ር. ሊ. ጳ ፍራንችስኮስ ከአረጋዊያን ጋር ሰላምታ ሲለዋወጡ፣ ር. ሊ. ጳ ፍራንችስኮስ ከአረጋዊያን ጋር ሰላምታ ሲለዋወጡ፣ 

ካርዲናል ታርክሰን በወረርሽኙ ወቅት ማኅበረሰብ ለአረጋዊያን እንክብካቤ እንዲያደርግ ጠየቁ።

በአውሮፓ ውስጥ በኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ሕይወታቸውን ካጡት መካከል ግማሽ የሚሆኑ በአረጋዊያን መርጃ ማዕከላት ውስጥ ይኖሩ የነበሩ መሆንስቸው ታውቋል። ርዕሠ ሊቃነ ጳጳስት ፍራንችስኮስ ለአረጋዊያን ሊደረግ የሚገባውን እንክብካቤ በማስመልከት ባለፈው የጥር ወር ባስተላለፉት መልዕክት “እርጅና ጸጋ እንጂ በሽታ አይደለም” ማለታቸው ይታወሳል። ለአረጋዊያን የሚሰጥ አገልግሎት በማስመልከት በቅድስት መንበር የሰው ልጅ ሁለንተናዊ እድገት አገልግሎት ጳጳሳዊ ጽሕፈት ቤት ተጠሪ የሆኑት ብጹዕ ካርዲናል ፒተር ኮዱዎ ታርክሰን ከቫቲካን የዜና አገልግሎት ጋር ቃለ ምልልስ አድርገዋል።  

የዚህ ዝግጅት አቅራቢ ዮሐንስ መኰንን - ቫቲካን 

በተባበሩት መንግሥታት ሥር የአውሮፓ አህጉር የጤና ጥበቃ ጉዳይ ዳይሬክተር የሆኑት ክቡር ሃንስ ክሉግ እንዳስታወቁት በአውሮፓ ውስጥ በኮሮርና ቫይረስ ወረርሽኝ ሕይወታቸውን ካጡት ሰዎች መካከል ሃምሳ ከመቶ የሚሆኑት የሚሆኑ በአረጋዊያን መንከባከቢያ ማዕከላት ውስጥ ይኖሩ የነበሩ መሆናቸውን ገልጸዋል። በመሆኑም ማዕከላቱ ለአረጋዊያን የሚሰጡትን አገልግሎት በድጋሚ በማጤን ፈጣን ለውጥ እንዲያደርጉ ጠይቀው፣ በእርግጥ በማዕከላቱ ተመድበው የሚሠሩ የሕክማና ባለሞያዎች እና ረዳቶቻቸው ከፍተኛ የሥራ ጫና ያለባቸው፣ ለነፍስ አድን አገልግሎት ራሳቸውን አሳልፈው የሰጡ መሆናቸውንም አስታውሰዋል። ቤተክርስቲያን ሁል ጊዜ ለአረጋዊያን ቅድሚያን በመስጠት የምታቀርበውን የአገልግሎት ደረጃ መመልከት ያስፈልጋል ተብሏል።

ካርዲናል ታርክሰን፥ ወጣቶች አረጋዊያንን የመንከባከብ አደራ አለባቸው፣

በቅድስት መንበር የሰው ልጅ ሁለንተናዊ እድገት አገልግሎት ጳጳሳዊ ጽሕፈት ቤት ተጠሪ የሆኑት ብጹዕ ካርዲናል ፒተር ኮዱዎ ታርክሰን ከቫቲካን የዜና አገልግሎት ጋር በሚያደርጉት ቃለ ምልልስ፣ በእያንዳንድዱ ትውልድ መካከል የመተጋገዝ ባሕል መኖር የግድ ነው በማለት በተደጋጋሚ ማስገንዘባቸው ይታወሳል። በቃለ ምልልሳቸው ወቅት ወጣቶችም በሚኖሩበት ማሕበረሰብ ውስጥ አረጋዊያንን መርዳት እና መንከባከብ እንደሚያስፈልግ አሳስበው፣ በአፍሪካ ማህበረሰቦች ውስጥ ወጣቶች አረጋዊያንን የመርዳት፣ የመታዘዝ እና የማገዝ ባሕል ከምን ጊዜም በላይ አስፈላጊ መሆኑን አስረድተዋል። የሰውን  ልጅ ሕይወት መሠረት ባደረገ አስተንትኗቸው ብጹዕ ካርዲናል ታርክሰን እንዳስረዱት፣ የሰው ልጅ ልዩ ትኩረት ተሰጥቶት በቂ እንክብካቤ ሊደረግለት የሚያሻው መሆኑን ገልጸው፣ ይህም የሕክምና አገልግሎትን ጨምሮ በሁሉም የአገልግሎት ዘርፍ ተግባራዊ ሊሆን ይገባል ብለዋል። ብጹዕ ካርዲናል በማከልም የዘመናዊ ቴክኖሎጂዎች እድገት ራሳችንን ከፍ አድርገን እንድንመለከት ቢያደርገንም ፣ የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ባስከተለው አስቸኳይ የዕርዳታ አቅርቦት ላይ እጅግ የበለጸጉ አገራትም ዝቅተኛ ዋጋ ያላቸው የሕክምና እጥረት ያጋጠማቸው መሆኑን አስታውሰዋል።

