ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ፣ የመልአከ እግዚአብሔር ጸሎት በመሩበት ወቅት ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ፣ የመልአከ እግዚአብሔር ጸሎት በመሩበት ወቅት 

ር. ሊ. ጳ ፍራንችስኮስ፣ በማጉረምረም ጊዜን ማጥፋት የክርስቲያን ተግባር አለመሆኑን ገለጹ

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ፣ እሑድ ነሐሴ 23/2013 ዓ. ም. በላቲን የአምልኮ ሥርዓት የቀን አቆጣጠር መሠረት ከማርቆስ ወንጌል ምዕ. 7 ተወስዶ በተነበበው በዕለቱ ንባብ ላይ በማስተንተን ስብከታቸውን አቅርበዋል። በቅዱስ ጴጥሮስ አደባባይ ለተሰበሰቡት ምዕመናን የመልአከ እግዚአብሔር ጸሎት በመሩበት ወቅት፣ በማር. 7. 2-5 በተጻፈው ላይ በማስተንተን ባቀረቡት ስብከት፣ ሌሎችን ከመውቀሳችን በፊት እራሳችንን መመልከት እንደሚያስፈልግ አሳስበዋል። ቅዱስነታቸው አክለውም ችግሮች የሚመነጩት በሁሉም ነገር ሌሎችን እንድንወቅስ የሚያደርግ ስሜት ከልባችን ውስጥ ስለሚወጣ ነው ብለው፣ በእምነት እንድናድግ እግዚአብሔር ልባችንን እንዲያጸዳው በጸሎት መጠየቅ ይኖርብናል ብለዋል።

ክቡራት እና ክቡራን የዚህ ጽሑፍ አንባቢዎቻችን ከዚህ ቀጥሎ ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ ነሐሴ 23/2013 ዓ. ም በተነበበው የቅዱስ ወንጌል ክፍል ላይ በማስተነተን ያደረጉትን አስተንትኖ ትርጉም ሙሉ ይዘቱን እንደሚከተው አቅርበነዋል።

የዚህ ዝግጅት አቅራቢ ዮሐንስ መኰንን - ቫቲካን

"ውድ ወንድሞቼ እና እህቶቼ እንደምን አረፈዳችሁ!

በዛሬው የመስዋዕተ ቅዳሴ ጸሎት ወቅት የተነበበው የቅዱስ ወንጌል ክፍል፣ የሙሴ ሕግ መምህራን እና ፈሪሳውያን በኢየሱስ ክርስቶስ መገረማቸውን ይገልጻል። የተገረሙበት ምክንያትም ከኢየሱስ ደቀ መዛሙርት አንዳንዶቹ የሽማግሌዎችን ወግ ባለመጠበቅ፣ እጃቸውን ሳይታጠቡ እንጀራ ሲበሉ በማየታቸው ነበር። “ይህ የአሠራር መንገድ ሐይማኖታዊ ልማድን ይቃረናል” ብለው በማሰባቸው ነበር።

እኛም ብንሆን፣ ኢየሱስ እና ደቀ መዛሙርቱ የሽማግሌውችን ባሕል ለምን አላከበሩትም? ለምንስ ተቃወሙት? ብለን መጠየቅ እንችላለን። ከሁሉም በላይ ምግብ ከመመገብ በፊት እጅ መታጠብ መልካም ልማድ እንጂ መጥፎ የሚባል ባሕል አይደለም። ኢየሱስ ይህን ልማድ ያላከበረው ወይም ያልተከተለው ለምንድነው? ለኢየሱስ እጅግ አስፈላጊው እምነትን ማስቀደም ነበር። በቅዱስ ወንጌልም እምነት መቅደም እንዳለበት ተደጋግሞ ተጽፎ እናገኘዋለን። የሙሴ ሕግ መምህራን እና እኛም ብንሆን፣ ልባችንን እና እምነታችንን ደብቀን ውጫዊ ሥርዓቶችን ብቻ ከመፈጸም መቆጠብ እንዳለብን ቅዱስ ወንጌል ይናገራል። ብዙ ጊዜ እኛም ልባችንን ሳይሆን ውጫዊ ማንነታችንን አሳምረን መገኘትን እንወዳለን። የልባቸው ቆሻሻ ማጽዳት ሳይችሉ ቀርተው በውጫዊ ማንነት መልካም መስሎ መታየት መንፈሳዊነትን ለአደጋ ያጋልጣል። እግዚአብሔርን ከልባችን ሳይሆን ከአንገት በላይ የማምለክ ፈተና ሁል ጊዜ አለ። ነገር ግን ኢየሱስ ይህን ለመሰለ አምልኮ ዋጋን አይሰጥም። እርሱ ልብን የሚነካ እምነት እንጂ ለመታየት የሚቀርብ አምልኮን አይፈልግም።

