ር.ሊ.ጳ. ፍራንቸስኮስ ዓለማቀፍ የቅዱስ ቁርባን ጉባሄ ማብቂያ ላይ ር.ሊ.ጳ. ፍራንቸስኮስ ዓለማቀፍ የቅዱስ ቁርባን ጉባሄ ማብቂያ ላይ 

ር.ሊ.ጳ. ፍራንቸስኮስ “በማኅበረሰባችን ውስጥ የቅዱስ ቁርባን ባህል ማስረጽ ይኖርብናል!”

በቫቲካን በመካሄድ ላይ የነበረው ዓለማቀፍ የቅዱስ ቁርባን ጳጳሳዊ ኮሚቴ ያዘጋጀው ጠቅላላ ስብሰባ በሕዳር 01/2011 ዓ.ም መጠናቀቁ ይታወሳል። በዚህ ዓለማቀፍ የቅዱስ ቁርባን ጉባሄ ማብቂያ ላይ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ ተገኝተው ንግግር ማድረጋቸውን በተለይ ለቫቲካን ዜና ከደረሰን ዘገባ ለመረዳት የተቻለ ሲሆን “በማኅበረሰባችን ውስጥ የቅዱስ ቁርባን ባህል ማስረጽ ይኖርብናል!” ማለታቸውን ለመረዳት ተችሉዋል።

የዚህ ዜና አቅራቢ መብራቱ ኃ/ጊዮርጊስ-ቫቲካን

ክቡራን እና ክቡራት የዝግጅቶቻችን ተከታታዮች ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ በወቅቱ ያደረጉትን ንግግር ሙሉ ይዘት እንደ ሚከተለው ተርጉመነዋል እንድትከታተሉን እንጋብዛለን።

የተከበራችሁ ወንድሞቼ ጳጳሳት እና ካህናት

ውድ ወንድሞቼ እና እህቶቼ

በዚህ ስብሰባ ማጠቃለያ እናንተን በመገናኘቴ እና እንዲሁም ሊቀ ጳጳስ ፒዬሮ ማሪኒ ቀደም ሲል ባሰሙት ንግግር መደሰቴን ለመግለጽ እወዳለሁ። በዚህ ስብሰባ ላይ የተገኙትን ብሔራዊ የጳጳሳት ጉባሄ ተወካዮችን በተለይም ደግሞ እንደ አውሮፓዊያኑ የቀን አቆጣጠር በ2020 ዓ.ም ዓለማቀፍ የቅዱስ ቁርባን ኮንፈረን የሚካሄድበት የሀጋሪ ውና ከተማ ቡዳፔስት በካርዲናል ፒተር አርዶ መሪነት እዚህ ለተገኛችሁ ተወካዮች ሁሉ ሰላምታዬን አቀርባለሁ። መጪው ክብረ በዓል የሚከበረው በሀገሪቱ እና ከሀገሪቱ ባሽገር በአሁኑ ወቅት በመንጸባረቅ ላይ ባለው ሃይማኖታዊ ይዘት የሌለው ዘመናዊነት እና የተለያዩ ባሕላዊ እሴት ያላቸውን ታሪኮች እና ልዩነቶችን በማጥፋት ላይ የሚገኘው የግሎባላይዜሽን አስተሳሰብ በከፍተኛ ሁኔታ እየተንጸባረቀ በሚገኝበት  በታላቋ የአውሮፓ ከተማ ውስጥ የሚገኙ የክርስቲያን ማኅበርሰቦች እየገጠማቸው የሚገኘውን አዲስ ፈታኝ ሁኔታዎችን ለመቋቋም የምያስችል ቅዱስ ወንጌልን በአዲስ መልኩ ለማስፋፋት እንደ ሚረዳ ይጠበቃል።

ዘመናዊና በጣሙ ብዙ የተለያዩ ባህሎች በሚንጸባረቁበት ከተማ ቅዱስ ወንጌልና የሃይማኖት ተቋማት እምብዛም ባልተስፋፉበት ከተማ የቅዱስ ቁርባን ጉባሄ ማካሄድ ምን ማለት ነው? የሚለውን መሰረታዊ የሆነ ጥያቄ ያስነሳል። ይህም ማለት ከእግዚኣብሔር ጸጋ ጋር በመተባበር በጸሎት እና በተግባር "የቅዱስ ቁርባን ባሕል” መገንባት ማለት ነው-በሌላ አነጋገር በቅዱስ ቁርባን ላይ የተመሰረተ አስተሳሰብ እና አሠራር በመዘርጋት ይህ ምስጢር ከቤተ ክርስቲያን ማኅበርሰብ ባሻገር እንዲታወቅ ማድረግ ማለት ነው። በግድዬለሽ ስሜት፣ በክፍፍል እና የተለያየ ቅርጽ ባለው እቢታዎች በተሞላው አውሮፓ ክርስቲያኖች ግን ከእሁድ እስከ እሁድ እምነታቸውን በድጋሚ በማደስ ቀለል ባለ መልኩና ነገር ግን ኃይለኛ በሆኑ ምልክቶች ይገልጻሉ፣ በጌታ ስም ይሰበሰባሉ፣ እነርሱ ወንድማማቾች እና እህታማማቾች መሆናቸውን ይገልጻሉ። በዚህም ሁኔታ ተአምራቱ ይደጋገማሉ፣ ቃሉን በመስማት እና በሚቆርሱት እንጀራ ምልክት ውስጥ ታናናሾች እና አናሳ የሚባሉት እንኳን ሳይቀር የአማኞች ጉባሄ የጌታ አካል ይሆናሉ፣ በዓለም ውስጥ የእርሱ ማደሪያ ይሆናሉ። የቅዱስ ቁርባን ክብረ በዓል የቅዱስ ቁራባን ባህል የሚፈጥሩ አመለካከቶችን ያመጣል፣ ምክንያቱም በአኗኗራችን እና በአስተሳሰባችን ሁሉ ራሱን በምልኣት ለእኛ የሰጠውን ክርስቶስን እንድናስብ ስለሚያደርገን ነው።