አረጋውያን ክብር ሊሰጣቸው ይገባል፣

ብጹዕ ካርዲናል ፒተር ታርክሰን በማኅበረሰብ ውስጥ አንዱ ለሌላው መቆርቆር አስፈላጊ መሆኑን ገልጸው፣ ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ ብዙን ጊዜ እንዳስገነዘቡት፣ አረጋዊያን በማኅበረሰብ ውስጥ ልዩ ክብር እና ምስጋና ሊሰጣቸው ያስፈልጋል ማለታቸውን አስታውሰዋል። አክለውም በማኅበረሰብ እና በአረጋዊያን መካከል ያለው ግንኙበት ማደግ እንዳለብት አሳስበው የማኅበራዊ ኑሮ ዘይቤ በእጅጉ መለወጡን ገልጸው፣ በአንዳንድ አዳዲስ አስተሳሰቦች የተነሳ ወጣቶች ለአረጋዊያን ሊያበረክቱ የሚገባቸው ድጋፍ መጓደሉን አስረድተዋል።

ብጹዕ ካርዲናል ፒተር ታርክሰን የአረጋዊያንን ሕይወት በተመለከተ አስተንትኗቸው እንዳስረዱት፣ እያንዳንዳችን ከሕጻንነ ዕድሜ ጀምሮ የኖርንበት እና ያደግንበት ቤታችን ሕይወታችንን የመሰረትንበት ትንሿ የዓለማችን ክፍል መሆኗን አስታውሰው፣ ባሁኑ ወቅት በርካታ ሰዎች የሕይወታቸውን መጨረሻ ዘመን በዕርዳታ መስጫ ማዕከላት ውስጥ ለማሳለፍ የሚወስኑ መሆኑን ገልጸዋል። ይህን ውሳኔ የሚያደርጉት የሚረዳቸው አጥተው ብቻቸውን ስለቀሩ እና ከሌሎች ሰዎች ጋር ለመሆን ስለሚፈልጉ መሆኑን አስረድተዋል። አንዳንዶች ደግሞ በአረጋዊያን ማዕከላት ውስጥ መኖር እንደ ቤታቸው አድረገው መቁጠር የሚከብዳቸው መሆኑን አስረድተዋል። በአረጋዊያን እርዳታ መስጫ ማዕከላት ውስጥ የተለያዩ አገልግሎቶችን  በማበርከት ላይ ለሚገኙ ሠራተኞች ብጹዕ ካርዲናል ፒተር ታርክሰን ምስጋናቸውን አቅርበውላቸዋል። በሃያ አንደኛው ክፍለ ዘመን ስለ አረጋዊያን ሕይወት በስፋት እንድናስታውስ ያጋብዘናል ያሉት ብጹዕ ካርዲናል ፒተር ታርክሰን፣ ባለፈው የጥር ወር ርዕሠ ሊቃነ ጳጳስት ፍራንችስኮስ “እርጅና ጸጋ እንጂ በሽታ አይደለም” ማለታቸውን አስታውሰዋል።

አረጋዊያን የእግዚአብሔር ፍቅር መስካሪዎች ናቸው፣

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳስት ፍራንችስኮስ ባለፈው ጥር ወር፣ ለአረጋዊያን የሚሰጥ ሐዋርያዊ አገልግሎት በማስመልከት በተካሄደው ዓለም ጉባኤ ላይ እንድተናገሩት እርጅና ጸጋ እንጂ በሽታ አይደለም ብለው በሽታ የሚሆነው በብቸኝነት ሲጠቁ ብቻ እንደሆነ አስረድተው፣ ከዚህ በሽታ መፈወስ የሚችሉት የፍቅር ሥራዎቻችንን ስናበረክት እና አጠገባቸው ስንሆን ነው ብለዋል። እግዚአብሔር በእድሜ ባለጸጎች በኩል አዲስ የቅድስና፣ የመንፈሳዊ አገልግሎት እና የጸሎት ምዕራፍ ሊያሳየን እንደሚፈልግ ገልጸው፣ አረጋዊያን ቤተክርስቲያን ውስጥ የዛሬም ሆነ የነገ አለኝታ ናቸው ብለዋል።

ዓለምን እና አውሮፓን ስናወዳድር፣ 

የአውሮፓዊያኑን አማካይ ዕድሜ ከዓለም ሕዝብ አማካይ የዕድሜ ገደብ ጋር ያወዳደሩት ፣ በዓለም ጤና ድርጅት የአውሮፓ አህጉር ተጠሪ የሆኑት ክቡር አቶ ሃንስ ክሉግ፣ አውሮፓ ከዓለም ሕዝብ አማካይ ዕድሜ ጋር ሲወዳደር ከፍተኛውን የዕድሜ ገደብ የያዘ መሆኑን አስረድተው፣ ከአሜሪካ እና ከኦሼኒያ አገሮች ጋር ሲነጻጸር በአሥር ዓመት እንደሚበልጥ፣ ከአፍሪቃ አህጉር ጋር ሲወዳደሰር በ25 ዓመት የሚበልጥ መሆኑን አስረድተው፣ በዓለም ጤና ድርጅት መረጃ መሠረት የጃፓን ሕዝብ በአማካይ ካስመዘገበው 84 ዓመት የዕድሜ ገደብ ቀጥሎ የአውሮፓ አህጉር ሁለተኛ ደረጃ መያዙን አስረድተዋል።

ይህን ዜና በድምጽ ማድመጥ ከፈለጉ የተጫወት ምልክትን ይጫኑ፣
27 April 2020, 17:57