በእርግጥ ለፈሪሳዊያን እና ለሙሴ ሕግ መምህራን ትልቅ እውነት ሲናገር፥ ‘ሰውን የሚያረክሰው ከሰው የሚወጣ ነገር እንጂ ከውጭ ወደ ሰው የሚገባውስ አያረክሰውም’ (ማር. 7:15) ብሏልና። ‘ሰውን የሚያረክሱት ከሰው ልብ የሚወጡት ነገሮች ናቸው’ (ማር. 7:21) ክፉ ነገሮች የሚወጡት ከሰው ልብ ውስጥ ነውና። ኢየሱስ ለፈሪሳዊያን እና ለሙሴ ሕግ መምህራን እንዲህ ብሎ መናገሩ በባሕላቸው ላይ ከፍተኛ ለውጥን የሚያስከትል ንግግር ነበር። ምክንያቱም በዘመኑ አስተሳሰብ የተወሰኑ ምግቦች ወይም ውጫዊ ግንኙነቶች እንደ ርኩስ ተደርገው ይታሰቡ ነበር። ኢየሱስ እምነታቸውን፣ ባሕላቸውን ወይም አመለካከታቸውን ለውጦ፣ ‘ከውጭ የሚመጣው ጉዳት የለውም፣ ይልቁንም ጉዳት የሚያስከትለው ከውስጥ የሚወጣው ነው’ ብሎ ነገራቸው።

ውድ ወንድሞቼ እና እህቶቼ፣ ይህ እኛንም ይመለከተናል። ብዙን ጊዜ ከክፉ ነገር የሚመጣው ከውጭ እንደሆነ እናስባለ፣ ክፉ ነገር፣ መጥፎ አመል ካላቸው፣ ለእኛ መልካም አመለካከት ከሌላቸው ሰዎች ወይም ከማኅበረሰባችን እንደሚመጣ እናስባብለን። በዚህም የተነሳ ለሚከሰቱብን ነገሮች በሙሉ ስንት ጊዜ ሌሎችን እንወቅሳለን? ስንት ጊዜ ማኅበረሰባችንን እና ዓለማችንን እንወቅሳለን? ሁል ጊዜ ስህተቱ የሌሎች እንደሆነ እናስባለን። ስህተቱ የሌሎች ሰዎች፣ የመንግሥት ወይም በአጋጣሚ የተከሰተ አድርገን እናስባለን። ችግሮች ከውጫዊ አካል እንደሚመጡ በማሰብ ሌሎችን ስንወቅስ እንታያለን። ጥፋትን በሌሎች ላይ ስንጭን ጊዜያችንን እንጨርሳለን። ሌሎችን እየወቀስን ጊዜን መጨረስ ጊዜን ማጥፋት ነው የሚሆንብን። በዚህ ምክንያት ስንቆጣ እና ስናማርር እግዚአብሔር ከልባችን እናርቀዋለን። በቅዱስ ወንጌል ውስጥ እንደተጠቀሱት እና ሁል ጊዜ ሌሎችን እንደሚወቅሱ ፣ ክርክር እንደሚፈጥሩ እና ኢየሱስን እንደማይቀበሉ ፈሪሳውያን እና የሙሴ ሕግ መምህራን እንሆናለን። ማጉረምረም መርዝ ነው። ወደ ቁጣ ይመራናል። ለእግዚአብሔር በር እንዲዘጋ ወደሚያደርግ ቂም እና ሀዘን ስለሚመራ፣ የሚያጉረመርም ሰው እውነተኛ መንፈሳዊ ሊሆን አይችልም።

