2018.11.15 Card. Parolin - convegno Fondazione Ratzinger 2018.11.15 Card. Parolin - convegno Fondazione Ratzinger 

ብጹዕ ካርዲናል ፔትሮ ፓሮሊን ሰብአዊ መብትን ለማስከበር ጥረት ማድረግ እንደሚያስፈልግ አሳሰቡ።

ብጹዕ ካርዲናል ፓሮሊን ቅድስት መንበር የሰውን ልጅ መብት ለማስከበር የምታሰማውን ድምጽና የምታደርገውን ጥረት አታቁርጥም ብለው መላዋ ቤተክርስቲያን ለመሠረታዊው የሰው ልጅ ነጻነት የቆሙ ተቋማትንና ግለሰቦችን አግኝታ ለመወያየት ዝግጁ መሆኗን አስረድተዋል።

የዚህ ዝግጅት አቅራቢ ዮሐንስ መኰንን - ቫቲካን

የቅድስት መንበር ዋና ጸሐፊ የሆኑት ብጹዕ ካርዲናል ፔትሮ ፓሮሊን በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የሰብዓዊ መብቶች ድንጋጌ 70ኛ ዓመትን ምክንያት በማድረግ በተካሄደው በራዚንገር ፋውንዴሽን ዓለም አቀፍ ሲምፖዚየም ላይ ባደረጉት ንግግር እንዳስገነዘቡት የቤተክርስቲያ ቀዳሚ ተግባር ስለ ሰው ልጅ ሙሉ ማንነት መስራት እንደሆነ አስታውቀዋል።

ብጹዕ ካርዲናል ፓሮሊን በንግግራቸው፣ የዛሬው ሕብረተሰብ ሰብዓዊ መብት ሲባል ብዙ የተጨነቀበት ነገር መብት በሚለው ቃል ብቻ እንጂ መብት ለሰው ልጅ አገልግሎት እንደቆመ የተረዳ አይመስልም ብለዋል። መብት ይከበር ሲባል ሊያገለግለው የቆመለትን የሰውን ልጅ ወደ ጎን የሚያደርግ ከሆነ ግለ ሰቦችና ቡድኖችን የራሳቸውን ጥቅም ብቻ ለማስጠበቅ ይጥራሉ እንጂ ለሰው ልጅ የሚሰጠው ፋይዳ አይኖርም ያሉትን የርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስን መልዕክት አስታውሰዋል። የቅድስት መንበር ዋና ጸሐፊ ብጹዕ ካርዲናል ፔትሮ ፓሮሊን ንግግራቸውን ያደረጉ በሮም ከተማ የሚገኘው የቅድስት ማርያም እርገት ዩኒቨርሲት ከራዚንገር ፋውንዴሽን ጋር በመሆን “የሰው ልጅ መሠረታዊ መብቶች እና በመብቶች መካከል የሚፈጠሩ ግጭቶች” በሚል ርዕስ ላይ በተዘጋጀው ሲምፖዚዬም ላይ ተገኝተው እንደሆነ ታውቋል።

ብጹዕ ካርዲናል ፓሮሊን ወደ አፍሪቃ የሚያደርጉትን ጉብኝት ከመጀመራቸው አስቀድመው የራዚንገር ፋውንዴሽን ፕሬዚደንት ክቡር አባ ፌደሪኮ ሎምባርዲና በቅድስት መንበር የሰብዓዊ መብት ጉዳይ ለሚከታተል ጽሕፈት ቤት ሰራተኞች ሰላምታቸውን አቅርበው፣ በቤተክርስቲያን ውስጥ የሰውን ልጅ ከማሕበራዊ፣ ኤኮኖሚያዊና መንፈሳዊ አመለካከት የሚነጥል የመብት ጥያቄ እንደሌለ አስታውሰው፣ የቤተክርስቲያ ቀዳሚ ተግባር ስለ ሰው ልጅ ሙሉ ማንነት መስራት እንደሆነ አስረድተዋል። ብጹዕ ካርዲናል ፓሮሊን ቅድስት መንበር የሰውን ልጅ መብት ለማስከበር የምታሰማውን ድምጽና የምታደርገውን ጥረት አታቁርጥም ብለው መላዋ ቤተክርስቲያን ለመሠረታዊው የሰው ልጅ ነጻነት የቆሙ ተቋማትንና ግለሰቦችን አግኝታ ለመወያየት ዝግጁ መሆኗን አስረድተዋል።

የቤተሰብ ክፍሎች፣

ብጹዕ ካርዲናል ፔትሮ ፓሮሊን ቤተሰብ አስመልክተው ባሰሙት ንግግራቸው፣ በተለይም የምዕራባዊያንን ባሕል በማስታወስ እንደተናገሩት የሰው ልጅ መብት በተወሰኑ ዘመናትና አካባቢዎች ብቻ ይተግበር የነበረው አሁን ግን በሁሉም የማሕበረሰቡ ክፍሎች ተግባራዊ እንዲሆን አሳስበው፣ በ1940 ዓ. ም. በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የጸደቀው የሰብዓዊ መብት ድንጋጌ በዓለም ውስጥ በሰው ልጆች መካከል ነጻነትን፣ ሰላምንና ፍትህን ተግባራዊ ማድረግ ያስፈልጋል ብለዋል።

