ካርዲናል ካንታላሜሳ “በዘላለም ሕይወት ያለን እምነት” እንደገና ማንቃት አለብን አሉ።

የጎርጎሮሳዊያኑን የቀን አቆጣጠር በሚከተሉ የካቶሊክ ቤተክርስቲያን ምዕመና ዘንድ የስብከተ ገና ወቅት በሕዳር 20/2013 ዓ.ም መጀመሩ የሚታወቅ ሲሆን በዚህ የስብከተ ገና ወቅት ተገቢ የሆነ መንፈሳዊ ዝግጅት ለማድረግ ያስችላቸው ዘንድ የርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት፣ በቫቲካን የእርሳቸው የቅርብ የሥራ ተባባሪ የሆኑት ብጹዕን ጳጳሳት እና ቄሳውስት፣ የርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ቤት ሰባኪ በሆኑት እና በቅርቡ የካርዲናለት ማዕረግ የተሰጣቸው ካርዲናል ራኔሮ ካንታላሜሳ ከሕዳር 25/2013 ዓ.ም ጀምሮ ይህንን የስብከተ ገና ወቅት አስመልክተው ለእዚህ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ የልደት በዓል ዝግጅት ይሆን ዘንድ በየሳምንቱ ዘወትር ዓርብ እለት አስተንትኖ ማደረግ መጀመራቸው ተገልጿል። በእዚህ መሰረት በታሕሳስ 02/2013 ዓ.ም ዐርብ እለት በቫቲካን በሚገኘው በጳውሎስ 6ኛ የስብሰባ አዳራሽ በተደርገው ሁለተኛው የስብከተ ገና ወቅት አስተንትኖ ካርዲናል ራኔሮ ካንታላሜሳ ሁላችንም “በዘላለም ሕይወት ያለን እምነት” እንደገና ማንቃት አለብን ብለዋል።

ይህንን ዝግጅት ከእዚህ በታች ያለውን ተጫወት የሚለውን ምልክት በመጫን ማዳመጥ ትችላላችሁ!

የእዚህ ዝግጅት አቅራቢ መብራቱ ኃ/ጊዮርጊስ ቫቲካን

የጳጳሳዊው ቤተሰብ ሰባኪ ካርዲናል ራኔሮ ካንታላሜሳ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ በተገኙበት በቫቲካን በሚገኘው በጳውሎስ ስድስተኛ የስብሰባ አዳራሽ ሁለተኛውን የስብከተ ገና ወቅት አስተንትኖ አድርገዋል። ካርዲናል ራኔሮ ካንታላሜሳ በወቅቱ ባደረጉት አስተንትኖ “በዘላለም ሕይወት ያለን እምነት” እንደገና ማወቅ አለብን በሚል ጭብጥ ዙሪያ ላይ ያጠነጠነ እንደ ነበረ ተገልጿል። ዘላለማዊነት “ቃል የተገባልን ነገር እና ተስፋ ብቻ አይደለም” ነገር ግን በክርስቶስ ታሪክ ውስጥ ገብቶ መኖር ማለት ነው ብለዋል።

ካርዲናል ካንታላሜሳ ስለ ሞት ትርጉም ባለፈው ሳምንት በሕዳር 25/2013 ዓ.ም ባደረጉት የመጀመርያው የስብከተ ገና አስተንትኖ ላይ እንዲንፀባረቅ ካደረጉ በኋላ በኮሮና ወረርሽኝ ሁኔታ ወደ ብርሃን ስለመጣው ሌላ “እውነት” እንድያሰላስሉ ጋብዘዋል። ሁሉም ነገር ያልፋል-“ሀብት ፣ ጤና ፣ ውበት ፣ አካላዊ ጥንካሬ” ሳይቀር እነዚህ ሁሉ ነገሮች አላፊዎች ናቸው።  ነገር ግን በምንኖርበት ምድራችን ላይ እየደረሰ የሚገኘው ከፍተኛ ቀውስ ካርዲናልን ካንታላሜሳ እንደገለፁት ምንም እንኳን ሁሉም ነገር ቢኖርም ፣ ቋሚ የሆነ ቦታ ፣ ጠንካራ መሬት ፣ ጠንክራ የሆነ ዐለት፣ ምድራዊ ሕልውናችንን መሠረት የምናደርግበት እፎይታን ለማግኘት እንደገና ለመርዳት አዲስ ዕድል ሊፈጥር ይችላል” ብለዋል። ይህንን በተመለከተ ሲናገሩ የሚከተለውን ብለዋል . . .

