የአፍሪካ የሐይማኖት ተቋማት ተወካዮች ዘመናዊ ጭቆናን ለማስቀረት እንደሚተባበሩ ገለጹ
የዚህ ዝግጅት አቅራቢ ዮሐንስ መኰንን - ቫቲካን
ሐምሌ 23/2013 ዓ. ም ዓለም አቀፍ ጸረ ሕገወጥ የሰዎች ዝውውር ቀን እንዲከበር ድጋፍ ያደረገው የአውስትራሊያ “ነፃ የእግር ጉዞ” ፋውንዴሽን፣ ሕገ-ወጥ የሰዎች ዝውውር ለመዋጋት በተቋቋመው ዓለም አቀፍ የነፃነት መድረክ ሥር የሚገኙ የአፍሪካ አብያተ ክርስቲያናት ኅብረት መሆኑ ታውቋል።
ሕገወጥ የሰዎች ዝውውርን ለመቃወም መተባበር
የስምምነት ሰነዱን ለማጽደቅ በጋና መዲና አክራ ላይ የተሰበሰቡት የአራት አፍሪካ አገራት የሐይማኖት ተቋማት ተወካዮች ከጋና፣ ከአይቮሪ ኮስት፣ ከኮንጎ ዴሞክራሲያዊት ሪፓብሊክ እና ከናይጄሪያ የተወጣጡ መሆናቸው ታውቋል። የደቡብ አፍሪካ የሐይማኖት ተቋማት እና የኬንያ የሐይማኖት ተቋማት ምክር ቤቶች በኮቪድ-19 ወረርሽ ምክንያት በስምምነት ሥነ-ሥርዓቱ ላይ መገኘት ባይችሉም ድጋፋቸውን ገልጸዋል። ስምምነታቸውን በፊርማ ካረጋገጡት መካከል አንዱ የጋና ካቶሊካዊ ብጹዓን ጳጳሳት ጉባኤ ጠቅላይ ጸሐፊ፣ ክቡር አባ ላዛሩስ ኣኖንዲ ናቸው። አባ ላዛሩስ በንግግራቸው፥ “ሕገወጥ የሰዎች ዝውውር ጥላቻን በማስፍፋት ፣ የሰው ልጆችን ለትርፍ ማግኛ የሚያውል በመሆኑ ወንጀል ነው” በማለት ገልጸውታል። በዓለም ዙሪያ በአስር ሚሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎችን ለጉዳት የዳረጋቸውን ሕገወጥ የሰዎች ዝውውር ለመዋጋት የሃይማኖት ተቋማት ተወካዮች ወሳኝ ሚና ለመጫወት ተስማምተዋል።
እ. አ. አ. በ 2014 በቫቲካን የስምምነት ውል ተፈርሟል
በጋና መዲና አክራ ላይ በአብያተ ክርስቲያናት ተወካዮች በኩል ዘመናዊ የጭቆና ቀንበርን ለመዋጋት የተደረሰው ስምምነት ስምንተኛው መሆኑ ታውቋል። ከዚህ በፊት እ. አ. አ በታኅሳስ 2/2014 ዓ. ም በቫቲካን በተካሄደው ስብሰባ ላይ ር. ሊ. ጳ ፍራንችስኮስ ከአንግሊካን ኅብረት መሪ እና የካንተርበሪው ሊቀ ጳጳስ ከሆኑት ከአቡነ ጃስቲን ዌልቢ እና የቆንስጣንጢንያ ኦርቶዶክሳዊት ቤተክርስቲያን ፓትሪያርክ ብጹዕ ወቅዱስ በርተለሜዎስ ቀዳማዊ ጋር ተገኝተው እንቅስቃሴ መጀመራቸው ይታወሳል። የእንቅስቃሴው ዓላማ፥ ዓለም አቀፍ የአብያተ ክርስቲያናት አውታረ መረቦችን በማስተባበር፣ በሁሉም የጭቆና ዓይነቶች፥ ከሴተኛ አዳሪነት እና ከአስገዳጅ የጉልበት ሥራ ጀምሮ እስከ አካል ዝውውር ድረስ ምዕመናን ግንዛቤ እንዲኖራቸው ማድረግ መሆኑ ይታወሳል። ሌሎች ዓላማዎችም ስነ-ምግባርን ማሳደግ ፣ ለወንጀሉ ተጠቂዎች እና ከወንጀሉ ላመለጡት ዕርዳታን ማድረግ፣ በመንግሥታት እና በፓርላማዎች ላይ ጫናን ማሳደር ፣ በማኅበረሰቦች መካከል ግንዛቤን ማሳደግ እና የገንዘብ ዕርዳታን ማሰባሰብ የሚሉ ይገኙባቸዋል።