በደቡብ አፍሪካ እየተከሰተ የሚገኝ ሁከት በደቡብ አፍሪካ እየተከሰተ የሚገኝ ሁከት  

ር.ሊ.ጳ ፍራንቸስኮስ በድህረ-አፓርታይድ ደቡብ አፍሪካ ውስጥ ገንቢ ትብብር እንዲደረግ ጥሪ አቅርበዋል

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ በኮቪድ 19 ወረርሽኝ ምክንያት እጅግ በጣም ከፍተኛ የሆነ ሰቆቃ በደረሰባት በደቡብ አፍሪካ ከባለፈው ሳምንት ጀምሮ እየተከሰተ የሚገኘው ሁከት ገንቢ ትብብር በመፍጠር እንዲፈታ እና የችግሩ ገፈት ቀማሽ የሆኑ ሰዎች አሰፈላጊው እርዳታ ይደረግላቸው ዘንድ ጥሪ ማቅረባቸው ተገልጿል።

የዚህ ዝግጅት አቅራቢ መብራቱ ኃ/ጊዮርጊስ ቫቲካን

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ እሁድ ሐምሌ 11/2013 ዓ.ም በቫቲካን በሚገኘው በቅዱስ ጴጥሮስ አደባባይ ለተሰበሰቡ ምዕመናን በእለቱ ቅዱስ ወንጌል ላይ ተንተርሰው አስተንትኖ ካደረጉ በኋላ ለአለም ባስተላለፉት ሳምንታዊ መልእክት የደቡብ አፍሪካ ፖለቲከኞች ፣ የቡድን መሪዎችን እና በቅርቡ በተከሰተው ሁከት ውስጥ የተሳተፉት ሁሉ ሰላምን ለማስፈን ለሚደረገው ጥረት ገንቢ ትብብር እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርበዋል።

ቅዱስነታቸው በወቅቱ እንደተናገሩት “እንደ አለመታደል ሆኖ በዚህ ባለፈው ሳምንት በደቡብ አፍሪካ ያሉ በርካታ ወንድሞቻችን እና እህቶቻችንን ሁኔታ የሚያባብሱ እየተከናወነ የሚገኘውን ሁከት የሚገልጹ ዜናዎች ደርሶናል” ብለዋል። የቀድሞ የደቡብ አፍሪካ ፕሬዝዳንት ጃኮብ ዙማ እስር ቤት በመግባታቸው ምክንያት በአንዳንድ ሰዎች ቁጣ የተነሳ ይህ ሁከት ድህነትና እኩል የመሆን መብት እንደተነፈጋቸው በሚያምኑ ሰዎች ምክንያት በተቀሰቀሰው ሁከት ከ 200 በላይ ሰዎች መገደላቸው ተገልጿል።

በደቡብ አፍሪካ የተነሳው ብጥብጡ በፍጥነት ወደ ዘረፋ በመዛወሩ በመቶዎች የሚቆጠሩ የንግድ ድርጅቶች የወደሙ ሲሆን ፖሊስ ሁከትን በማነሳሳት ተሳትፈዋል በማለት የጠረጠራቸው  ከ 2500 በላይ ሰዎችን በቁጥጥር ስር አውሏል።

የደቡብ አፍሪካ ዜጎች በድህነት ፣ በእኩልነት እጦት እና በወረርሽኝ ተመትተዋል

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳቱ ብዙ የደቡብ አፍሪካ ዜጎች ቀደም ሲል በኩቪድ -19 በተከሰተው ወረርሽኝ በተፈጠረው ኢኮኖሚያዊ እና የጤና ችግሮች እንደተጎዱ አስተውለዋል። “ከሀገሪቱ ጳጳሳት ጋር በመሆን ለሰላም እንዲሰሩ እና ከባለስልጣናት ጋር በመተባበር ለችግረኞች እርዳታ ለመስጠት እንዲሳተፉ ኃላፊነት ላላቸው ሁሉ ለሚመለከታቸው ሁሉ ልባዊ ጥሪዬን አቀርባለሁ” ብለዋል።

የአፓርታይድ አገዛዝ ከተጠናቀቀ ወዲህ ወደ ሶስት አስርት ዓመታት ገደማ በአገሪቱ ውስጥ ከተፈጠረው እጅግ የከፋ ሁከት ተብሎ የተፈረጀው ይህንን ከባለፈው ሳምንት ጀምሮ በደቡብ አፍሪካ እየተካሄደ የሚገኘው ሁከት በተመለከተ የተናገሩት ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ አክለውም “የደቡብ አፍሪካን ህዝብ ያላቸው ፍላጎት ፣ በሁሉም የአገሪቷ ልጆች መካከል ያለው መግባባት ዳግም እንዲወለድ፣ ይህ ትብብር መቼም ቢሆን አንዳይረሳ” ጥሪ አቀርባለሁ ብለዋል።

የደቡብ አፍሪካ ፕሬዝዳንት ሲሪል ራማፎሳ ባለፈው ሳምንት አርብ ዕለት በሀገሪቱ የተከሰተው ሁከት መረጋጋቱ እና አብዛኛዎቹ አካባቢዎች ወደ ሰላማዊ ሁኔታ መመለሳቸውን አስታውቀው የነበረ ሲሆን ጥፋቱ ግን ሀገሪቱን በቢሊዮን የሚቆጠር ገንዘብ ያስከፍላታል ብለዋል።

በኮቪድ -19 ወረርሽኝ በተጨማሪ የተከሰተ ሁከት

ይህ በእንዲህ እንዳለ ሐሙስ ሐምሌ 08/2013 ዓ.ም ላይ ወደ 16,500 የሚጠጉ አዳዲስ በኮቪድ 19 ወረርሽኝ የተያዙ ሰዎች በአገሪቷ እንደ ሚገኙ እና በኮቪድ -19 ወረርሽኝ የሚያዙ ሰዎች ቁጥር እየጨመረ መምጣቱን የዓለም ጤና ድርጅት ዘገባ ያሳያል።

ሰሞኑን የተከሰተው ሁከት የኮቪድ -19 ወረርሽኝ የመቆጣጠር ጥረቶችን እና የክትባት አሰጣት ሂደቶች እንዲቋረጥ ያደረገ ሁከት ሲሆን ባለሞያዎችም ብጥብጡን ተከትሎ የሚከሰቱ ከፍተኛ ችግሮች እንደሚኖሩ ይተነብያሉ።

18 July 2021, 11:15