በቅኝ ግዛት ውስጥ ከሚገኙ አፍሪካዊያን መካከል በቅኝ ግዛት ውስጥ ከሚገኙ አፍሪካዊያን መካከል 

የጀርመን መንግሥት በናሚቢያ ውስጥ የዘር ማጥፋት ወንጀል መፈጸሙን አመነ

የጀርመን መንግሥት እ. አ. አ በሃያኛው ክፍለ ዘመን መጀመሪያ ላይ በናሚቢያ ውስጥ ሄሬሮ እና ናማ በተባሉ ሁለት ጎሳዎች ላይ የዘር ማጥፋት ወንጀል መፈጸሙን በማመን የአንድ ቢሊዮን ዩሮ ካሳን ለመክፈል ቃል መግባቱን ተገለጸ። የካሳ ክፍያው በቅኝ ገዢዎች በኩል ኢ-ሰብዓዊ ተግባር ለተፈጸመባቸው የሄሬሮ እና ናማ ጎሳዎች የልማት ዕቅዶች ማስፈጸሚያ የሚውል መሆኑ ታውቋል።

የዚህ ዝግጅት አቅራቢ ዮሐንስ መኰንን - ቫቲካን

የጀርመን ቅኝ ገዢዎች በወቅቱ በናሚቢያ ውስጥ በአስር ሺዎች የሚቆጠሩ ሄሬሮ እና ናማ ጎሳ አባላትን መግደላቸው ሲታወስ ጭፍጨፋውም በሃያኛው ክፍለ ዘመን በደቡብ ምዕራብ አፍሪቃ የጀርመን ግዛት የተፈጸመ የዘር ጭፍጨፋ እየተባለ ሲነገር መቆየቱ ይታወሳል። በወቅቱ በጀርመን ቅኝ ገዢዎች የተፈጸመው ግድያ የዘር ማጥፋት ወንጀል ነበር በማለት የጀርመን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር የሆኑት አቶ ሄይኮ ማስ አስታውቀዋል።

የገንዘብ ዕርዳታ

የጀርመን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አቶ ማስ አክለውም፣ የጀርመን ቅኝ ገዥዎች በሁለቱ የናሚቢያ ጎሳዎች ላይ የፈጸሟቸው በርካታ አሰቃቂ ድርጊቶች መኖራቸውን በመገንዘብ፣ የሁለቱ ጎሳዎች ቤተሰቦችን ማቋቋሚያ ልማት የሚውል የ 1. 1 ቢሊዮን ዩሮ ካሳ ለመክፈል ከናሚቢያ መንግሥት ጋር ስምምነት ላይ መድረሳቸውን ተናግረዋል። ስምምነቱ የሁለቱ አገሮች የጨለማ ታሪክን ለመለወጥ የተደረገ ጥረት ውጤት ነው ብለዋል። በሁለቱ ወገኖች ማለትም በጀርመን እና በናሚቢያ መንግሥታት  ተወካዮች መካከል በተደረገው የስድስት ዓመት የስምምነት ድርድር ወቅት የሄሬሮ እና ናማ ጎሳዎች ተወካዮችም መገኘታቸው ታውቋል። በጀርመን እና በናሚቢያ መንግሥታት መካከል የተደረሰው ስምምነት ገና በፊርማ ያልጸደቀ መሆኑ ተነግሯል።

ተረስቶ የቆየ የዘር ማጥፋት ወንጀል

አንዳንድ የታሪክ ተመራማሪዎች በሃያኛው ክፍለ ዘመን መጀመሪያ የጀርመን ቅኝ ገዢዎች በናሚቢያ ላይ ያደረሱትን ስቃይ “ተዘንግቶ የቆየ የዘር ማጥፋት ወንጀል” ብለው ገልጸውታል። የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የዘር ማጥፋት ወንጀልን በልዩ ልዩ መንገድ የሚገልጽ ሲሆን ከእነዚህም መካከል የግድያ ተግባርን ጨምሮ በአንድ አገር ሕዝብ፣ ጎሳ፣ የዘር እና የሐይማኖት ቡድን ላይ በከፊል ወይም ሙሉ በሙሉ የሚፈጸም የግድያ ተግባር እንደሆነ ያስረዳል።

እውኔታው ሲፈተሽ

በናሚቢያ ውስጥ የሄሬሮ እና ናማ ጎሳዎች በአገሪቱ የሚገኙ ሁለት ቀደምት የጎሳ ቡድኖች መሆናቸው ይታወቃል። በሃያኛው ክፍለ ዘመን መጀመሪያ ላይ የጀርመን ቅኝ ገዢዎች በፈጸሙት በደል እነዚህ ሁለቱ ጎሳዎች የእርሻ መሬታቸውን በመቀማት ለጉልበት ብዝበዛ መዳረጋቸው ይታወሳል። እ. አ. አ በ1904 ዓ. ም የናማ እና የሄሬሮ ጎሳዎች ማመጽ በጀመሩበት ወቅት አገሪቱን በወታደራዊ አስተዳደር ይመሩ የነበሩት የጦር አዛዥ ጄኔራል ሎታር ቮን ትሮታ የዘር ማጥፋት ትዕዛዝ ባወጡበት ጊዜ የሄሬሮ እና ናማ ጎሳ አባላት ወደ በረሃ ለመሰደድ መገደዳቸው ይታወሳል።

ትዕዛዙን ሳይቀበሉ ቀርተው ወደ ቀዬአቸው በሚመለሱ አባላት ላይ የግዲያ ወይም ወደ ማጎሪያ ካምፖች የመግባት ዕድል የሚያጋጥማቸው መሆኑ ታውቋል። በወቅቱ በጀርመን ቅኝ ገዢዎች እጅ የተገደሉ የጎሳ አባላት ቁጥር ምን ያህል መሆኑ በውል ባይታወቅም በአሥር ሺህዎች የሚቆጠር እና በአገሬው ተወላጅ ሕዝቦች ላይ ከፍተኛ የቁጥር መቀነስን ያስከተለ ነበር ተብሏል።      

29 May 2021, 13:50