘናቸው ተካፋይ መሆናቸውን እና በጸሎታቸው ማስታወሳቸውን ገልጸዋል። ትናንት ሰኞ ሚያዝያ 7/2011 ዓ. ም. በፈረንሳይ ዋና ከተማ በፓሪስ የሚገኘው የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ካቴድራ በእሳት አደጋ መጎዳቱን የቫቲካን የዜና አገልግሎት አስታውቋል።

የዚህ ዝግጅት አቅራቢ ዮሐንስ መኰንን - ቫቲካን

የቅድስት መንበር ጋዜጣዊ መግለጫ ክፍል ጊዜያዊ ዳይሬክተር የሆኑት አቶ አሌሳንድሮ ጂሶቲ ባሰሙት አጭር ጋዜጣዊ መግለጫ ካቴድራሉ በአደጋው መጎዳቱ ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስን እንዳሳዘናቸው እና አደጋውን ለመቆጣጠር በሥፍራው የተገኙ የእሳት አደጋ ተቆጣጣሪዎችን ቅዱስነታቸው በጸሎታቸው እንዳስታወሷቸው አስታውቀዋል።

አቶ አሌሳንድሮ ጂሶቲ ከርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ የተላከውን የሐዘን መግለጫ መልዕክትን በመጥቀስ እንደተናገሩት የፓሪስ ኖተር ዳም ካቴድራል ለፈረንሳይ ምዕመናን እና ለዓለም የክርስትና እምነትም ምልክት ሆኖ የቆየ መሆኑን አስታውቀዋል። ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ ከፈረንሳይ ካቶሊካዊ ማሕበረሰብ እና ከአገሩ ሕዝብ ጎን በመሆን በጸሎት እንደሚተባበሯቸው እና የእሳት አደጋውን ለመቆጣጣር የበኩላቸውን ጥረት ያደረጉትን እና በማድረግ ላይ የሚገኙትን በጸሎታቸው ያስታወሱ መሆናቸውን አስታውቀዋል።           

16 April 2019, 17:14