አዲስ ለተወለደ ሕጻን የሚደረግ የወላጅ እንክብካቤ፣ አዲስ ለተወለደ ሕጻን የሚደረግ የወላጅ እንክብካቤ፣ 

በቅድስት መንበር የምእመናን፣ የቤተሰብ እና የሕይወት መምሪያ ጳጳሳዊ ምክር ቤት ምስረታ ተዘከረ።

በቅድስት መንበር ሥር ተጠናክሮ በመቅረብ አገልግሎቱን ከጀመረ ሦስት ዓመታትን ያስቆጠረው የምእመናን እና የቤተሰብ ሕይወት መምሪያ ጳጳሳዊ ምክር ቤት፣ በሦስት ዓመታት ውስጥ ያካሄዳቸውን ልዩ ልዩ ሥራዎቹን ተመልክቷል። ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ በሐዋርያዊ የግል ስልጣናቸው የምእመናን እና የቤተሰብ ሕይወት የሚከታተል ጳጳሳዊ ምክር ቤት በአዲስ መልክ እንዲቋቋም ሐዋርያዊ ትዕዛዝ ካስተላለፉ ሦስት ዓመታት መቆጠራቸውን የቫቲካን ዜና ዘጋቢ አመዴዎ ሎሞናኮ የላከልን ዘገባ አመልክቷል።

የዚህ ዝግጅት አቅራቢ ዮሐንስ መኰንን - ቫቲካን

“ለምእመናኖችዋ የምትራራ እናት ቤተክርስቲያን” የሚለው የርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ ሐዋርያዊ ትዕዛዝ፣ ቤተክርስቲያን በውስጧ ለሚገኙት ምእመናን እና የቤተሰብ ክፍሎች የሚገባውን እንክብካቤን በመስጠት፣ የምህረት አባት የሆነውን የእግዚአብሔርን እውነተኛ ፍቅርን ለሰው ልጆች በሙሉ የምትገልጽ መሆኗን አስረድቷል። የርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ ሐዋርያዊ ትዕዛዝ፣ በቅድስት መንበር ስር የሚገኙ ሌሎች ጳጳሳዊ ምክር ቤቶችም የዘመናችንን ክስተቶች በሚገባ በመገንዘብ ከኩላዊት ቤተክርስቲያን አካሄድ ጋር በመጓዝ አገልግሎታቸውን ያበረክታሉ ብሏል። ለምእመናን፣ ለቤተሰብ እና ለሕይወት በሙሉ ለሚሰጥ ትኩረት እና እንክብካቤ ቅድሚያን የሰጠው የቅዱስነታቸው ሐዋርያዊ ትዕዛዝ፣ ምዕመናን እና የቤተሰብ ክፍሎች የወንጌል ሕይወትን እየኖሩ፣ በንቃት የእግዚአብሔርን ምህረት የሚመሰክሩ መሆናቸውን ገልጿል።

ለአገልግሎቱ ብቁ ሆኖ መገኘት፣

በቅድስት መንበር የምእመናን፣ የቤተሰብ እና የሕይወት መምሪያ ጳጳሳዊ ምክር ቤት፣ ሐዋርያዊ መንበር በእግዚአብሔር እቅድ መሠረት ለወጣቶች፣ ለቤተሰብ እና ለምእመናን በሙሉ የምታበረክተውን ሐዋርያዊ እንክብካቤ በመከታተል ድጋፍ የሚሰጥ መሆኑን ታውቋል። የምእመናን፣ የቤተሰብ እና የሕይወት መምሪያ ጳጳሳዊ ምክር ቤት ከሚያከናውኗቸው ተግባራት መካከል ጥቂቶቹ፣ የወጣቶችን እና የቤተሰብን መንፈሳዊ እና ማሕበራዊ እደገትን በማስመልከት የሚደረጉ ዓለም አቀፍ ጉባኤዎችን ማዘጋጀት እና ባስተባበር፣ ለምስጢረ ተክሊል ወይም ለጋብቻ ሕይወት ለሚዘጋጁ ወጣቶች በቂ መንፈሳዊ ትምህርቶች እንዲዳረሱ በማድረግ፣ በማሕበራዊ ሕይወት ውስጥ የምእመናን እና የቤተሰብ ሕይወት ምን እንደሚመስል የቅርብ ክትትልን የሚያደርግ መሆኑ ታውቋል። ከዚህም ባሻገር የምእመናን፣ የቤተሰብ እና የሕይወት መምሪያ ጳጳሳዊ ምክር ቤት በአገልግሎቱ አማካይነት በቤተክርስቲያን ውስጥ ምእመናን በግል ሆነ በጋራ ሆነው ለወንጌል ተልእኮ እንዲዘጋጁ በማድረግ፣ ለዚህም እውነተኛ ጥሪ የሚገኝበት መንገድ እንዲዘጋጅ በማስተባበር፣ እንደዚሁም የቤተክርስቲያን ማሕበራት እና እንቅስቃሴዎች የሚጠናከሩበትን መንገድ በመፈለግ የአገልግሎት ድርሻውን የሚያበረክት መሆኑ ታውቋል። የምእመናን፣ የቤተሰብ እና የሕይወት መምሪያ ጳጳሳዊ ምክር ቤት በተጨማሪም ወላጅን ያጡ ሕጻናት በመልካም ስነ ምግባር እና በእውቀት እንዲያድጉ በማለት አስፈላጊውን እገዛ የሚያደርጉ ተቋማትን የሚደግፍ ሲሆን፣ በተመሳሳይ መልኩ አቅመ ደካማ የሆኑ የማሕበረሰብ ክፍሎችን ወደ ማዕከላቸው ተቀብለው እርዳታ የሚያደርጉ ተቋማትን የሚያግዝ እና የሚያበረታታ መሆኑ ታውቋል።           

 የስነ ሕይወት ጥናት አካዳሚ ጳጳሳዊ ምክር ቤት፣

በቅድስት መንበር የምእመናን፣ የቤተሰብ እና የሕይወት መምሪያ ጳጳሳዊ ምክር ቤት ፕሬዚደንት ብጹዕ ካርዲናል ኬቪን ፋረል ሲሆኑ ዋና ጸሐፊያቸው ክቡር አባ አሌሳንደር አዊ ሜሎ መሆናቸው ታውቋል። በቅድስት መንበር የምእመናንና የቤተሰብ ሕይወት መምሪያ ጳጳሳዊ ጽሕፈት ቤት፣ በቫቲካን ከሚገኝ ከስነ ሕይወት ጥናት አካዳሚ ጳጳሳዊ ምክር ቤት ጋር ተደጋግፈው በመሥራት የቅርብ ግንኙነት ያላቸው መሆኑ ታውቋል።

ይህን ዘገባ በድምጽ ለማዳመጥ ከዚህ ቀጥሎ የሚገኘውን “ተጫወት” የሚለውን ምልክት ይጫኑ!
20 August 2019, 17:08