ከእነዚህ ልምዶች ውስጥ የመጀመሪያው ኅብረት ነው። በመጨረሻው እራት ላይ ኢየሱስ የምስክርነቱ ስጦታ ምልክት እንዲሆን እንጀራን እና የእርሱ ተከታዮች እንድንሆን የሚያደርገንን ጽዋ መረጠ። ከዚህ በኋላ እኛ የጌታን መታሰቢያ በማክበር ስጋውን እና ደሙን በምንመግብበት ወቅት ከእርሱ ጋር የጠበቀ ግንኙነት እንዲኖረን፣ እንዲሁም በእያንዳንዱ አማኝ መካከል አንድነት እንዲፈጠር ያደርጋል። ከእየሱስ ጋር ኅብረት መፍጠር የሚለው አስተሳሰብ በአሁኑ ወቅት ላለው ሐዋርያዊ እንቅስቃሴ ትልቅ ተግዳሮት የሆነ ነገር ሲሆን፣ ይህም የሚሆንበት ምክንያት አማኞች በምስጢረ ቅዱስ ቁርባን ውስጥ ከሚገኘው ከኢየሱስ ጋር ያላቸውን ሕብረት ጠብቀው እዲቀጥሉ እና ከእርሱ ጋር አብረው እንድኖሩ፣ በእርሱ ፍቅር እና ተልዕኮ ውስጥ እንዲሳተፉ ስለሚረዳቸው ነው። ይህንንም ከመስዋዕተ ቅዳሴ ስነ-ስረዓት ውጪ በሚደረገው፣ ሁልጊዜም ቢሆን በቤተ ክርስቲያን ውስጥ በጋራ በሚደረገው የቅዱስ ቁርባን አምልኮ ማዳበር ይቻላል። የቅዱስ ቁራባን አምልኮ ጸሎት የኢየሱስ አካል እና አስተሳሰብ አንድ መሆናቸውን ለይተን እንድናውቅ ይረዳናል፣ ከእርሱ ጋር ምስጢራዊ በሆነ መልኩ የምንፈጥረው ኅብረት- ከሌሎች አባላት ጋር ተመሳሳይ ኅብረት እንድንፈጥር ይረዳናል፣ በተጨማሪም ከወንጌል ተልዕኮ ጋር ያለንን ኅብረት አጠናክረን እንድንቀጥል ያደርገናል።

ሁለተኛው አመለካከት ደግሞ አገልግሎት ነው። የቅዱስ ቁርባን ማኅበረሰብ አገልጋይ የሆነውን የኢየሱስን ባህሪይ በመላበስ ራሳችን “አገልጋይ እንድንሆን ያደርገናል”፡ የተሰጠውን የኢየሱስን ሥጋ በመመገብ እርሱ ራሱ ለሌሎች የተሰጠ አካል ይሆናል ማለት ነው። የቤተ ክርስቲያን ማሕጸን ወደ ሆነው ፣ ኢየሱስ የሐዋርያቱን እግር ወደ አጠበበት “ወደ ላይኛው ክፍል” በተከታታይ በመውጣት ክርስትያኖች በመስቀሉ ጥላ ሥር ተጠልለው፣ በቅዱስ ወንጌል ላይ ተምሰርተው ያገኙትን ፈውስ ለሌሎች ያካፍላሉ። በቤተ ክርስቲያን እና በማኅበርሰቡ ውስጥ በመንፈሳዊ እና በአካላዊ መልካም ስራዎች አማካይነት ፈውስ የሚያስገኝ ምሕረት ማምጣት የሚችሉ ምን ያህል ብዙ ሁኔታዎች አሉ! ችግር የገጠማቸው ቤተሰቦች፣ ሥራ አጥ የሆኑ  ወጣቶች እና አዋቂዎች፣ በሽተኞች እና የተረሱ አረጋዊያን ብዙ ጥቃት እየደረሰባቸው የሚገኙ ስደተኞች፣ በተለያየ ዓይነት ድህነት የሚሰቃዩ ሰዎችን ሁሉ ማሰብ ይገባል። በእነዚህ ነገሮች ምክንያት በቆሰለው ሰብዓዊ ማኅበርሰብ ውስጥ ክርስትያኖች በመስቀል ላይ ያለውን መታሰቢያ ማክበር እና አገልጋይ የሆነውን የኢየሱስ ክርስቶስን ወንጌል ለማቅረብ ተዘጋጅተዋል። በመሆኑም የተጠመቁ ሰዎች የቅዱስ ቁርባን ባሕል ልያስፋፋ የሚችል ዘር በመሆን  በግለሰባዊ ስሜት ተሞልተን ሳይሆን ነገር ግን በቅዱስ ወንጌል በመመራት  የድሆች አገልጋይ በመሆን የማኅበረሰቡ የሕይወት መመርያ እንዲሆን ማድረግ ይችላሉ። ይህንን ቀጣይነት ያለው ምስክርነት በጣም በብዙ ቅዱሳን የፍቅር ምስክርነት ሕይወት ውስጥ ተወልዶ እንደ ነበረ እንመለከታለን።