“በጭራሽ የማያልፈው ነገር” ቢኖር በትርጉሙ ዘላለማዊነት ነው። ከሞት በኋላ ባለው ሕይወት ውስጥ ያለውን እምነት እንደገና ማግኘት አለብን። የተሻለ እና የወንድማማችነት ዓለም ለመፍጠር ከሚደረገው ጥረት ጋር ሃይማኖቶች አብረው ሊያደርጉት ከሚችሉት ትልቅ አስተዋፅዖ አንዱ ይህ ነው። የዘር ወይም የብሔር ልዩነቶች ወደ ሌሉበት ወደ የጋራ የትውልድ ሀገራችን በሚወስድን መንገድ ላይ ሁላችንም የምንጓዝ ወዳጆች መሆናችንን እንድንገነዘብ ያደርገናል። እኛ የጋራ መንገድ ብቻ ሳይሆን የጋራ ግቡም አለን።

በዘላለም ሕይወት ማመን እና ስብከተ ወንጌል

“ለክርስቲያኖች በዘላለም ሕይወት ላይ ያለው እምነት በትክክለኛው እውነታ ላይ የተመሠረተ ነው፣ ይህም በክርስቶስ ትንሣኤ ላይ ያለን እምነት ነው” በማለት አስተንትኖዋቸውን የቀጠሉት ካርዲናል ካንታላሜሳ “ለእኛ ክርስቲያኖች የዘላለም ሕይወት ረቂቅ የሆነ ምድብ አይደለም፣ ይልቁንም የሰው ልጅን የተመለከተ ጉዳይ ነው ብለዋል። ይህ ማለት ከኢየሱስ ጋር መሆን ፣ ከእርሱ ጋር “አንድ አካል መሆን” ፣ የሶስትዮሽ ሕይወት ሙላት እና የማይዳሰስ ደስታ ውስጥ የራሴን ግዛት ማካፈል ማለት ነው ብለዋል። “ዘላለማዊነት” የሚለው ቃል በመርሳት እና በዝምታ ውስጥ ገብተናል፣ ሴኩላሪዝም ማለትም በሳይንስና ተጨባጭ እውነታ ላይ የተመሰረተ እምነት “እውነተኛ የሆነውን ነገር ወደ ምድራዊ ልኬት የቀነሰ” አስተሳሰብ እንደ ሆነ የገለጹ ሲሆን “የዘላለም ሕይወት አድማስ ስር ነቀል ለውጥ በማደረግ ለማስወገድ” ችሎ እንደ ነበረ ገልጸዋል። ካርዲናል ካንታላሜሳ አስተንትኖዋቸውን ሲቀጥሉ እንደ ገለጹት አንዴ ይህ አድማስ ከወደቀ በኋላ የሰዎች ሥቃይ “በእጥፍ እና በማይጠቅም ሁኔታ የማይረባ ይመስላል” ብለዋል። ዓለም “የምስጥ ኩይሳ የሚያፈርስ” ሰው እና “ቀጣዩ ሞገድ በሚሽረው በባህር ዳርቻ አሸዋ ላይ በማዕበል የተሰራ ዲዛይን” ይመስላል ብለዋል። ይህንን በተመለከተ የሚከተለውን ብለዋል . . .

በዘላለማዊ ሕይወት ላይ ያለን እምነት የስብከተ ወንጌል አገልግሎት ለመስጠት ከሚቻልባቸው ሁኔታዎች አንዱ ነው። "ሐዋርያው ጳውሎስ እንደ ገለጸው ‘ክርስቶስም ካልተነሣ ስብከታችን ዋጋ ቢስ ነው፤ እምነታችሁም ከንቱ ነው [...] ክርስቶስን ተስፋ ያደረግነው ለዚህች ሕይወት ብቻ ከሆነ፣ ከሰው ሁሉ ይልቅ የምናሳዝን ነን’” (1 ቆሮ 15፡14.19) የዘላለም ሕይወትን ማወጅ የክርስቲያን ስብከት ጠንካራ እና ቆንጣጭ እንዲሆን ያደርጋል።

