አባ ራኔሮ ካንታላሜሳ አባ ራኔሮ ካንታላሜሳ  

አባ ካንታ ላሜሳ “የእግዚኣብሔርን እንጂ የሰውን አመለካከት መከተል አይገባንም!”

አሁን የምንገኝበት ወቅት የዐብይ ጾም ወቅት እንደ ሆነ ይታወቃል። በዚህ በዐብይ ጾም ወቅት ተገቢ የሆነ መንፈሳዊ ዝግጅት ለማድረግ ያስችላቸው ዘንድ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ እና በቫቲካን የእርሳቸው የቅርብ የሥራ ተባባሪ የሆኑት ብጹዕን ጳጳሳት እና ቄሳውስት፣ የርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ቤት ሰባኪ በሆኑት አባ ራኔሮ ካንታላሜሳ መሪነት ባለፉት ቀናት ውስጥ ሲካሄድ የቆየው ሱባሄ መጋቢት 06/2011 ዓ.ም ላይ መጠናቀቁ ታውቁዋል። በዚህ ሱባሄ ማብቂያ አከባቢ አባ ካናታ ላሜሳ እንደ ገለጹት “የእግዚኣብሔርን እንጂ የሰውን አመለካከት መከተል አይገባንም” ማለታቸው ተገልጹዋል።

የዚህ ዝግጅት አቅራቢ መብራቱ ኃ/ጊዮርጊስ-ቫቲካን

ኢየሱስ ክርስቶስ በጥብቅ ያወገዘውን ግብዝነትን ለመዋጋት ያስችለን ዘንድ፣ በእየለቱ በሕይወታችን ውስጥ እየገባ የሚረብሸንን የግል ፍላጎቶቻችንን ለማሸነፍ ያስቸልን ዘንድ፣ ከራሳችን እያታ ይልቅ በቅድሚያ የእግዚኣብሔር አመለካከት በሕይወታችን ውስጥ ይሰርጽ ዘንድ ማድረግ እንደ ሚገባ አባ ካንታ ላሜሳ ጨምረው ገልጸዋል።

አምላክን ለማየት የሚያስችለን ቅድመ ሁኔታ ምንድነው? በማለት ጥያቄ በማንሳት ስብከታቸውን የቀጠሉት ቅዱስነታቸው ለዚህ ጥያቄ ተገቢው መልስ የሚገኘው ኢየሱስ በተራራው ላይ በሰበከው ስብከት ውስጥ የሚገኘው “ልበ ንፁዕን የተባረኩ ናቸው ምክንያቱም እግዚኣብሔርን ያዩታልና!” የሚለውን መስፈርት በቅድሚያ ሟሟላት ይኖርብናል ብለዋል።

ከፆታዊ ግንኙነት ጋር የተዛመደ ንጽሕና

'ንጽሕና' የሚለው ቃል ብዙ ትርጉሞች ያለው ሲሆን ሰባኪው አባ ካንታ ላሜሳ ከእነዚህ ብዙ ትርጉሞች ውስጥ ሁለቱን ይመርጣሉ፡ እነዚህም የሕሊና ንጽሕና እና ጾታዊ ንጽሕና የተሰኙት ናቸው። የእነዚህ ሁለት ትርጉሞች ተቃራኒ የሆኑ ሁለት ጫፎች ደግሞ በአንድ በኩል ግብዝነት ሲሆን በሌላ በኩል ደግሞ ጾታዊ ግንኙነትን ያለአግባብ መጠቀም እንደ ሆነ ገልጸዋል። የስነ-ጾታዊ ግንኙነት መዛባት ደግሞ የሚከተለውን ያስከትላል . . .

ጾታዊ ንጽሕናን በማጉደፍ የምንሠራው ኃጢአት የእግዚአብሔርን ፊት እንዳናይ ይጋርደናል፣ ብናይ ብናይ እንኳን ትክክለኛውን የእግዚኣብሔር ፊት ማየት አንችልም። በተቃራኒው በደንብ ማየት የምንችለው የጠላትን የሰይጣንን ፊት ነው። ምክንያቱ የሰው ልጅ ሥጋ ወይም አካል በከፍተኛ ሁኔታ ለፈተና የተጋለጠ ነው።  የሥጋ ፍላጎቶቻችንን ለማርካት ቢቻ የምንጓዝ ከሆንን ከእግዚኣብሔር ጋር የሚያገናኘን መንገድ የተዘጋ ይሆናል ማለት ነው። ኋጢአት በሰዎች ልብ ውስጥ እግዚኣብሔርን የሚቃረን ነገር እንዲተከል ያደርጋል፣  ከእግዚአብሄር ጋር ቅራኔ እንዲፈጠር ያደርጋል፣ አሁንም በዚሁ መንገድ ከቀጠልን በልባችን ውስጥ  እግዚአብሔር ጨርሶ እንዳይኖር ያደርጋል።

ጾታዊ ንጽሕና የሕሊና ንጽሕና እንድኖር ያደርጋል

“ጾታዊ የሆነ ንጽሕና እንዲኖረን በርትተን የምንሰራ ከሆንን ንጹሕ የሆነ ሂሊና ሊኖረን ይችላል” በማለት ስብከታቸውን የቀጠሉት አባ ካንታ ላሜሳ በተለይም ደግሞ አሁን ባለንበት የዐብይ ጾም ወቅት “እንግዲህ ምጽዋት ስታደርግ፥ ግብዞች በሰው ዘንድ ሊከበሩ በምኩራብ በመንገድም እንደሚያደርጉ በፊትህ መለከት አታስነፋ፤ እውነት እላችኋለሁ፥ ዋጋቸውን ተቀብለዋል። ስትጸልዩም እንደ ግብዞች አትሁኑ፤ ለሰው ይታዩ ዘንድ በምኩራብና በመንገድ ማዕዘን ቆመው መጸለይን ይወዳሉና፤ እውነት እላችኋለሁ፥ ዋጋቸውን ተቀብለዋል። ስትጦሙም፥ እንደ ግብዞች አትጠውልጉ፤ ለሰዎች እንደ ጦመኛ ሊታዩ ፊታቸውን ያጠፋሉና፤ እውነት እላችኋለሁ፥ ዋጋቸውን ተቀብለዋል” (ማቴ 6) በማለት ኢየሱስ የሰጠንን ማሳሰቢያ በሕይወታችን ውስጥ የምንተገብርበት ወቅት ሊሆን ይገባል ብለዋል።

ብዙን ጊዜ ኋጢአት የምንሰራው በግብዝነት መንፈስ ተነሳስተን በመሆኑ የተነሳ፣ ግብዝነትን ደግሞ ኢየሱስ በወንጌሉ ያወገዘው ነገር በመሆኑ በዚህ አሁን በያዝነው የዐብይ ጾም ወቅት የግብዝነት መንፈስን የምናሸንፍበት ወቅት ሊሆን ይገባል በማለት አስተንትኖዋቸውን የቀጠሉት አባ ካንታ ላሜሳ የግብዝነት መንፈስን ማሸንፍ የምንችለው ደግሞ በቅድሚያ ያ መንፈስ በውስጣችን መኖሩን በመገንዘብ፣ ሁለት ዓይነት ሕይወት ከመኖር በመቆጠብ፣ በጸሎት በመትጋት እንደ ሆነ ጨምረው ገልጸዋል።

15 March 2019, 10:42