በናይጄሪያ ታጣቂዎች 140 ተማሪዎችን እና አንድ የካቶሊክ ቤተክርስቲያን ካህን ማገታቸው ተገለጸ! በናይጄሪያ ታጣቂዎች 140 ተማሪዎችን እና አንድ የካቶሊክ ቤተክርስቲያን ካህን ማገታቸው ተገለጸ!  

በናይጄሪያ ታጣቂዎች 140 ተማሪዎችን እና አንድ የካቶሊክ ቤተክርስቲያን ካህን ማገታቸው ተገለጸ!

በናይጄሪያ በቅርቡ በተከሰተው ድንገተኛ አፈና አንድ የካቶሊክ ቄስን ጨምሮ በካዱና ግዛት ውስጥ ከሚገኘው አንድ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት 140 ተማሪዎች ታፍነው መወሰዳቸው ተገለጸ። በናይጄሪያ የማይዳጉሪ ሀገረ ስብከት ሥር በሚተዳደረው የካቶሊክ ቤተክርስቲያን አባል የሆኑት አባ ኤልያስ ጁማ ዋዳ የቦኮ ሃራም አባላት ናቸው ተብለው በተጠረጠሩ ታጣቂዎች ታፍነው ተወስደዋል ተብሏል።

የዚህ ዜና አቅራቢ መብራቱ ኃ/ጊዮርጊስ ቫቲካን

ከአከባቢው የሚወጡት የዜና ዘገባዎች እንዳሉት ይህ ክስተት ባለፈው ሰኞ ሰኔ 28/2013 ዓ.ም በሰሜን ምስራቅ ናይጄሪያ በቦርኖ ግዛት በዳምቦ-ማይጉዳይ አከባቢ ነበር ጉዳዩ የተፈጸመው። የአገረሰብከቱ ምዕመናን ካህኑ እና ተማሪዎቹ በሰላም ይለቀቁ ዘንድ ጸሎት እንዲያደርጉ ተጠይቋል።

140 ተማሪዎች ታፍነው ተወስደዋል

በተናጠል በቅርቡ በናይጄሪያ ውስጥ በትምህርት ቤቶች እና በዩኒቨርሲቲዎች ላይ በተፈፀመ የጠለፋ ጥቃት በሌላ ሁኔታ ፣ በሰሜን ምዕራብ የአገሪቱ ክፍል ከሚገኙ ትምህርት ቤቶች በደርዘን የሚቆጠሩ ሕፃና በታጣቂዎች ቡድን ታግተው እንደ ተወሰዱ የአገሪቷ ባለስልጣናት ተናግረዋል።

ታጣቂዎቹ ሰኞ ሰኔ 28/2013 ዓ.ም ማለዳ ላይ በካዱና ግዛት በቺኩን አካባቢያዊ አስተዳደር በዳሚሺ ከተማ በሚገኘው የቤቴል ባፕቲስት ሁለተኛ ደረጃ ት / ቤት ጥቃት የከፈቱ ሲሆን ቢያንስ 140 ተማሪዎችን አግተው ወስደዋል።

አንድ የፖሊስ ቃል አቀባይ እንዳሉት ታጣቂዎቹ በትምህርት ቤቱ የጥበቃ ሰራተኞች ላይ ከፈተኛ ጉዳት ካደረሱ በኋላ ነበር ወደ ተማሪዎች ማረፊያ ቤት በመግባት ቁጥራቸው ያልታወቁ ተማሪዎችን ወደ ጫካ ይዘው የተሰወሩት። ቃል አቀባዩ አክለው እንደ ተናገሩት የፀጥታ ኃይሎች አጋቾቹን በማሳደድ ላይ እያሉ 26 ተማሪዎችን እና አንዲት ሴት አስተማሪ በሰላም ማስለቀቅ መቻላቸውን ገልጸዋል። ሁሉም ተጎጂዎች በሰላም እንዲመለሱ ለማድረግ የነፍስ አድን ስራው አሁንም እንደቀጠለ ነው።

በናይጄሪያ ውስጥ የሚፈጸሙ አፈናዎች

ሰኞ ሰኔ 28/2013 ዓ.ም በቤቴል ባፕቲስት ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ላይ የተደረገው ጥቃት ከታህሳስ ወር ጀምሮ በካዱና ግዛት ውስጥ ቢያንስ አራተኛው የጅምላ ጥቃት እንደ ነበረ ተዘግቧል። የቦኮ ሃራም ፅንፈኛ ቡድን በቦርኖ ግዛት ቺቦክ ውስጥ ከሚገኝ አንድ ትምህርት ቤት ወደ 270 የሚጠጉ ልጃገረዶችን አፍኖ በወሰደበት ወቅት በናይጄሪያ በትምህርት ቤቶች ላይ የሚቃጣው ጥቃት እና አፈና ለመጀመሪያ ጊዜ ዓለም አቀፍ ትኩረት ስቦ እንደ ነበረ ይታወሳል።

በናይጄሪያ ውስጥ የታጠቁ ሽፍቶች ሰዎችን አፍኖ በመውሰድ ከፍተኛ የሆን ካሳ በመጠየቅ ላይ እንደ ሚገኙ እና የዚህ ዓይነቱ ሁኔታ ደግሞ በከፍተኛ ሁኔታ እየተንሰራፋ መምጣቱ ተገልጿል። አጋቾች በትምህርት ቤቶች እና በዩኒቨርሲቲዎች ፣ በመንገድ ፣ በግል መኖሪያ ቤቶች ውስጥ ሳይቀር በቅርቡ ደግሞ በሆስፒታሎች ላይ ያነጣጠሩ ጥቃቶችን በመክፈት ሰዎችን እያገቱ እንደ ሚገኙ ተገልጿል።

እሁድ ሰኔ 27/2013 ዓ.ም ማለዳ ላይ ታጣቂዎች በሰሜን ካዱና ግዛት ከሚገኝ ሆስፒታል ውስጥ የአንድ አመት ህፃን ጨምሮ ሌሎች 6 ሰዎችን አፍነው ወስደዋል። የናይጄሪያ የፀጥታ ኃይሎች በአገሪቱ በሰሜን ምሥራቅ እ.አ.አ ከ 2009 ዓ.ም ጀምሮ በአስር ሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎችን መገደላቸውን እና ከ 2 ሚሊዮን በላይ ሰዎችን በማፈናቀል የሚታወቀው አሸባሪ ቡድን ቦኩ አራም እንደ ሆነ ዘግበዋል።

07 July 2021, 15:35