በመጨረሻም እያንዳንዱ መስዋዕተ ቅዳሴ በእያንዳንዳችን ከተማ ውስጥ  ብዙውን ጊዜ የሚረሱትን የወንጌል ቃላት በማስተዋወቅ የቅዱስ ቁርባን ሕይወትን ያፀናል። ምሕረትን ብቻ ማሰብ ያስፈልገናል። ሁሉም በማኅበረሰባችን ውስጥ የተፈጥረውን እና እየተንሰራፋ የሚገኘው ሰቆቃን በማሰብ ሁሉም ያማረራሉ። የተለያዩ የፍርሃት ዓይነቶች፣ ጭቆና፣ እብሪት፣ ጭካኔ፣ ጥላቻ እና ለአካባቢ ጥበቃ ለማድረግ ተነሳሽነትን ማጣት የመሳሰሉትን መጥቀስ ይችላል። ሆኖም ግን የእኛን ዓለም እያጥለቀለቀ በመምጣት ላይ ያለው ወንዝ በእየእሁዱ በምናገኘው የምሕረት ውቅያኖስ ላይ ኃይል እንደሌለው ክርስቲያኖች ያውቃሉ። ቅዱስ ቁርባን የእግዚአብሔር ምህረት የውሃ ምንጭ ነው፣ በእርሱ ውስጥ የታረደው፣ ነገር ግን ተነስቶ የቆመው የእግዚአብሔር በግ ከተወጋው ጎኑ ውስጥ የውኃ ጅረቶች እንዲፈልቁ በማድረግ መንፈሱን በማፍሰስ አዲስ ሕይወት እዲኖረን በማድረግ በፋሲካ ጠረጴዛ ላይ እራሱን ምግብ አድርጎ ያቀርብልናል። በዚህ ምክንያት ምህረት በዚህ ዓለም የደም ሥር ውስጥ ገብቶ በዚህ ዘመናዊ በሆነው ዓለማችን ውስጥ የሚኖሩትን የእግዚአብሔር ሕዝብ ምስል እና መዋቅር ለመመስረት ይረዳል።

የሚቀጥለው ዓለማቀፍ የቅዱስ ቁርባን ጉባሄ ከዘመናት በፊት የነበሩትን ጥንታዊ የሆኑ ባሕሎች እንዲቀጥሉ በማድረግ አዲስ መንፈሳዊ የሆነ ለውጥ የምናመጣበት ጎዳና እንዲጠቆም እና ቅዱስ ቁርባን የቤተ ክርስቲያን ሕይወት ማዕከል እንደሆነ ለማስታወስ ተጠርቷል። ምስጢረ ጥምቀትን የተቀበሉ ሰዎችን በግለሰብ ደረጃ አቅፎ የሚይዝ የፋሲካ ምስጢር ሲሆን ነገር ግን በተጨማሪም የሚኖሩበት እና የሚሠሩባት ምድራዊ ከተማን ሊያጠናክር ይችላል። የቡዳፔስት የምደረገው ዓለማቀፍ የቅዱስ ቁርባን ጉባሄ በክርስቲያን ማህበረሰቦች ውስጥ መንፈሳዊ የሆነ የእድሳት ሂደቶችን እንድያበረታታ፣ ከቅዱስ ቁርባን የሚመነጨው ደህንነት በአፅኖት በባህላዊ ልምምድ ውስጥ መልካም እና በጎ ፈቃድ ያላቸው ወንድ እና ሴቶች እንዲፈጠሩ በማድረግ በፍቅር፣ በትብብር፣ በሰላም በመኖር በቤተሰብ ሕይወት ውስጥ እና ለተፈጥሮ ጥበቃ ማድረግ እንዲችሉ ይረዳል።

ይህንን ዘገባ በድምጽ ለመከታተል ከዚህ በታች ያለውን “ተጫወት” የሚለውን ምልክት ይጫኑ!
10 November 2018, 16:09