እንደ ሕጻናት ሁል ጊዜ ሌሎችን ከመውቀስ ነጻ እንዲያደርገን እግዚአብሔርን በጸሎት እንጠይቅ። በማጉረምረም ብቻ ጊዜያችንን እንዳናጠፋ እግዚአብሔር ጸጋውን እንዲሰጠን እንለምነው። በማጉረምረም ጊዜን ማጥፋት የክርስቲያን ሰው ተግባር አይደለም። ኢየሱስ ልባችንን እና መላውን ዓለም እንድንመለከት ይጋብዘናል። ውስጣችንን ብንመለከት እንደ ዋዛ ቆጥረን ንቀን ያለፍናቸውን ነገሮች እናገኛቸዋለን። እግዚአብሔር ልባችንን እንዲያነጻልን ከለመንነው ፣ ዓለምን ንጹህ ማድረግ የምንጀምረው ያኔ ነው። ምክንያቱም ክፋትን ለማሸነፍ የምንችለው ልባችንን ስናጸዳ ነው። ልባችን የምናጸዳው ራስን ማሸነፍ ስንጀምር ነው። የመጀመሪያዎቹ የቤተክርስቲያን አባቶች፣ መነኮሳት፣ ‘የቅድስና መንገድ የቱ ነው?’ ተብለው ሲጠየቁ፥ ‘የመጀመሪያው እርምጃ ራስን መውቀስ ነው’ ይሉ ነበር። ስለዚህ ራሳችንን እንውቀስ። ይህ እንዲህ አረገኝ! ያ ደግሞ ጨክኖብኝ እንዲህ አረገኝ ከማለት በቀር፣ ለመሆኑ ስንቶቻችን ነን በቀን ውስጥ ወይም በሳምንት ውስጥ እራሳችንን የምንወቅሰው? ራስን መውቀስ መማር ጥበብ ነው። ይህን ማድረግ ከተቻለ ከራስ አልፎ ለሌሎችም ከፍተኛ ጥቅም ያስገኛል።

ልቧን በማጽዳት ታሪክን የቀየረች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም፣ ሌሎችን ከመውቀስ፣ በሁሉ ነገር ማጉረምረምን ትተን፣ ልባችንን ማጽዳት እንድንችል ትርዳን በማለት እንለምናታለን።”       

30 August 2021, 16:44

የገብርኤል ብሥራት ጥንታዊ መሠርት የያዘና የጌታችን እየሱስ ክርስቶስን ሰው መሆን በማስታወስ በቀን ሦስት ጊዜ ማለትም በንጋት (በአስራሁለት ሰዓት) በቀትር (በስድስት ሰዓት) እንዲሁም በማታ (በአስራሁለት ሰዓት) የሚደገም የጸሎት ዓይነት ሲሆን ጸሎቱ በሚደገምበት ሰዓት ቤተ ክርስቲያንም የመልኣከ እግዚኣብሔርን ደወል በዚሁ ሰዓት ትደውላለች። ይህ ጸሎት መልኣከ እግዚኣብሔር የሚለውን ስያሜ ያገኝው ከጸሎቱ ከመጀመሪያ ስንኝ የእግዚኣብሔር መልኣከ ማርያምን አበሠራት ከሚለው የተወሰደ ሲሆን ጸሎቱ ስለ ጌታችን እየሱስ ክርስቶስ ሰው መሆን ይናገራል። ጸሎቱ በሦስት የተከፈሉ አጫጭር ስንኞች ሲኖሩት በእነኚህ በሦስት አጫጭር ስንኞች መሓል ጸጋን የተሞላሽ የሚለው የማርያም ጸሎት ይደገማል። ይህ ጸሎት በሰንበትና በበዓላት ዕለት ልክ በእኩለ ቀን ላይ በዕለቱ ወንጌል ላይ ትንሽ አስተምሮና ገለፃ ከሰጡ በኋላ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት በቅዱስ ጴጥሮስ ኣደባባይ ላይ ይህንን ጸሎት ይመራሉ። በመቀጠልም በአደባባዩ ላይ የተገኝው ከተለያየ ቦታ ለንግደት የመጣውን ሕዝብ ሰላምታ ይሰጣሉ።በየትኛውም ጊዜ ከበዓለ ፋሲካ እስከ በዓለ ጰራቅሊጦስ በመልኣከ እግዚኣብሔር ጸሎት ፈንታ የጌታችን እየሱስ ክርስቶስን ትንሣኤ የሚዘክረውን “የሰማይ ንግሥት ሆይ ደስ ይበልሽ” የሚለው ጸሎት የሚደገም ሲሆን በመሓል በመሓሉ ጸጋን የተሞላሽ ማርያም ሆይ የሚለው ጸሎት ይታከልበታል።

መልኣኩ ገብርኤል ማሪያምን አበሰራት የሚለው የቀርብ ጊዜ ጸሎት

ሁሉንም ያንብቡ >