ሰፊ ንጽጽርን ይጠይቃል፣

ብጹዕ ካርዲናል ፓሮሊን በንግግራቸው በዓለም አቀፋዊ ድርጅቶች መካከል የሚታየውን ዘርፈ ብዙ የዲፕሎማሲ ግንኙነት ኣየተዳከመ መምጣት በሰብዓዊ መብቶች ጉዳይ የተሰማሩትን አደጋ ላይ መጣሉን አስረድተው፣ ቅድስት መንበር በዚህ ዘርፍ ከሌሎች ጉዳዩ ከሚመለከታቸው ተቋማት ጋር በመሥራት ለሰዎች መብት፣ የጋራ ጥቅምና ማሕበራዊ እድገት በመሥራት ላይ መሆኗን ገልጸዋል። ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ እነዚህን ከላይ የተጠቀሱትንና ለሰው ልጆች ጥቅም የቆሙ ርዕሠ ጉዳዮችን ተግባራዊ ለማድረግ በዓለም አቀፍ ተቋማት መካከል፣ መንግሥታዊና መንግሥታዊ ባልሆኑ ድርጅቶችና ግለሰቦች መካከል አገናኝ ድልድይ መገንባት እንደሚያስፈልግ ማሳሰባቸውን ብጹዕ ካርዲናል ፓሮሊን ጠቅሰዋል።

ትኩረት የተጣሉባቸው ሰብዓዊ መብቶች፣

የተለየ ትኩረትን በማድረግ ቅድስት መንበር ጥረት ከምታደርግባቸው የሰው ልጅ መብቶች መካከል ለሕይወት ሊሰጥ የሚገባውን መብታ ያስታወሱት የቅድስት መንበር ዋና ጸሐፊ ብጹዕ ካርዲናል ፓሮሊን፣ አሁነ በደረስንበት የሳይንስ እድገት ለሰው ልጅ ሕይወት የሚሰጠው ትርጉም መልኩን ቀይሮ፣ በሴሎች ላይ በሚያድረጉት የተራቀቀ ምርምር ተፈጥሯዊ የሴል ግኝት በመለውጥ ሌላ ሰው ሰራሽ ፍጥረት እንዲገኝ ማድረጉ፣ የቀድሞ ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት በነዲክቶስ እንዳሉት፣ በሰው ልጅ መብቶች ላይ ጉዳትን በማስከተል ለሕይወት ሊሰጥ የሚገባው መብት እየጠፋ መሆኑን አስረድተዋል።

ስደተኞች አስመልክቶ ከሚደረጉ ውይይቶች ራስን ማግለል፣

የሞት ቅጣት ፍርድን ማስወገድ የቤተክርስቲያን አንዱ ጥረት እንደሆነ ብጹዕ ካርዲናል ፓሮሊን ተናግረዋል። ስለ ስደተኞችና ስለ ተፈናቃዮች መብት አንስተው ማብራሪያቸውን የሰጡት ካርዲናል ፓሮሊን በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ውስጥ እስከ መጭው ዓመት ድረስ የቅድስት መንበር ተግባር የሚሆነው የስደተኞችና የተፈናቃዮች መብት እንዲከበር ማድረግ እነደሆነ የገለጹት ብጹዕነታቸው አንዳንድ አገሮች ከውይይቱ እየወጡ መሆናቸው እንዳሳዘናቸው ገልጸዋል። ዓለም አቀፋዊ ስምምነቶች ተግባራዊ እንዲሆኑ የሚያደርጉ 20 አስተያየቶች፣ ዓለም አቀፉ ማሕበረሰብ፣ ስደተኞችንና ጥገኝነት ጠያቂዎችን በተመለከተ የወሰዳቸውን ውሳኔዎች ተግባራዊ እንዲሆኑ የሚያግዙ ገንቢ ዓለም አቀፋዊ ስምምነቶች ተግባራዊ እንዲሆኑ የሚያደርጉ አራት ርዕሶች እነርሱም ስደተኞችን ተቀብሎ ማስተናገድ፣ መንከባከብ፣ በሕብረተሰቡ መካከል ትክክለኛ ግንዛቤን እንዲኖር ማድረግና ስደተኞች ከሕብረተሰቡ ጋር አብረው መኖር እንዲችሉ ማድረግ የሚሉ ዓለም አቀፍ ስምምነቶች እንደሆኑ ብጹዕ ካርዲናል ፓሮሊን አስረድተዋል።

ይህን ዘገባ በድምጽ ለማዳመጥ ከዚህ ቀጥሎ የሚገኘውን ተጫወት የሚለውን ምልክት ይጫኑ
16 November 2018, 14:26