ዘላለማዊነት ካርዲናል ካንታላሜሳ እንዳሉት “የሰው ልብ ጥልቅ ፍላጎት” ነው ያሉ ሲሆን እኛ በእውነቱ “ውስን የመሆን ችሎታ ያላቸው ዘላለማዊ የሆን ፍጡሮች ነን፣ ሟች ፍጥረታት ያለመሞት ምኞት ያላቸው ናቸው ብለዋል። በዘላለማዊነት የታደሰ እምነት “የሚያገለግለን ለስብከተ ወንጌል አገልግሎት ብቻ አይደለም” በማለት አስተንትኖዋቸውን የቀጠሉ ካርዲናል ካንታላሜሳ በመጀመሪያ “ለመቀደስ የሚያስችሉንን አዳዲስ መንገዶች ለመምረጥ ተነሳሽነቱ ሊኖረን ይገባል” ብለዋል፣ የመጀመርያ ፍሬ “ከሚያልፉ ነገሮች ራሳችንን ነፃ ማውጣት ሊሆን ይገባል” ብለዋል። ይህንን በተመለከተ ደግሞ የሚከተለውን ብለዋል . . .

እስቲ ይህንን ሁኔታ እናስብ። አንድ ሰው ከቤት እንዲወጣ የሚገልጽ ማስጠንቀቂያ ይደርሰዋል፣ እናም በአጭር ጊዜ ውስጥ ቤቱን ለቅቆ መውጣት አለበት። እንደ እድል ሆኖ ወዲያውኑ አዲስ ቤት የማግኘት ዕድል ለማግኘት ተቃርቧል። ነገር ግን ምን ያደርጋል? የሚለቀውን ቤት ጥሎ ከመውጣቱ በፊት ያን ያለበትን ቤት በማደስ እና በማስዋብ ገንዘቡን ሁሉ ይጨርሳል! ያ ሞኝነት አይደለም እንዴ? እኛም ሁላችንም በዚህ ዓለም ውስጥ "ተባራሪ” ነን፣ እናም ከሞት በኋላ ለሚገጥመን አዲሱ ቤታችን የሚያበቁን እና ለሚከተሉን መልካም ሥራዎች ሳንጨነቅ ምድራዊ ቤታችንን ስለ ማስዋብ ብቻ ካሰብን ያንን ሞኝ ሰው እንመስላለን። የዘላለማዊነት እሳቤ ሲደበዝዝ በአማኞች ላይ እርምጃ ይወስዳል ፣ በእነሱም ውስጥ የሕይወትን ስቃይ እና ፈተና በድፍረት የመቋቋም ችሎታን ይቀንሰዋል። የቅዱስ በርናዶስ እና የሎዮላውን ቅዱስ ኢግንሺየስ እምነት እንደገና መፈለግ አለብን። እነርሱም  በእያንዳንዱ ሁኔታ እና በእያንዳንዱ መሰናክል ፊት ለራሳቸው “በዘለአለም ሕይወት ፊት ይህ ምንድነው?” ብለው ጥያቄ ያቀርቡ ነበር።

ዘላለማዊነት መኖር ማለት ነው

ካርዲናል ካንታላሜሳ አስተንትኖዋቸውን ከማጠናቀቃቸው በፊት እንደገለጹት “ዘላለማዊነት ቃል ኪዳን እና ተስፋ ብቻ አይደለም፣ ወይም ካርል ማርክስ እንዳሰበው በምድር ተስፋ ያስቆረጡንን ነገሮች ወደ ሰማይ መበትን ማለት አይደለም። ዘላለማዊነት ማለት “መኖር እና ተሞክሮ” ነው። በክርስቶስ “ከአብ ጋር የነበረው የዘላለም ሕይወት ታየ”። “ሰው ከሆነው ቃል ክርስቶስ ጋር ፣ ዘላለማዊነት ወደ ጊዜ ውስጥ ገባ። በክርስቶስ የምናምንበትን እውነተኛ የእምነት ተግባር በምናደርግበት ጊዜ ሁሉ እናገኘዋለን ፣ ምክንያቱም በእርሱ የሚያምኑት ቀድሞውኑ የዘላለም ሕይወት አላቸው ካሉ በኋላ የሁለተኛ የስብከተ ገና አስተንትኖዋቸውን አጠቃለዋል።

11 December 2020, 15:42